1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የሐምሌ 29 ቀን፣ 2016 ዓ.ም የስፖርት ዘገባ

ሰኞ፣ ሐምሌ 29 2016

የፓሪስ ኦሎምፒክ ቀጥሏል ። በዐሥር ሺህ ሜትር የወንዶች ፉክክር የብር ሜዳሊያ ያገኘችው ኢትዮጵያ በሴቶቹ አምስት ሺህ እና ስምንት መቶ ሜትር ፉክክር ምሽቱን ተጨማሪ ሜዳሊያ ትጠብቃለች ። ኖቫክ ጄኮቪች በሜዳ ቴኒስ ድል ተቀዳጅቷል ። በፓሪስ ኦሎምፒክ ትሪያትሎን የተሳተፉ አትሌቶች ከወንዙ ጋ በተገናኛ ለሕመም መዳረጋቸው ተዘቧል ።

https://p.dw.com/p/4j8fA
ፎቶ ከማኅደር፦ ኢትዮጵያውያን፤ ኬንያውያን እና ኔዘርላንዳዊቷ ትውልደ ኢትዮፕያ ተፎካካሪዎች ምሽቱን በ5000 ሜትር ፍጻሜ ይጠበቃሉ
ፎቶ ከማኅደር፦ ኢትዮጵያውያን፤ ኬንያውያን እና ኔዘርላንዳዊቷ ትውልደ ኢትዮጵያ ተፎካካሪዎች ምሽቱን በ5000 ሜትር ፍጻሜ ይጠበቃሉምስል JAVIER SORIANO/AFP

ሣምንታዊ የስፖርት ዘገባ

የፓሪስ ኦሎምፒክ ቀጥሏል ። በዐሥር ሺህ ሜትር የወንዶች ፉክክር የብር ሜዳሊያ ያገኘችው ኢትዮጵያ በሴቶቹ አምስት ሺህ እና ስምንት መቶ ሜትር ፉክክር ምሽቱን ተጨማሪ ሜዳሊያ ትጠብቃለች ። የ37 ዓመቱ ኖቫክ ጄኮቪች የማታ ማታ በሜዳ ቴኒስ ድል ተቀዳጅቷል ። በፓሪስ ኦሎምፒክ የትሪያትሎን ተፎካካሪ ተሳተፉ አትሌቶች ከወንዙ ጋ በተገናኛ ለሕመም መዳረጋቸው ተዘግቧል ። በፓሪስ እና አካባቢዋ ወንዞችን ለማጽዳት ከ1.4 ቢሊዮን ዶላር በላይ መውጣቱ ቀደም ሲል ተገልጦ ነበር ። 

የፓሪስ ኦሎምፒክ

በኦሎምፒክ ውድድር ታሪክ  የኢትዮጵያ ኦሎምፒክ ቡድን በሲድኒ እና ቤጂንግ አራት አራት የወርቅ ሜዳሊያዎችን በማግኘት ያስመዘገባቸው ውጤቶች አመርቂ ተብለው ተመዝግበዋል ። ዛሬ ማታ በሴቶች የ5000 ሜትር እና የ800 ሜትር የሩጫ ፉክክር ኢትዮጵያውያት አትሌቶች ለሜዳሊያ ይጠበቃሉ ። 

በ5000 ሜትር ሴቶች ፍጻሜ በዩጂን የዓለም ክብረወሰን ባለቤቷ ጉዳፍ ፀጋዬ እና ኬኒያዊቷ የሪዮ ዴ ጄኔሮ ኦሎምፒክ ክብረወሰን ባለድል ቪቪያን ጄፕኬሚ ቼሩዮት ተሳታፊ ናቸው ። እነ መዲና ኢሳ እና እጅጋየሁ ታዬም ኢትዮጵያን ወክለው ይሳተፋሉ ። የኔዘርላንዷ ሲፋን ሐሰን እና ኬንያዊቷ ኪፕዬጎ ብርቱ ተፎካካሪ እንደሚሆኑ ይጠበቃል ። በሴቶች 800 ሜትር የፍጻሜ ውድድር ኢትዮፕያ በፅጌ ዱጉማ እና ወርቅነሽ መለሠ ተወክላለች ። በርቀቱ የዓለም እና የኦሎምፒክ ክብረወሰኖች በቼኳ ጃርሚላ ክራቶችቪሎቫ 1983 ሙይንሽን እና በሩስያዊቷ ናዴዣኦሊዛሬንኮ በ198 ሞስኮ ኦሎምፒክ የተያዘ ነው ። የሁለቱም በጎርጎሪዮሱ አቆጣጠር ነው ።

