ከአፍሪቃ የዘር ሐረግ የሚመዘዙት ድንቅ የአውሮጳ ተጨዋቾች
ቅዳሜ፣ ሐምሌ 6 2016«ዩሮ 2024፦ አፍሪቃ የእግር ኳስ ጠቢባን ሲራቀቁ ዕያየች ነው» ይለናል በካይ ኔቤ የቀረበው ዘገባ ። እንደሚከተለው ለአድማጭ በሚመች መልኩ አሰናድተነዋል ።
በእሁዱ የዩሮ 2024 የፍጻሜ ጨዋታ ስፔን እንግሊዝን ትገጥማለች ። ከአፍሪቃ የዘር ሐረግ የሚመዘዙት እንደ ላሚን ያማል፣ ኒኮ ዊሊያምስ እና ቡካዮ ሳካ ያሉ ተጫዋቾችም ውድድሩን አድምቀዋል ። በእሁዱ የፍጻሜ ፍልሚያ የትኛውም ቡድን የአሸናፊነት ክብሩን ይቀዳጅ ላሚን ያማል እና ኒኮ ዊሊያምስ ግን ማንነታቸውን ከወዲሁ አስመስክረዋል ።
ሁለቱ የስፔን ብሔራዊ የእግር ኳስ ቡድን የክንፍ ተጨዋቾች በዩሮ 2024 ግጥሚያ እንዲያቆሟቸው የተመደቡ የየትኛውም ሀገር ተከላካዮች ፈርዶባቸዋል ማለት ይቻላል ። የፍጻሜ ግጥሚያው እስከተደረገበት ቀን ከ16ኛ ዓመቱ ያልዘለለው ላሚን ያማል ከኢኳቶሪያል ጊኒ እና ሞሮኮ ወላጆች ነው የተወለደው ። ይህ ድንቅ የኳስ ጥበበኛ 17ኛ ዓመቱ የሚሞላው በአውሮጳ ፍጻሜ ጨዋታ ማግስት ነው ። ይህ የባርሴሎና ቡድን አዳጊ ተጨዋች በዩሮ ታሪክ ትንሹ ተሰላፊ ነው ። ያም ብቻ አይደለም በግማሽ ፍጻሜው ፈረንሳይ ላይ ድንቅ ግብ በማስቆጠርም በዩሮ የእግር ኳስ ታሪክ ትንሹ ግብ አስቆጣሪ ሆኖ ተመዝግቧል ።
«ያማል ገና ብሩኅ ተስፋ ያለው አፍላ ጮርቃ ተጨዋች ነው ። ዛሬ ግብ ያስቆጥራል ብዬ እገምታለሁ ።»
ስፔናዊው የላሚን ያማል አድናቂ ላሚን ግብ ባስገባበት ቀን ከጨዋታው በፊት የሰጠው ግምት ነው ። በእለቱ በእርግጥም የስፔኑ ደጋፊ ግምት ሠርቷል ። ያማል ስፔንን ለፍጻሜ ያበቃትን ድንቅ ግብ ከመረብ አሳርፏል ። ሌላኛው የስፔን ድንቅ ኒኮ ዊሊያምስ የተወለደው አሰቃቂውን የሰሐራ በረሃ አቋርጠው ስፔን አዲስ ሕይወት ከጀመሩ ጋናውያን ቤተሰቦች ነው ። ኒኮ በአትሌቲኮ ቢልባዎ ቡድን በስፔን ላሊጋ ከታላቅ ወንድሙ ኢናኪ ዊሊያምስ ጋ በመሰለፍ ቡድኑ የነበረበትን ዋንጫ የማንሳት ድርቀት ባለፈው የጨዋታ ዘመን ወደ ታሪክነት ቀይረውታል ። ኢናኪ ዊሊያምስ እንደ ጎርጎሪዮስ አቆጣጠር በ2022 ለጥቋቁር ከዋክብቱ የጋና ብሔራዊ ቡድን በመሰለፍ ብቃቱን አስመስክሯል ።
ታናሽ ወንድሙ ዘንድሮ ዋንጫ ለማንሳት ጫፍ ደርሷል ። በእርግጥ የስፔን ቡድን ጨዋታ ውጤት በላሚን ያማል እና ኒኮ ዊሊያምስ ብቻ የሚገደብ አይደለም ። ግን ደግሞ እነ ያማልም ሆኑ ሌሎች ከአፍሪቃ ሐረግ ከሚመዘዝ ቤተሰብ የሚወለዱ የዩሮ 24 ተሳታፊ ሃገራት ተጨዋቾች ለአውሮጳው እግር ኳስ ልዩ ቅመም ናቸው ። ይህን ያሉት ጃኮብ ሙሌ ናቸው፤ የኬንያ ብሔራዊ ቡድን የቀድሞ አሰልጣኝ ።
«ከአፍሪቃ የዘር ሐረጋቸው የሚመዘዝ ተጨዋቾች ምናልባትም በርካታ የአውሮጳ ተጨዋቾች ያጡት ነገር አላቸው ። ምክንያቱም አፍሪቃውያን ተጨዋቾች ኳስ ሲጫወቱ የደነሱ ያህል ነው ። መድረክ ላይ የወጡ ነው የሚመስለው ። ለጨዋታው የሚሰጡት የተለየ ውበት አለ ። ማለቴ ጄጄ ኦካቻን ተመልከቱ፤ እንደ ኬሊያን እምባፔ ያሉ ተጨዋቾችን እዩ፤ ቡካዮ ሳካን ሳይቀር ተመልከቱ፤ ለጨዋታው የሚሰጡት የተለየ ቅመም አለ ። ያን የተወገደ ጊዜ ጨዋታው በሙሉ ወዝ አልባ ነው የሚሆነው ባይ ነኝ ።»
እነዚህ እና ሌሎች ከአፍሪቃውያን ቤተሰቦች የሚወለዱ ተጨዋቾች በውድድሩ ላይ መድመቃቸው በአፍሪቃ ልዩ ትኩረትን ስቧል ።
«በአሁኑ ወቅት ዩሮ 2024 ጀርመን ውስጥ እየተካሄደ ነው ። ፍላጎት ከፍተኛ ነው ። አብዛኞቹ የሬዲዮ ጣቢያዎች የቀጥታ ሥርጭት ሽፋን እየሰጡ ነው ። ሰዉ በሙሉ በዩሮ ወቅት ቴሌቪዥን ላይ ተለጥፎ ነው የሚውለው ።»
በአውሮጳ ምድር ገንነው የወጡት ከአፍሪቃ ዘራቸው የሚመዘዝ ተጨዋቾች በእየ ፊናቸው ቡድናቸውን ለልዩ ክብር አብቅተዋል ። ያም ብቻ አይደለም ። የእነዚህ ተጨዋቾች ስኬት ለብዙዎች በአፍሪቃ ምድር ላሉ አዳጊዎችም ራሳቸውን ወደፊት አሻግረው የሚመለከቱበት አንዳች ተምሳሌት በመፍጠር አርአያነቱ እጅግ ላቅ ያለ ነው ።
ማንተጋፍቶት ስለሺ
ፀሐይ ጫኔ