1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የነሐሴ 27 ቀን፣ 2016 ዓ.ም የስፖርት ዘገባ

ሰኞ፣ ነሐሴ 27 2016

ኢትዮጵያ በፓሪስ ፓራሊምፒክ በወርቅ ተሽቆጥቁጣለች ። ማንቸስተር ዩናይትድ በገዛ ሜዳው ኦልድ ትራፎርድ ጉድ ሆኗል ። እስካሁን አንድም ግብ ባልተቆጠረበት ሊቨርፑል የ3 ለዜሮ ብርቱ ቅጣት ደርሶበታል ። ቸልሲ እናs አርሰናል ነጥብ ጥለዋል ። ማንቸስተር ሲቲ በአሸናፊነት ግስጋሴው ገፍቶበታል ።

https://p.dw.com/p/4kC99
Tigest ist der erste äthiopische Paralympiker, der eine Goldmedaille gewann
ምስል Himanot Tirune/DW

ሣምንታዊ የስፖርት ዘገባ

ማንቸስተር ዩናይትድ በገዛ ሜዳው ኦልድ ትራፎርድ ጉድ ሆኗል ። እስካሁን አንድም ግብ ባልተቆጠረበት ሊቨርፑል የ3 ለዜሮ ብርቱ ቅጣት ደርሶበታል ። ቸልሲ ትናንት አርሰናል ቅዳሜ ዕለት ነጥብ ጥለዋል ። ማንቸስተር ሲቲ በአሸናፊነት ግስጋሴው ገፍቶበታል ። እስካሁን በተደረጉ ሦስት ጨዋታዎች ከሊቨርፑል ጋ በእኩል ነጥብ እና ተመሳሳይ የተጣራ ግብ ሆኖም ብዙ በማግባት ቀዳሚውን ስፍራ ይዟል ባለፉት ሦስት ጨዋታዎች ሁለት ግቦች ተቆጥሮበታል ። በጀርመን ቡንደስሊጋ ከታችኛው ዲቪዚዮን ያደገው ሐይደንሀይም በጨዋታ ዘመኑ ሁለተኛ ዙር ውድድር ቢሆንም ባዬርን ሙይንሽንን በልጦ በደረጃ ሠንጠረዡ አንደኛ ላይ ሰፍሯል ። የአትሌቲክስ እና ሌሎች ስፖርታዊ መረጃዎችን አካተናል

አትሌቲክስ

ኢትዮጵያ በዘንድሮ የፓሪስ 2024 ፓራሊምፒክስ ፉክክር ተደጋጋሚ ድሎችን እያስገኘች ነው ። ስታድ ደ ፍራንስ ውስጥ ዛሬ ጠዋት በነበረው የ1500ሜትር T11 (ሙሉ ለሙሉ ማየት በተሳናቸው) ፉክክር ኢትዮጵያዊቷ አትሌት ያየሽ ጌጤ የራሷን ክብረወሰን በመስበር ጭምር የወርቅ ሜዳሊያ አግኝታለች ። ያየሽ ከረዳቷ ክንዱ ሲሳይ ጋር አብራ በመሮጥ ባደረገችው ፉክክር ለድል የበቃችው ውድድሩን በ4 ነጥብ አምስት ሰከንድ በማሻሻል ጭምር ነው ።

ያየሽ ከሁለት ወር በፊት ኮቤ ውስጥ በነበረው የዓለም ፓራሊምፒክስ አትሌቲክስ ፍጻሜ ፉክክርም ክብረወስን በመስበር ጭምር ነበር ያሸነፈችው ። ያየሽ በኦሎምፒክ ድል ስታስመዘግብም የመጀመሪያዋ ነው ።