ኢትዮጵያ በፓሪስ ኦሎምፒክ

ኢትዮጵያውያን አትሌቶች በብዛት የሚጠበቁበት  የፓሪስ ኦሎምፒክ  ፉክክር ቀጥሏል ። ኢትዮጵያ እስካሁን በወንዶች 10,000 ሜትር የፍጻሜ ፉክክር በበሪሁ አረጋዊ የብር ሜዳሊያ አግኝታለች ። በፍጻሜው ስለተገኘው እና ስለሌሎች ውድድሮች ከፓሪስ ወኪላችን ሃይማኖት ጥሩነህ ጋ ቃለ መጠይቅ አድርገናል ወደዚያው እንለፍ ።

በርምጃ እና ውኃ ዋና ውድድሮችም ኢትዮጵያውያን አትሌቶች ተፎካካሪ ነበሩ ። በተለይ  በአትሌት ምሥጋናው ዋቁማ  ስድስተኛ ደረጃ የተገኘበት የርምጃ ፉክክር ኢትዮጵያ ከ31 ዓመታት በኋላ ወደ ኦሎምፒክ ብቅ ያለችበት በመሆኑ ውጤቱ የሚወደስ ነው ። አትሌት ምሥጋናው ዋቁማ በቅርቡ በተኪያሄደው የአፍሪቃ አትሌቲክስ ሻምፒዮና የርምጃ ፉክክር ባለድል ነው ። በመላው አፍሪቃ ጨዋታዎች የኢትዮጵያ ክብረወሰን ባለቤት የሆነችው ሊና ዓለማየሁም በዋና ውድድር በፓሪስ ኦሎምፒክ መሳተፏም አበረታች ነው ።

ሰዎች በፓሪስ ኦሎምፒክ ወቅት በሉቭር ቆመው ሲመለከቱ
ሰዎች በፓሪስ ኦሎምፒክ ወቅት በሉቭር ቆመው ሲመለከቱምስል Natacha Pisarenko/AP/picture alliance

ዩጋንዳዊው እንደምን ከኢትዮጵያውያኑ አትሌቶች አፍትሎ ወጣ?

ኢትዮጵያውያን አትሌቶች እስከ ውድድሩ መገባደጃ ድረስ በአብዛኛው ፊታውራሪ በነበሩበት የ10,000 ሜትር የወንዶች የፍጻሜ ፉክክር በአጨራረስ ብቃት ዩጋንዳ ወርቁን ከኢትዮጵያ ፈልቅቃ ወስዳለች ። በ10,000 ሜትር የዓለም ፍጻሜ የሁለት ጊዜ ባለድሉ ጆሹዋ ቺፕቼጌ በውድድሩ መገባደጃ ልክ እንደነ ኃይሌ ገብረ ሥላሴ እና ቀነኒሳ በቀለ የአሯሯጥ ስልት በድንገት አፈትልኮ በመውጣት አሸናፊ ሁኗል ። ጆሹዋ ዓርብ ዕለት ያሸነፈውም 26 ደቂቃ ከ43.14 በመግባት ነው ።

