1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

በሕይወትና ንብረት ጉዳት ያደረሰው የጎርፍ መጥለቅለቅ በኢትዮጵያ

ሐሙስ፣ ኅዳር 20 2016

ባለፉት ሳምንታት በኢትዮጵያ 1.5 ሚሊዮን የሚገመቱ ሰዎች በጎርፍ አደጋ ምክንያት እንደተጎዱ እና ከግማሽ ሚሊዮን በላይ ደግሞ እንደተፈናቀሉ ተገለፀ ። ሰሞነኛው የጎርፍ መጥለቅለቅ ያስከተለው ችግር በአፍሪቃ ቀንድ ለአምስት ተከታታይ ጊዜያት ከደረሰው ከባድ ድርቅ ማገገም ያልቻለውን ማኅበረሰብስቃይ ይበልጥ እያባባሰው ነው ።

https://p.dw.com/p/4Zcdq
የጎርፍ አደጋው በሶማሌ ክልል ከሰማንያ ዓመት ወዲህ ታይቶ የማይታወቅ ተብሏል
የጎርፍ አደጋው በተለይ በሶማሌ ክልል ከሰማንያ ዓመት ወዲህ ታይቶ የማይታወቅ ተብሏልምስል Somali region government communication bureo

በኢትዮጵያ 1.5 ሚሊዮን ሰዎች የጎርፍ አደጋ ደርሶባቸዋል

ባለፉት ሳምንታት በኢትዮጵያ 1.5 ሚሊዮን የሚገመቱ ሰዎች በጎርፍ አደጋ ምክንያት እንደተጎዱ እና ከግማሽ ሚሊዮን በላይ ደግሞ እንደተፈናቀሉ ተገለፀ ። ሰሞነኛው የጎርፍ መጥለቅለቅ ያስከተለው ችግር በአፍሪቃ ቀንድ ለአምስት ተከታታይ ጊዜያት ከደረሰው ከባድ ድርቅ ማገገም ያልቻለውን ማኅበረሰብስቃይ ይበልጥ እያባባሰው ነው ። የኢትዮጵያ የአደጋ ሥጋት ስራ አመራር ኮሚሽነር እና የመንግሥታቱ ድርጅት የሰብአዊ ርዳታ ማስተባባሪ የኢትዮጵያ ተወካይ በጋራ ባወጡት መግለጫ የጎርፍ አደጋው በሶማሌ ክልል የከፋ ቢሆንም በሰባት ክልሎች ውስጥ ባሉ 23 ዞኖች የተስፋፋ እና 85 ወረዳዎችን ለጉዳት ያጋለጠ ነው።

የጋራ መግለጫው የጠቀሰው የጎርፍ አደጋ መጠን

የኢትዮጵያየአደጋ ሥጋት አመራር ኮሚሽነር እና የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የሰብአዊ እርዳታ ማስተባባሪ የኢትዮጵያ ተወካይ ትናንት ምሽት በጋራ ባወጡት መግለጫ ኢትዮጵያ ውስጥ በሰባት ክልሎች የተከሰተው የጎርፍ አደጋው በሶማሌ ክልል የከፋ ቢሆን በሌሎች አካባቢዎችም ብርቱ ጉዳት እያደረሰ መሆኑን ይጠቅሳል። 

አደጋው በተከሰተባቸው አካባቢዎች የመስክ ምልከታዎች ተደርገው አፋጣኝ የሰብዓዊ እርዳታዎች እንዲደርሱ ጥረት እየተደረገ መሆኑም ተገልጿል። የኢትዮጵያ መንግስት እና አጋር ግብረሰናይ ድርጅቶች ዘርፈ ብዙ የሕይወት አድን እርዳታ ለተጎዱ ማህበረሰቦች እየሰጡ ነው የሚለው መግለጫው ያም ሆኖ ግን በአንዳንድ አካባቢዎች ባለው የአቅም ውስንነት ምክንያት እርዳታው አልፎ አልፎ የሚቀርብ እና እና በቂ አንዳልሆነ ተገልጿል። 

ለዚህ ማሳያ ሆኖ የቀረበው በሶማሌ ክልል ብቻ ከ1 ሚሊየን በላይ የሚሆኑ ሰዎች በጎርፉ ምክንያት የተጎዱ እና  500,000 ያህል አዲስ ተፈናቃዮች ቢኖሩም እርዳታ የተደረገላቸው 10 በመቶው ብቻ ናቸው ተብሏል። በዚህ ምክንያት ተጋላጭ ማህበረሰቦች ለድርብርብ ችግር መጋለጣቸው ተጠቅሷል። 

ባለፉት ሳምንታት በኢትዮጵያ 1.5 ሚሊዮን የሚገመቱ ሰዎች የጎርፍ አደጋ ደርሶባቸዋል
ባለፉት ሳምንታት በኢትዮጵያ 1.5 ሚሊዮን የሚገመቱ ሰዎች በጎርፍ አደጋ ምክንያት እንደተጎዱ እና ከግማሽ ሚሊዮን በላይ ደግሞ እንደተፈናቀሉ ተገለፀ ምስል Somali region government communication bureo