ኢትዮጵያ በዘንድሮ ውድድር በሁለት ሴቶች ለመጀመሪያ ጊዜ ተካፍይ ሆና በሁለቱም ሴት አትሌቶች የወርቅ ሜዳሊያ አስመዝግባለች ። ውድድሩን ያጠናቀቀችበር 4:27.68 አዲስ ክብረወሰን ሆኖ ተመዝግቧል ። የቻይና ሯጭ ሻንሻን 4:32.82 በመሮጥ የብር ሜዳሊያ አግኝታለች ። ደቡብ አፍሪቃዊቷ ደሎውዛኔ ኮዬትዜ የነሐስ ሜዳሊያ ማግኘት ችላለች ።

ዛሬ በተመሳሳይ በተካሄደ የወንዶች የ1500ሜትር T11 ማለትም የማጣሪያ ውድድር ይታያል ሁለተኛ በመውጣት ነገ ለሚደረገው የፍጻሜ ውድድር አላፊ መሆኑን አረጋግጧል ። 

በሌላ  የፓሪስ 2024 ፓራሊምፒክስ የሴቶች 1500 ሜትር የT13 (በጭላንጭል የሚያዩ) የሩጫ ፉክክር ኢትዮጵያዊቷ አትሌት ትእግስት ገዛኻኝ ትናንት አሸናፊ በመሆን የመጀመሪያውን የወርቅ ሜዳሊያ አስገኝታለች ። 80 ሺህ ታዳሚዎች በተገኙበት የፍጻሜው ውድድር አትሌት ትእግስት አስደማሚ ድል ስታስመዘግብ በስፍራው የነበረችው የፓሪስ ወኪላችን ሃይማኖት ጥሩነህ ቀጣዩን ዘገባ ልካልናለች ።

በፓሪስ ፓራሊፒክስ ኢትዮፕያ ተደጋጋሚ ድል ቀንቷታል
በፓሪስ ፓራሊፒክስ ኢትዮፕያ ተደጋጋሚ ድል ቀንቷታል ምስል Himanot Tirune/DW

በፔሩ ሊማ በተካሄደው የዓለም ከ20 ዓመት በታች የአትሌቲክስ ፉክክር የኢትዮጵያ ቡድን ለመጀመሪያ ጊዜ ከዓለም ሁለተኛ ደረጃን በመያዝ ደማቅ ታሪክ አስመዝግቧል ።  ካለፈው ሳምንት ማክሰኞ ነሐሴ 21 ቀን፣ እስከ ቅዳሜ ነሐሴ 25 ቀን፣ 2016 ዓ.ም በነበረው ፉክክር የኢትዮጵያ ቡድን ስድስት የወርቅ፤ ሁለት የብር እና ሁለት የነሐስ ሜዳሊያዎችን በመሰብሰብ ፉክክሩን በከፍተኛ ድል አጠናቋል ።

ኢትዮጵያን የቀደመችው ዩናይትድ ስቴትስ ስምንት የወርቅ፤ አራት የብር እንዲሁም አራት የነሐስ ሜዳሊያ አግኝታለች ። ቻይና በአራት ወርቅ፤ በአራት ብር እና በሦስት ነሐስ ሦስተና ደረጃ ይዛለች ። ተመሳሳይ አራት የወርቅ እና አንድ የነሐስ ሜዳሊያ ያገኘችው ጃማይካ አራተኛ ደረጃ ይዛ አጠናቃለች። ኬንያ በሦስት ወርቅ፤ በሦስት የብር እና በአንድ የነሐስ ሜዳሊያ አምስተኛ ሆናለች ። ጀርመን በአንድ ወርቅ እና በሁለት የነሐስ ሜዳሊያዎች ብቻ ተወስኖ በሜዳሊያ ሰንጠረዡ 14ኛ ደረጃ ላይ ሰፍሯል ።  ከስሩ ፈረንሳይ እና ኖርዌይ በአንድ የወርቅ ሜዳሊያ  15ኛ ደረጃ አግኝተዋል ። 

