በ2015 ዓ. ም የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ በገዢው ፓርቲ እና በባለሙያ ዕይታ
ቅዳሜ፣ መስከረም 5 2016የብልፅግና ፓርቲ ምክትል ፕሬዚዳንት አቶ አደም ፋራህ በ2015 ዓ.ም "በኢኮኖሚው ዘርፍ ለዘመናት ሲንከባለሉ የመጡ የኢኮኖሚው ስብራቶችን ለመጠገናንና ችግሩን ከስር መሰረቱ ለመፍታት የሚያስችሉ" ያሏቸው ስኬቶች በግብርና፣ በቱሪዝም እና በኢንዱስትሪ ዘርፎች ተመዝግቧል ማለታቸው ተሰምቷል።
የገዢው ፓርቲ ምክትል መሪ ኢትዮጵያን "በዓለማችን ፈጣን የኢኮኖሚ እድገት ካስመዘገቡ ሀገራት ተርታ ማሰለፍ ከመቻላችንም በተጨማሪ የኢኮኖሚ እድገቱን ጤናማነት፣ ቀጣይነትና ዘላቂነት ለማስጠበቅ፣ አዳዲስ ሀብቶችን ለመፍጠር የሚያስችሉ" ያሏቸውን ስኬታማ ሥራዎች ማከናወናቸውን ተናግረዋል።
በጉዳዩ ላይ ሙያዊ ምልከታቸውን ያጋሩን አንድ ገለልተኛ ከፍተኛ የምጣኔ ሀብት ባለሙያኢትዮጵያ በአጠቃላይ የማክሮ ኢኮኖሚ አመላካቾች ማለትም በዋጋ ንረት ፣ በውጪ ምንዛሬ እጥረት እና በሥራ አጥነት መሠረታዊ ችግር ውስጥ ያለች በመሆኗ "ቆንጆ የማክሮ ኢኮኖሚ ሁኔታ ላይ አይደለችም" ብለዋል።
አክለውም መንግሥት "ቁጭ ብሎ ከፖለቲካው ሌላ በኢኮኖሚውም ላይ ከባድ ችግር አለብኝ ብሎ አንድ ነገር ላድርግ ብሎ ማሰብ ያለበት ጊዜ ነው" ብለዋል።
የምጣኔ ሀብት ባለሙያ ስለዚህ ጉዳይ ምን አሉ ?
የብልፅግና ፓርቲ ምክትል ፕሬዚዳንት አቶ አደም ፋራህ ኢትዮጵያ በ2015 ዓ.ም በኢኮኖሚው ዘርፍ ለዘመናት ሲንከባለሉ የመጡ ላሏቸው ግን ያልዘረዘሯቸው "የኢኮኖሚ ስብራቶች" ን ለመጠገናንና ችግሩን ከስር መሰረቱ ለመፍታት የሚያስችሉ ስኬቶች ነበሩ ማለታቸው በተረጋገጠ የፓርቲው የማህበራዊ መገናኛ ዐውታር - ፌስቡክ ሰፍሯል።
የምጣኔ ሀብት ከፍተኛ ባለሙያው ፕሮፌሰር አለማየሁ ገዳ መንግሥት ይህንን ለማለት የስታቲስቲክስ ኤጄንሲ ተዓማኒነት ያለውን መረጃ አለመጠቀሙን በመግለጽ፣ ከዚያም አልፎ የተቋሙ ነባር የሥራ ኃላፊዎች ከኃላፊነት እንዲነሱ መደረጋቸው በተለይ የስንዴ ምርትን በተመለከተ እየወጡ ላሉ መረጃዎች የተጋነኑ መሆን እንደ ምክንያት አድርገው በመጥቀስ ሞግተዋል።
"አሁን ችግሩ ምን መሰለህ የ 2015 ዓ. ም ይፋዊ መረጃ አልወጣም።መንግሥት ያንን የነበረ 5.5 በሦስት እጥፍ ጨምሬዋለሁ 15 አድርጌዋለሁ ወይም 55 ሚሊዮን የነበረውን 150 ሚሊየን በላይ ኩንታል አድርጌዋለሁ ነው የሚለው። ስለዚህ የሚሰጥህ አሐዝ የራሱ አሐዝ እና የግብርና ሚኒስቴር አኃዝ ነው። የስታቲስቲክስ ባለስልጣን ስልታዊ ዘዴ ተጠቅሞ በየዓመቱ የሚያወጡት ተዓማኒ የሆነ አኃዝ አለ። ይሄ ነገር በ2015 አልወጣም"
የኢትዮጵያ አጠቃላይ ማክሮ ኢኮኖሚ ምን ይመስላል?
በአጠቃላይ የማክሮ ኢኮኖሚ አመልካቾች ትንትና ሲታይ ይህ የገዢው ፓርቲ አቋም ትክክል አለመሆኑን የምጣኔ ሀብት ባለሙያው በማሳያ ጭምር አጣቅሰው አሳይተዋል።
"አጠቃላይ የማክሮ ኢኮኖሚ ስትል የምታይባቸው አመላካቾች አሉ ። እነዚህ አመላካቾች ምንድን ናቸው ። አንድ የዋጋ ንረት ነው። ሁለት የውጪ ምንዛሬው ተመን የተረጋጋ ነው የተረጋጋ አይደለም የሚለው ነው። ሦስተኛ ሥራ አጥነት ነው።በእነዚህ መለኪያዎች ስታይ የዋጋ ግሽበት ጣሪያ ነክቷል።የውጭ ምንዛሬው በጣም አሳሳቢ ችግር አለበት።የወጣት ሥራ አጥነት የተረጋገጠ መረጃ ስትውፕስድ 26 በመቶ ነው። ስለዚህ እነዚህን አመላካቾች ወስደህ ስታይ ቆንጆ ማክሮ ኢኮኖሚ ላይ አይደለም ማለት ነው ኢኮኖሚው።" በማለት ጠቅሰዋል።
ሰሎሞን ሙጬ
ዮሃንስ ገብረእግዚአብሄር