1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የወባ በሽታ ወረርሽኝ ስርጭት በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል

ማክሰኞ፣ ሐምሌ 9 2016

በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ወባ በወረርሽኝ መልክ መስፋፋቱን የክልሉ ጤና ጽ/ቤት ዐሳውቋል፡፡ በክልሉ 22 ውስጥ ወረዳዎች በከፍተኛ ሁኔታ መስፋፋቱን የክልሉ ጤና ቢሮ የመርሀ ግብር ዘርፍ ምክትል ኃላፊ አቶ አብዱልሙኒየም አልበሽር ለዶቼቨለ ተናግረዋል፡፡

https://p.dw.com/p/4iNUW
የወባ በሽታ መከላከያ ክትባት። ፎቶ፦ ከማኅደር
የወባ በሽታ መከላከያ ክትባት። ፎቶ፦ ከማኅደርምስል Desire Danga Essigue/REUTERS

የወባ በሽታ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል 22 ወረዳዎች ውስጥ ተስፋፍቷል

በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ወባ በወረርሽኝ መልክ መስፋፋቱን የክልሉ ጤና ጽ/ቤት ዐሳውቋል፡፡ በክልሉ 22 ውስጥ ወረዳዎች በከፍተኛ ሁኔታ መስፋፋቱን የክልሉ ጤና ቢሮ የመርሀ ግብር ዘርፍ ምክትል ኃላፊ አቶ አብዱልሙኒየም አልበሽር ለዶቼቨለ ተናግረዋል፡፡ ከሰኔ 24 ቀን፣ 2016 ዓ.ም ወዲህ በክልሉ ከተመረመሩት 22ሺ188 ሰዎች መካከል በ10ሺ 526 ሰዎች ላይ ወባ መገኘቱን 5 ሰዎች ደግሞ ሕይወት ማለፉን ኃላፊው ጠቁመዋል፡፡ በክልሉ መተከል ዞን ድባጢ እና ቡሌን ወረዳዎች ውስጥ የወባ ስርጭት በስፋት መታየቱንና 3 ህጻናት ሕይወት ማለፉን ነዋሪዎች ተናግረዋል፡፡

የወባ በሽታ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል 22 ወረዳዎች ውስጥ ተስፋፍቷል

የወባ የበሽታ ስርጭት በዘንድሮ ዓመት ከፍተኛ በሆነ መልኩ ስርጭቱ በክልሉ መስተዋሉን የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ጉሙዝ ጤና ቢሮ አስታውቋል፡፡ በመተከል ዞን ድባጤ ወረዳ ውስጥ በርበር እና ሶምቦስሬና ቆርቃ በሚባሉ አካባቢዎችም ከዚህ ቀደም ባልተለመደ ሁኔታ ወባ በሽታ ስርጭት መጨመሩን ያነገጋርናቸው ነዋሪዎች ተናግረዋል፡፡ በዚህ አካባቢ ከአንድ በተሰብ ቢያንስ አንድ ሰው በወባ እንደሚያዝ የተናገሩት ያነገጋርናቸው ነዋሪዎች በወባ በሽታ ሶስት ህጻናት ሕይወት ማለፉን ገልጸዋል፡፡ የጸረ ወባ ከሚካኤል ሪጭት ከሁለት ሳምንት በፊት መደረጉን የተናገሩት ነዋሪዎች የበሽታው ስርጭት ግን መቀነስ አለመቻሉን ጠቁመዋል፡፡

የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ጤና ቢሮ በበኩሉ ወባ ስርጭትን ለመከላከል ከጤና ጥበቃ ሚንስቴር ጋር በመሆን ጥረት እያደረገ እንደሚገኝ ገልጸዋል፡፡ በክልሉ ጤና ቢሮ የመርሀ ግብር ምክትል ዘርፍ ኃላፊ የሆኑት አቶ አብዱልሙኒየም አልበሽር እንደተናገሩት ካለፈው ሰኔ ወር መጨረሻ አንስቶ ከ10ሺ በላይ ሰዎች በወባ መያዛቸው መረጋገጡን ተናግረዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት በክልሉ ሁሉም አካባቢዎች ወባ እንደሚገኝ በመግለጽ የክልሉ ጤና ቢሮ አጎበር በሁሉም አካባቢዎች ማሰራጨቱን አክለዋል፡፡

ፎቶ ከማኅደር፦ የወባ ስርጭትን ለመከላከል ጥቅም ላይ ከሚውሉ ስልቶች አንዱ
ፎቶ ከማኅደር፦ የወባ ስርጭትን ለመከላከል ጥቅም ላይ ከሚውሉ ስልቶች አንዱምስል Naveen Sharma/SOPA/ZUMA/picture alliance

የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ከኦሮሚያና እና አማራ ክልል ጋር የሚያገናኙ መንገዶች ጸጥታ ችግር ሳቢያ ዝግ በመሆናቸው በክልሉ ወባ ስርጭትን ለመከላከልበሚሠሩ ስራዎች ላይ ተጽህኖ መፍጠሩን ኃላፊው ተናግረዋል፡፡ በዚሁ ምክንያት በቂ መድኃኒትና ልዩ ልዩ ቁሳቀሶችን ወደ ክልሉ በሚፈለገው መልኩ እየገባ እንዳልሆነ አብራርተዋል፡፡ ከወባ ስርጭት መከላከል በተጨማሪም በሌሎች ጤና ጥበቃ ስራዎች ላይ የመንገድ መዘጋትና ጸጥታ ችግር ከፍተኛ ተጽህኖ ማሳደሩን ገልጸዋል፡፡

በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ባለፉት 10 ወራት ወደ ጤና ተቋማት በመምጣት ከተመረመሩት 751ሺ በላይ ሰዎች መካከል 289ሺ 035 ሰዎች በወባ በሽታ መያዛቸው መረጋጡን የክልሉ ጤና ቢሮ ጠቁመዋል፡፡ ከፍተኛ የወባ ስርጭት በታየባቸው የአማራ፣ኦሮሚያ፣ቤኒሻንጉል ጉሙዝና ሌሎችም የሐገሪቱ አካባቢዎች ጤና ሚኒስቴር አስቸኳይ የህክምና ድጋፍ እያደረገ እንደሚገኝ ማሳወቁን ሀምሌ 6/2016 የሀገር ውስጥ መገናኛ ብዙሐን ዘግበዋል፡፡

ነጋሳ ደሳለኝ

ማንተጋፍቶት ስለሺ

ታምራት ዲንሳ