1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የታኅሣሥ 15 ቀን፣ 2016 ዓ.ም የስፖርት ዘገባ

ሰኞ፣ ታኅሣሥ 15 2016

በእንግሊዝ ፕሬሚየር ሊግ፦ ሊቨርፑልን በሜዳው ነጥብ ያስጣለው ማንቸስተር ዩናይትድ ቅዳሜ ዕለት በዌስትሀም ዩናይትድ የ2 ለ0 ሽንፈት አስተናግዷል ። ማንቸስተር ሲቲ በፊፋ የዓለም እግር ኳስ ዋንጫ የብራዚሉ ፍሉሚኔንዜን ዐርብ ዕለት 4 ለ0 አሸንፎ ዋንጫውን ወስዷል ። የአበረታች ንጥረ ነገር ጉዳይ የኢትዮጵያ አትሌትን ሰቅዞ ይዟል ።

https://p.dw.com/p/4aZQZ
Fußball Saudi Arabien | Club WM |  Manchester City v Fluminense
ምስል AMR ABDALLAH DALSH/REUTERS

ሣምንታዊ የስፖርት ዘገባ

የእንግሊዝ ፕሬሚየር ሊግ የእግር ኳስ ግጥሚያ ፉክክር እጅግ ተጠናክሯል ። አርሰናል፤ ሊቨርፑል እና አስቶን ቪላ በአንድ ነጥብ ብቻ ልዩነት ከአንደኛ እስከ ሦስተኛ ደረጃ ተከታትለዋል።  በጀርመን ቡንደስሊጋ ማሰራጪያ ጣቢያችን የሚገኝበት የቦን ከተማ ተጎራባቹ ኮሎኝ ቡድን ከቡንደስሊጋው ሊሰናበት እንደ ማይንትስ እና ዳርምሽታድት ወራጅ ቀጣናው ውስጥ ቁልቅል ሰፍሯል ። ሩስያን ከዓለም እና ከኦሎምፒክ መድረክ ያሰናበታት የአበረታች ንጥረ ነገር ጉዳይ የኢትዮጵያ አትሌትንም ሰቅዞ ይዟል ። ጉዳዩ በአስቸኳይ መፍትኄ ካልተበጀለት ብርቱ አደጋ መደቀኑ እየተነገረለት ነው ።

እግር ኳስ

በእንግሊዝ ፕሬሚየር ሊግ፦ ሊቨርፑልን በሜዳው ነጥብ ያስጣለው ማንቸስተር ዩናይትድ ቅዳሜ ዕለት በዌስትሀም ዩናይትድ የ2 ለ0 ሽንፈት አስተናግዷል ። ይህም በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የዘንድሮ ውድድር ለማንቸስተር ዩናይትድ ስምንተኛ ሽንፈቱ ሆኖ ተመዝግቧል ። በ18 ጨዋታዎች በሰበሰበው 28 ነጥብም ስምንተኛ ደረጃ ላይ ተወስኗል ። በደረጃ ሰንጠረዡ እንደ ሊቨርፑል ተመሳሳይ 39 ነጥብ ይዞ ሦስተኛ ላይ ከሚገኘው አስቶን ቪላ ጋ ይጋጠማል ።  ከመሪው አርሰናል በአንድ ነጥብ ብቻ የሚበለጠው አስቶን ቪላ ለማንቸስተር ዩናይትድ ብርቱ ተገዳዳሪ መሆኑ አይቀርም ።

ፕሬሚየር ሊግ

የታኅሣሥ 8 ቀን፣ 2016 ዓ.ም የስፖርት ዘገባ ሊቨርፑል ረቡዕ እለት ዌስትሀም ዩናይትድን 5 ለ1 ድባቅ መትቶ ለካራባዎ ዋንጫ ግማሽ ፍፃሜ ደርሷል ። በፕሬሚየር ሊጉ ግን ቅዳሜ ዕለት በገዛ ሜዳው አንፊልድ ላይ በአርሰናል ነጥብ ጥሏል ። አንፊልድ እንዲያ በቀያዮቹ ድጋፍ ስትናጥ አምሽታ በተለያዩ ምክንያቶች ግን ድል ለሊቨርፑል ሳይሆን ቀርቷል ። ፍጽም ቅጣት ምት ክልል ውስጥ በአርሰናል አማካይ ተጨዋች ማርቲን ኦዴጋርድ በእጅ የተነካችው ኳስ ፍጹም ቅጣት ምት ልትሆን የምትገባ እንደነበር የአርሰናል ተጨዋቾች ራሳቸው ከጨዋታው በኋላ መስክረዋል ።  የአርሰናሉ አጥቂ ቡካዮ ሳካ ኮስታስ ሲሚካስ ላይ አደገኛ ጥፋት ሠርቶም በቀላሉ ታልፏል ። በጥፋቱ ግሪካዊው የሊቨርፑል ተከላካይ ትከሻው ላይ ከፍተኛ ጉዳት ደርሶበት ከሜዳ ወጥቷል፤ ለረዥም ጊዜ ከጨዋታ ውጪ መሆኑም ተረጋግጧል ። ሲሚካስ ተገጭቶ ሲወድቅ ጀርመናዊው አሰልጣኝ የርገን ክሎፕን ጠልፎ ጥሏቸዋል ። በአጠቃላይ ዬርገን ክሎፕ በሚታወቁበት በሰው ለሰው የማስጨነቅ ስልት ድንቅ ጨዋታ ብልጫ ዐሳይቶ ለነበረው ሊቨርፑል ምሽቱ ጥሩ አልነበረም ። በቅዳሜው ውጤት መሰረት፦ አርሰናል በ1 ነጥብ ልዩነት መሪነቱን አስጠብቋል ።

