1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የደቡብ ሱዳን የቅርጫት ኳስ ቡድን የኦሎምፒክ ተሳትፎ

ሰኞ፣ ሐምሌ 29 2016

በደቡብ ሱዳን አሁንም አመቺ የሆኑ የማሰልጠኛ ተቋም የሉም። በዚህ የተነሳም ቡድኑ ለጨዋታው ሩዋንዳ ውስጥ መዘጋጀት ነበረበት። በቀላሉ ሲገለጽ ማንም እዚህ ይደርሳሉ ብሎ አልጠበቃቸውም፤ አሁን ደግሞ ከዓለም ምርጦች ጋር እየተደባለቁ ነው። ኦሞት የደቡብ ሱዳን ቡድን በፓሪሱ ኦሎምፒክ መሳተፉ ለመጪው ትውልድ ትልቅ ተስፋ ነው።

https://p.dw.com/p/4j8hh
Olympische Spiele 2024 | Basketball - USA v Südsudan
ምስል Gregory Shamus/Getty Images

የደቡብ ሱዳን የቅርጫት ኳስ ቡድን የኦሎምፒክ ተሳትፎ

ደቡብ ሱዳን በፓሪሱ ኦሎምፒክ ለመጀመሪያ ጊዜ በቅርጫት ኳስ ጨዋታ ተወዳደራለች። በአንድ ወቅት የአሜሪካን ብሔራዊ የቅርጫት ኳስ ማኅበር ኮከብ ተጫዋች በነበረው በሉል ዴንግ የሚመራው የቡድኑ የኦሊምፒክ ተሳትፎ ከስፖርትም በላይ ትርጉም አለው ይላል የዶቼቬለ የስፖርት ክፍል ባልደረባ ከሊል የላከው ዘገባ፤ ኂሩት መለሰ አጠናቅራዋለች። 
ለደቡብ ሱዳናዊው ኑኒ ኦሞት ፣በኦሎምፒክ የቅርጫት ኳስ መወደዳሪያ በዘርፉ ከሚታወቁት ለቦርን ጀምስ እና ስቴፍ ከሪ ጋር አንድ ቀን በተቃራኒ ቡድን ውስጥ ተሰልፈህ ልትጫወት ትችላለህ ተብሎ ቢነገረው ላያምን ይችል ነበር። ኬንያ በሚገኝ የስደተኞች መጠለያ የተወለደው የኦሞት የቅርጫት ኳስ ሞያ እንደ በአንድ ቦታ ላይ የጸና አልነበረም።  ቻይናንና ፖርቶሪኮን በመሳሰሉ ከትውልድ አካባቢው ራቅ ባሉ ሀገራት ጭምር በሚገኙ ቡድኖች ታቅፎ ቅርጫት ኳስ ይጫወት ነበር። ይሁንና በአሁኑ ዓይነት መድረክ ላይ ግን ተካፍሎ አያውቅም። «በዚህ ደረጃ ላይ መገኘት መቻል በጣም የሚገርም ልምድ ነው » ሲል ኦሞት ቡድኑ ባለፈው ረቡዕ በኦሎምፒክ በዩናያትድ ስቴትስ የቅርጫት ኳስ ቡድን ጋር ተወዳድሮ 103 ለ86 ከተሸነፈ በኋላ ተናግሮ ነበር። 