በሪሁ አረጋዊም ጆሹዋን በመከተል ከኋላ ተፈትልኮ ከፊት ለፊቱ የነበሩትን አትሌቶች በመደረብ ለኢትዮጵያ የመጀመሪያውን የብር ሜዳሊያ አስገኝቷል ። በጆሹዋ የተበለጠው በማይክሮ ሰከንዶች ሲሆን የገባበት ሰአት 26:43.44 ነው ። ምናልባትም በሪሁ አፈትልኮ የወጣበት ሁኔታ ቀድሞ የተከወነ ቢሆን ኑሮ ከጆሹዋ ቀድሞም በማሸነፍ ክብረወሰኑ ለእሱ ይሆን ነበር ። በዚህ ረገድ አትሌቶቹ በተናጠል አሰልጣኞች መሰልጠናቸው አስተዋጽዖ ሳያደርግ አይቀርም መባሉን ሃይማኖት ጠቁማለች ።  በፓሪስ ኦሎምፒክ አትሌቶቹ ለረዥም ጊዜ ከፊት ሆነው ውድድሩን ለመምራት ኃላፊነት የወሰደው ማነው የሚለውም እያነጋገረ ነው ። በ10,000 ሜትር የፍጻሜ ፉክክር ሰለሞን ባረጋ፣ ዮሚፍ ቀጄልቻ እና በሪሁ አረጋዊ ተሳታፊ ነበሩ ።

በፓሪስ ኦሎምፒክ ድል የተቀዳጁ አትሌቶች በከፊል
በፓሪስ ኦሎምፒክ ድል የተቀዳጁ አትሌቶች በከፊልምስል Li Jing/Xinhua/IMAGO

የሜዳ ቴኒስ

የ37 ዓመቱ የሜዳ ቴኒስ የምንጊዜም ብርቱ ተፎካካሪ ኖቫክ ጄኮቪች ስፔናዊውን ሮላንድ ጋሮስ በመርታት የወርቅ ሜዳሊያ አግኝቷል ። ሠርቢያዊው የሜዳ ቴኒስ ባለድል ስፔናዊውን የ21 ዓመት ወጣት የረታው ለሁለት ጊዜ  7-6 እና 7-6 በማሸነፍ ነው ።  ኖቫክ ጄኮቪች ለሠርቢያ ሁለተኛ ወርቅ ነው ያስገኘው ። ከትናንቱ ድል በኋላ ኖቫክ ጄኮቪች በደስታ ፊቱን በነች ፎጣ ሸፍኖ ሲንሰቀሰቅ እና እጆቹ ሲንቀጠቀጡ ታይቷል ። እንደ ጎርጎሪዮስ አቆጣጠር በ2008 የቤጂንግ ኦሎምፒክ የነሐስ ሜዳሊያ ካገኘ ወዲህ በኦሎምፒክ ድል ሲያስመዘግብ ይህ የመጀመሪያው ነው ።

የ37 ዓመቱ የሜዳ ቴኒስ የምንጊዜም ብርቱ ተፎካካሪ ኖቫክ ጄኮቪች ስፔናዊውን ሮላንድ ጋሮስ በመርታት የወርቅ ሜዳሊያ አግኝቷል
የ37 ዓመቱ የሜዳ ቴኒስ የምንጊዜም ብርቱ ተፎካካሪ ኖቫክ ጄኮቪች ስፔናዊውን ሮላንድ ጋሮስ በመርታት የወርቅ ሜዳሊያ አግኝቷል ምስል Marijan Murat/dpa/picture alliance

ላለፉት ሦስት የኦሎምፒክ ውድድሮችም ማጣሪያውና ሳያልፍ በመቅረቱ ለ37 ዓመቱ አትሌት የትናንቱ የኦሎምፒክ ድል እጅግ በልዩ ሁኔታ የሚታይ ነው ።  የሐምሌ 22 ቀን፣ 2016 ዓ.ም የስፖርት ዘገባ