ማንቸስተር ሲቲ የብራዚሉ ፍሉሚኔንዜን ሸንፎ
ማንቸስተር ሲቲ የብራዚሉ ፍሉሚኔንዜን ዐርብ ዕለት 4 ለ0 አሸንፎ ዋንጫ ሲወስድምስል GIUSEPPE CACACE/AFP

የታኅሣስ 1 ቀን፣ 2016 ዓ.ም የስፖርት ዘገባ ማንቸስተር ሲቲ አንድ ተስተካካይ ጨዋታ እየቀረው በ34 ነጥብ አምስተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል ። ከበላዩ በሁለት ነጥብ የሚበልጠው ቶትንሀም ሆትስፐር ሰፍሯል ። ቸልሲ ዳግም ሽንፈት አስተናግዷል ። ትናንት 2ለ1 የተሸነፈው በዎልቨርሀምፕተን ነው ። ረቡዕ ዕለት ከክሪስታል ፓላስ ጋ ይጋጠማል ። ማንቸስተር ሲቲ በፊፋ የዓለም እግር ኳስ ዋንጫ የብራዚሉ ፍሉሚኔንዜን  ዐርብ ዕለት 4 ለ0 አሸንፎ ዋንጫውን ወስዷል ። 

ምናልባትም ቸልሲ ከተደጋጋሚ ሽንፈቱ ይታደገው ዘንድ በጎርጎሪዮሱ የክረምት ወራት 180 ሚሊዮን ዩሮ መድቧል ። እንደ «ኢቭኒንግ ስታንዳርድ» ዘገባ ከሆነ፦ ቸልሲ በክረምቱ ሁለት ተጨዋቾችን ማስመጣት ይሻል ። በተለይ በፖርቹጋል ሊጋ የስፖርቲንግ አጥቂ ቪክቶር  ጊዮኬርስን ለማስመጣት የቆረጠ ይመስላል ። ስዊድናዊው አጥቂን ግን የጀርመኑ ባየርን ሙይንሽን እና የዘመናት ተቀናቃኙ ቦሩስያ ዶርትሙንድም ዐይናቸውን ጥለውበታል ።

ከስፖርት ጋዜጠኛ ዖምና ታደለ ጋ የተደረገው ሙሉ ቃለ መጠይቅ እዚህ ይገኛል

የኅዳር 24 ቀን፣ 2016 ዓ.ም የስፖርት ዘገባ ቸልሲ አጥቂ ብቻ ሳይሆን የተከላካይ መስመሩንም ማጠናከር ይሻል ።  ከዚያው ከፓርቹጋሉ ስፖርቲንግ ሊዛቦን የአይቮሮኮስቱ ተከላካይ ኦስማኔ ዲያማንዴን ለማሰመጣት ንግግሩ መቀጠሉ ተዘግቧል ። ስፖርቲንግ ሊዛቦን እስከ 2028 ያስፈረመው የ25 ዓመቱ አጥቂን ለመሸጥ እስከ 100 ሚሊዮን ዩሮ ይፈልጋል ። ለ20 ዓመቱ ወጣት ተከላካይ ደግሞ 80 ሚሊዮን ዩሮ እሻለሁ ማለቱ ተሰምቷል ። እሱም ቢሆን ረዘም ላለ ጊዜ እስከ 2027 ነው ለሊዛቦን የፈረመው ። በነገራችን ላይ ቸልሲ ዐይኑን የጣለበት የስፖርቲንግ ሊዛቦን አጥቂ በዘንድሮ የፖርቹጋል ሊጋ 17 ኳሶችን ከመረብ ማሳረፍ ችሏል ። ስምንት ግብ ሊሆኑ የቻሉ ኳሶችንም በማመቻቸት ግብ አዳኝነቱን አስመስክሯል ።