የዘንድሮው የፓሪስ ኦሎምፒክ የመክፈቻ ሥነ-ስርዓት ቅድመ ዝግጅት
«መላው ዓለም እየተከታተልህ በዓለም አቀፍ መድረክ ከሁሌዎቹ ታላላቅ ቡድኖች ጋር መግጠም እስከዛሬ ይሆናል ብዮ አስቤውም የማላውቀው ነበር። ከነዚህ ተጫዋቾች ጋር መፎካከር መቻል በራሱ ክብር ነው።» የኦሞት የቀድሞ ታሪክ የማሸነፍ እድሉ ዝቅተኛ ነው ተብሎ ይታሰብ የነበረውን «ብራይት ስታርስ» የተባለውን የደቡብ ሱዳንን ቡድን ተፈጥሮ ይገልጻል፤ ስፖርቱን ዘግይቶ የተቀላቀለው ቡድኑ በአንድ ወቅት ጥሬና ያልተመጣጠነ ችሎታ የነበረው ፣ ከዚያ በኋላ ግን መቀመጫቸውን በተለያየ የዓለም ክፍል ያደረጉ የተለያዩ ተጫዋቾችን ያቀፈ ቡድን ነው።
ሳይጠበቅ ለኦሎምፒክ የቅርጫት ኳስ ውድድር ያለፈው ቡድኑ የመጀመሪያውን ይፋ ዓለም አቀፍ ውድድር  ያካሄደው ከ7 ዓመት በፊት ነበር። በደቡብ ሱዳን አሁንም አመቺ የሆኑ የማሰልጠኛ ተቋም የሉም። በዚህ የተነሳም ቡድኑ ለጨዋታው ሩዋንዳ ውስጥ መዘጋጀት ነበረበት። በቀላሉ ሲገለጽ ማንም እዚህ ይደርሳሉ ብሎ አልጠበቃቸውም፤ አሁን ደግሞ ከዓለም ምርጦች ጋር እየተደባለቁ ነው። ኦሞት የደቡብ ሱዳን ቡድን በፓሪሱ ኦሎምፒክ መሳተፉ ለመጪው ትውልድ ትልቅ ተስፋ ነው። 

በፓሪስ ኦሎምፒክ የደቡብ ሱዳኑ ካርሊክ ጆንስ እና ተፎካካሪው የዩናይትድ ስቴትሱ የቅርጫት ኳስ ተጫዋች ዴቪን ቡከር
በፓሪስ ኦሎምፒክ የደቡብ ሱዳኑ ካርሊክ ጆንስ እና ተፎካካሪው የዩናይትድ ስቴትሱ የቅርጫት ኳስ ተጫዋች ዴቪን ቡከርምስል Sameer Al-Doumy/AFP/Getty Images


« የሚያውቁን ሰዎች የሌለን ሀገር ነን። አሁን በግልጽ ከኦሎምፒክ በኋላ ደግሞ ሰዎች እኛን ያውቁናል። ይህ ለመጪው ትውልድ በር ከፋች ነው የሚሆነው።»  
የደቡብ ሱዳን የቅርጫት ኳስ ቡድን ከዩናይትድ ስቴትስ ቡድን ጋር በገጠመበት በሊሉ መድረክ ተጫዋቾቹ የአድናቂዎቻቸው ድጋፍ ባይለያቸውም በርግጥ የዩናይትድ ስቴትስ ደጋፊዎች ግን በቁጥር በልጠዋቸዋል።  ዶቼቬለ ካነጋገራቸውe አብዛኛዎቹ የደቡብ ሱዳን ዳያስፖራ በብዛት ከሚገኝብቻው አገራት አንዱ ከሆነው ከአውስትራልያ ድረስ የመጡ ነበሩ። ከመካከላቸው አንዱ እንደተናገረው ፣ይህ ለደቡብ ሱዳናውያን ትልቅ ትርጉም አለው። «ይህ ለሀገራችን ለደቡብ ሱዳንና ለዓለማችን ህዝብ ታሪካዊ ወቅት ነው። የመጣነው በጦርነት ከተመሰቃቀለች ሀገር ነው። ትንሽ ሰላም ፣በጎ የሆነ ነገር ማግኘት ለኛ ብዙ ማለት ነው።»ሌላው ከአውስትራልያ የመጣው ዶም አብየም  ቅርጫት ኳስ ሱዳናውያንን አንድ አድርጓል ይላል።
«የማንደሰትባቸው ለሀገራችን ትክክለኛ ያልሆኑ ብዙ ነገሮች አሉ። ይህ ግን ተስፋ ሰጥቶናል።» 