የውኃ ዋና

የፓሪስ ኦሎምፒክ የወንዞች ተፋሰሶችን ከብክለት ለማጽዳት በሚል 1,5 ቢሊዮን ዶላር እንደፈሰሰ ተነግሮ ነበር ። ሆኖም በትሪያትሎን ተሳታፊ የነበሩ ተወዳዳሪዎች በባክቴሪያ የተነሳ ለሕመም መዳረጋቸው አነጋጋሪ ሁኗል ። ቤልጂየም ሰኞ ዕለት አንድተፎካካሪዋ በመታመሙ ዋና፤ ሩጫ እና ብስክሌት ግልቢያን በሚያጣምረው የትሪያትሎን ፉክክር ላይ አልተወዳደረችም ። የስዊትዘርላንድ፤ የኖርዌይ የትሪያትሎን ቡድን አባላትም በባክቴሪያ መታመማቸው ያ ሁሉ ገንዘብ የተከሰከሰበት የወንዙ ጥራት ጉዳይ አነጋጋቲነቱ ቀጥሏል ።

የፓሪስ ኦሎምፒክ የወንዞች ተፋሰሶችን ከብክለት ለማጽዳት በሚል 1,5 ቢሊዮን ዶላር እንደፈሰሰ ተነግሮ ነበር
የፓሪስ ኦሎምፒክ የወንዞች ተፋሰሶችን ከብክለት ለማጽዳት በሚል 1,5 ቢሊዮን ዶላር እንደፈሰሰ ተነግሮ ነበርምስል Jasper Jacobs/Belga/dpa/picture alliance

ቡጢ

የአልጀሪያዋ ቡጢኛ የጾታ ጉዳይ በፓሪስ የኦሎምፒክ ውድድር ውዝግብ አስነስቷል ። አልጀሪያዊቷ ቡጢኛ ኢማኔ ከሊፋ እና የታይዋኗ ቡጢኛ ሊን ዩ-ቲንግ በፓሪስ ኦሎምፒክ መወዳደር ነበረባቸው አልነበረባቸው አጨቃጭቋል ። ሁለቱ ቡጢኞች ባለፈው ዓመት በተደረገው የዓለም የሴቶች የቡጢ ፍልሚያ ላይ የጾታ ብቃት መመዘኛዎችን አላሟሉም በሚል እገዳ ተጥሎባቸው ሳይወዳደሩ ቆይተው ነበር ። የዘንድሮው የፓሪስ ኦሎምፒክ የመክፈቻ ሥነ-ስርዓት ቅድመ ዝግጅት

የአልጀሪያዋ ቡጢኛ ከጣሊያናዊቷ ተጋጣሚ ጋ ያደረገችው ቡጢ የተጠናቀቀው አንድ ደቂቃም ሳይሞላ ነበር
የአልጀሪያዋ ቡጢኛ ከጣሊያናዊቷ ተጋጣሚ ጋ ያደረገችው ቡጢ የተጠናቀቀው አንድ ደቂቃም ሳይሞላ ነበርምስል Ciro Fusco/ZUMA Press/IMAGO

በተለይ በተክለ ሰውነት ገዘፍ ያለችው የአልጀሪያዋ ቡጢኛ ከጣሊያናዊቷ ተጋጣሚ ጋ ያደረገችው ቡጢ የተጠናቀቀው አንድ ደቂቃም ሳይሞላ ነበር ። ምክንያቱ ደግሞ ጣሊያናዊቷ ቡጢኛ አንጄላ ካሪኒ ያረፈባት ቡጢ ከዚህ ቀደም ከሴቶች ተወዳዳሪዎች ከሚሰነዘረው የተለየ በመሆኑ ለሕይወቴ ሰግቼ ነው ብላለች ። የዓለም ቡጢ ማኅበር ሁለቱ ቡጢኞች እንዳይወዳደሩ በሚል የከለከለውን በፓሪስ ኦሎምፒክ የኦሎምፒክ ኮሚቴ ሽሮ ተፎካካሪዎች ማድረጉ አወዛግቧል ።  

ማንተጋፍቶት ስለሺ/ ሃይማኖት ጥሩነህ

ሸዋዬ ለገሰ