የአፍሪቃ እግር ኳስ ዋንጫ

የአፍሪቃ እግር ኳስ ዋንጫ ከ19 ቀናት በኋላ አይቮሪ ኮስት ውስጥ ሲጀምር ከጀርመን ቡንደስሊጋ 24 ተጨዋቾች ለአፍሪቃው ውድድር ወደየሃገሮቻቸው እንደሚሄዱ ታውቋል ። በተመሳሳይ ጊዜ በአንድ ቀን ልዩነት ብቻ ካታር ውስጥ በሚጀምረው የእስያ እግር ኳስ ዋንጫ ፉክክር ላይም ለመሳተፍ የጃፓን እና የደቡብ ኮሪያ ስምንት ተጨዋቾች ከቡንደስሊጋው ለአንድ ወር ያህል እንደሚርቁ ተዘግቧል ። ይህም በቡንደስሊጋው ላይ ብርቱ ተጽእኖ ማሳረፉ አይቀርም ።

ቡንደስ ሊጋ

የኅዳር 17 ቀን፣ 2016 ዓ.ም የስፖርት ዘገባ በጀርመን ቡንደስ ሊጋ የገና ሰሞን ረፍት ከመደረጉ በፊት ባለፈው ሳምንት በነበሩ ግጥሚያዎች፦ መሪው ባዬርን ሌቨርኩሰን ቦሁምን 4 ለ0 አደባይቷል ። በዚህም ነጥቡን 42 አድርሶ በደረጃ ሰንጠረዡ የበላይነት መኮፈስ ችሏል ። ባዬርን ሙይንሽን ረቡዕ ዕለት ቮልፍስቡርግን 2 ለ1 አሸንፎ ያገኘው ተደምሮለት አጠቃላይ ነጥቡን 38 በማድረስ ሁለተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል ። 34 ነጥብ ይዞ በደረጃ ሰንጠረዡ ሦስተኛ ላይ የሚገኘው ሽቱትጋርት ረቡዕ ዕለት አውግስቡርግን 3 ለ0 ማሰናበት ችሏል ። ከቬርደር ብሬመን ጋ ባለፈው ሳምንት ማክሰኞ ዕለት አንድ እኩል የወጣው ላይፕትሲሽ 33 ነጥብ ይዞ አራተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል ። ቦሩስያ ዶርትሙንድም በተመሳሳይ ቀን ከማይንትስ ጋ በተመሳሳይ አንድ እኩል ተለያይቷል ።  27 ነጥብ አለው ። ተደጋጋሚ ሽንፈትን ያስተናገደው ኮሎኝ ቡድን ከበታቹ ዳርምሽታድትን ከበላዩ ማይንትስን ይዞ በተመሳሳይ 10 ነጥብ ወራጅ ቀጣናው ውስጥ ይገኛል ። ዑኒዮን ቤርሊን በ13 ነጥብ ወራጅ ቀጣናው ጠርዝ 15ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል ። ቡንደስሊጋው የገና እና የአዲስ ዓመት ረፍት ፋታ አድርጎ ከሁለት ሳምንት በኋላ ዳግም ይጀምራል። 

አትሌቲክስ

የፓሪሱ ኦሎምፒክ ተዳርሷል
ኢትዮጵያ አፋጣን ርምጃ ካልወሰደች ምናልባትም ከፓሪሱ ኦሎምፒክ የመታገድም ስጋት አንዣብቧልምስል Francois Mori/AP/dpa/picture alliance

የኃይል ሰጪ ንጥረ ነገሮች ጉዳይ በኢትዮጵያ አትሌቲክስ ዘርፍ አነጋጋሪነቱ እጅግ እየጨመረ ነው ። በተለይ ዓለም አቀፉ የጸረ ኃይል ሰጪ ንጥረ ነገር ኩባንያ (WADA) ኢትዮጵያን የመጨረሻ ማስጠንቀቂያ ከተሰጣቸው ሃገራት ተርታ መመደቡ የችግሩን ግዝፈት የሚያሳይ ነው።  ኢትዮጵያ አፋጣን ርምጃ ካልወሰደች ምናልባትም ከፓሪሱ ኦሎምፒክ የመታገድም ስጋት አንዣብቧል ። ለዚህም ይመስላል የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን፤ የባሕል እና ስፖርት ሚንስትር እንዲሁም የኢትዮጵያ ፀረ-አበረታች ቅመሞች ባለስልጣን በጉዳዩ አሳሳቢነት ላይ ተደጋጋሚ ስብሰባዎችን እያደረጉ ነው ። የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን፤ የችግሩን አሳሳቢነት በመግለጽ የጠቅላይ ሚንስትር ጽ/ቤትን ጨምሮ 23 ማኅበራት እና ተቋማትን ያሳተፈ ስብሰባ እንዲጠራም ጥያቄ አቅርቦ ነበር ።  የስፖርት ጋዜጠኛው ዖማና ታደለ የኃይል ሰጪ ንጥረ ነገሮች ጉዳይ ኢትዮጵያ ውስጥ አሳሳቢነቱ እጅግ የከፋ ደረጃ ላይ ደርሷል ይላል ።

ማንተጋፍቶት ስለሺ

ኂሩት መለሠ