አደጋው ያስከተለው መጥለቅለቅ በአንዳንድ አካባቢዎች ከዓመታት በፊት ከታዩት የጎርፍ አደጋዎች ሁሉ የከፋው እንደሆነ ስለመግልፃቸውም የጋራ መግለጫው ይጠቅሳል። የጋራ መግለጫውን በተመለከተ ከሁለቱም አካላት ተጨማሪ ማብራሪያ ለማግኘት ጥረት ብናደርግም ምላሽ የሚሰጥ አላገኘንም። በኢትዮጵያ ሜትሪዮሎጂ ኢኒስቲቲዩት የሜትሪዮሎጂ ትንበያ እና ቅድማ ማስጠንቀቂያ ምርምር ዘርፍ ምክትል ዋና ዳይሬክተር ዶክተር አሳምነው ተሾመ ተቋማቸው ነሐሴ ላይ አድርጎት የነበረውን ቅድመ ትንበያ በተመለከተ ምላሽ ሰጥተዋል።

"በቃ ሁለተኛ የዝናብ ወቅታቸው በሆኑት በሀገራችን ሶማሌ ክልል ፣ ጉጂ ፣ ቦረና ፣ በሲዳማ ፣ እና ደቡብ ኢትዮጵያ እና በደቡብ ምእራብ የሀገራችን አካባቢዎች ላይ ከመደበኛ በላይ የሆነ የዝናብ መጠን እና ስርጭት እንደሚኖራቸው" ተተንብዮ ነበር ብለዋል።

የሜትሪዮሎጂ ቅድመ ትንበያ ምን ይል ነበር ?

ሶማሌ ክልል ሼቤሌ ዞን የጎርፍ መጥለቅለቅ ብርቱ ጉዳት

በሶማሌ፣ በደቡብ ምሥራቅ፣ በጋምቤላ፣ በኦሮሚያ፣ በአፋር እና በሲዳማ አካባቢዎች ከፍተኛ ጉዳት የደረሰባቸው ክልሎች እንደሆኑና ሶማሌ ክልል ብቻውን 80 በመቶውን የተጎጂዎችን ቁጥር እንደሚይዝ ተነግሯል። የጎርፍ አደጋው የሰው ህይወት ስለማጥፋቱ፣ ህዝብን ከቀየው ስለማፈናቀሉ እንዲሁም በሰብል፣ በከብቶች እና መሠረተ ልማቴች ላይ ውድመት ስለማድረሱ ተገልጿል። በቁጥር ባይገለጽም መኖሪያ ቤቶች፣ ሱቆች፣ ትምህርት ቤቶች እና የእርሻ መሬቶች በውኃ ተጥለቅልቀው ተጎድተዋል። 

ይህንን ተከትሌ የጤና አደጋዎች ስለመጨመራቸው ፣ በወባ ትንኝ ቁጥር መጨመር ሳቢያ የኮሌራ፣ የወባ እና መሰል ችግሮች መስፋፋትን ማስከተሉ ተገልጿል። መንግሥት የነፍስ አድን ተግባራትን የመከላከያ ኃይል ሄሊኮፕተሮችን እና ጀልባዎችን ጭምር በመጠቀም እያደረሰ መሆኑም በመግለጫው ተጠቅሷል። በኢትዮጵያ ሜትሪዮሎጂ ኢኒስቲቲዩት የሜትሪዮሎጂ ትንበያ እና ቅድማ ማስጠንቀቂያ ምርምር ዘርፍ ምክትል ዋና ዳይሬክተር ዶክተር አሳምነው ተሾመ በቀጣይ የሚኖረው የዝናብ ሁኔታም መጠኑ ከፍ ያለ እንደሚሆን የትንበያ መረጃን በማየት ጠቅሰዋል።

ለቀጣይ የዘላቂ መፍትሔ ጥሪ ስለመቅረቡ

በሰባት ክልሎች የተከሰተው የጎርፍ መጥለቅለቅ አደጋዘላቂ መፍትሔ እንዲያገኝ እና ከአስቸኳይ ድጋፍ ባለፈ የጉዳቱ ሰለባዎች ወደፊት ሊከሰቱ የሚችሉ መሰል ችግሮችን መቋቋም የሚችሉበት የሀብት ማሰባሰብ ሥራ ማከናወን የሚያሻው መሆኑ በመግለጫው ተጠቅሷል። 

በሶማሌ ክልል ብቻ በደረሰው ሰሞነኛ የጎርፍ መጥለቅለቅ አደጋ 28 ሰዎች መሞታቸው፣ እንስሳት ሀብት ላይ ፣ እርሻ እና መሰረተ ልማቶች ላይም ከፍተኛ ጉዳት መድረሱ ተገልጿል ።

 ሰለሞን ሙጬ

ማንተጋፍቶት ስለሺ

ነጋሽ መሐመድ