መሐመድ ሐምዳን ዳጋሎ ራሳቸውን ለሱዳን መሪነት እያዘጋጁ ወይስ...?
ከቤልጅየም ከባለቤታቸውና ከአራት ልጆቻቸው ጋር ለመጡት እንደ ሱዛን ውሮ ለመሳሰሉት ምንም እንኳን በአካል ተገኝተው ውድድሩን መከታተል ባይችሉም፣ በዚህ አጋጣሚ የታሪክ ምስክር መሆን ሊያመልጥ የማይገባ ጉዳይ ነው ።  «ቲኬቶች የሉንም ፤ተሽጦ አልቆ ነበር፤ይህን ማየት ፈልገን ነበር። ለደቡብ ሱዳን ብቻ አይደለም። ለመላው አፍሪቃ ጭምር እንጂ ።ይህ ለኛ ትልቅ ነገር ነው።»

የደቡብ ሱዳንና የዩናይትድ ስቴትስ  ቅርጫት ኳስ የኦሎምፒክ ጨዋታ
የደቡብ ሱዳንና የዩናይትድ ስቴትስ ቅርጫት ኳስ የኦሎምፒክ ጨዋታ ምስል Thomas Coex/AFP/Getty Images

ደቡብ ሱዳን ከሱዳን ጋር ለአሥርት ዓመታት ከተካሄደ ግጭት በኋላ የዛሬ 13 ዓመት በጎርጎሮሳዊው 2011 ነጻነቷን ያወጀች የዓለም ወጣቷ ሀገር ናት። ይሁን ሀገሪቱ ያገኘችው ነጻነት ህዝቧ በቅጡ ሳያጣጥም  ከሁለት ዓመት በኋላ በጎርጎሮሳዊው 2013 በሀገሪቱ ከባድ የርስ በርስ ጦርነት ፈነዳ ።ምንም እንኳን በ2018 የሰላም ስምምነት ላይ ቢደረስም በተለያu ጎሳዎች መካከል የሚካሄደው ግጭት አልቆመም ይህም ድሀነትና ረሀብ በተስፋፋባት በሀገሪቱ አለመረጋጋትን አስከትሏል። ለፓሪስ ኦሎምፒክ ተፎካካሪ ኢትዮጵያውያን አትሌቶች ደማቅ አቀባበል
ካርሊክ ጆንስ የተባለው ተጫዋች ቡድኑ በፓሪስ ኦሎምፒክ ያስገኘውን ውጤት ለደቡብ ሱዳናውያን ተስፋ ሰጭ ብሎታል። «በብዙዎች ፊቶች ላይ ፈገግታ እንዲኖር እናደርጋለን፤ ለበርካታ ወጣት ልጆች እና ቤተሰቦቻቸው ተስፋ እንሰጣለን፤ለኔ ትልቁ ነገር  የማይቻል ነገር እንደሌለ ለሁሉም ለማሳወቅ መሞከር ነው።»
የደቡብ ሱዳን የቅርጫት ኳስ ቡድንን እዚህ ለመድረስ የበቃው የቡድኑ ባለውለታ የሁለት ጊዜ የዩናይትድ ስቴትስ የቅርጫት ኳስ ዋና ኮከብ ተጫዋች የነበረው ሉል ዴንግ ነው። ዴንግ ደቡብ ሱዳን ቢወለድም ያደገው በኣመዛኙ ብሪታንያ ነው። ዴን የራሱን ገንዘብ ለቡድኑ እድገት ወጩ አድርጓል። በአሁኑ ጊዜም የቡድኑ ረዳት አሰልጣኝ ነው።ከዚህ በተጨማሪም የደቡብ ሱዳን የቅርጫት ኳስ ፌደሬሽን ፕሬዝዳንትም ነው። የቡድኑ ተጫዋቾች ዴንግ በመሪነትና ለቡድኑ በሚሰጣቸው የተለያዩ ድጋፎች ያከብሩታል፣ ያደንቁታል ፣ያመሰግኑታልም።

ኂሩት መለሰ

አዜብ ታደሰ