እግር ኳስ

የኢትዮጵያ ብሔራዊ  የእግር ኳስ ቡድን ለአፍሪቃ ዋንጫ ማጣርያ  ባለፈው ሳምንት ባደረጋቸው ጨዋታዎች ከሱዳን ብሔራዊ ቡድን ጋር በአበበ ቢቂላ ስታዲየም 2-0 አሸንፏል ። ግቦቹን ቢንያም ዐይተን እና ቸርነት ጉግሳ አስቆጥረዋል ።  ብሔራዊ ቡድኑ ቀደም ሲል በተመሳሳይ የልምምድ ጨዋታ ከድሬዳዋ ከተማ ቡድንን ጋ በማድረግ 4-0 አሸንፏል ።

የኢትዮጵያ ብሔራዊ የእግር ኳስ ቡድን በ2025 የአፍሪቃካ ዋንጫ ማጣርያ ከታንዛንያ እና ኮንጎ ዲ.ሪ ጋር ለሚያደርጋቸው ጨዋታዎች ዛሬ ወደ ታንዛኒያ ማቅናቱን የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ዐሳውቋል ።

የፓራሊምፒክስ ውድድር የሚካሄድበት ስፍራ ። ፓሪስ ፈረንሳይ
የፓራሊምፒክስ ውድድር የሚካሄድበት ስፍራ ። ፓሪስ ፈረንሳይምስል DIMITAR DILKOFF/AFP

ፕሬሚየር ሊግ

ማንቸስተር ዩናይትድ ትናንት በሜዳው ኦልድ ትራፎርድ ስታዲየም የ3 ለ 0 ሽንፈት አስተናግዷል ። በትናንቱ ግጥሚያ ማንቸስተርን ጉድ ያደረገው ሊቨርፑል ነው ። የምሽቱ ድንቅ ተጨዋች የተባለው ኮሎምቢያዊው ሉዊስ ዲያዝ በ35ኛው እና 42ኛው ደቂቃዎች ላይ ሁለት ግቦችን አስቆጥሯል ። ኳሶችን በግሩም ሁኔታ ሲያመቻች የነበረው ግብጻዊው ሞሐመድ ሣላኅ በበኩሉ 56ኛው ደቂቃ ላይ ሦስተኛዋን ኳስ ከመረብ አሳርፏል ። ከጨዋታው በኋላ በባዶ እግሩ ከመልበሻ ክፍል ወጥቶ ባደረገው አጠር ያለ ቃለ መጠይቅ በውድድር ዓመቱ መጨረሻ ከሊቨርፑል ጋ እንደሚለያይ ጠቁሟል ። ከሊቨርፑል ጋ ያደረገው የሦስት ዓመት ውልም በቀጣዩ የጎርጎሪዮሱ ዓመት በጋ ወራት ውስጥ ይጠናቀቃል ።  ውሉን ስለማራዘምም እስካሁን ያናገረው ሰው እንደሌለ ትናንት ገልጧል ።

ቸልሲ በሜዳው ስታምፎርድ ብሪጅ ከክሪስታል ፓላስ 1:1 ሲወጣ፤ ኒውካስል ቶትንሀምን 2 ለ 1 አሸንፎ ሸኝቷል ።  ቅዳሜ ዕለት በነበሩ ግጥሚያዎች፦ ኢፕስዊች ከፉልሀም ጋ አንድ እኩል ወጥቶ ነጥብ ተጋርቷል ። ላይስተር ሲቲ በአስቶን ቪላ የ2 ለ1 ሽንፈት አስተናግዷል ። ኤቨርተን በሜዳው ጉዲሰን ፓርክ ስታዲየም በቦርመስ የ3 ለ2 ሽንፈት ደርሶበታል ። ብሬንትፎርድ ሳውዝሐምፕተንን 3 ለ1 አሸንፏል ። ኖቲንግሀም ፎረስት ከዎልቨርሐምፕተን እንዲሁም 49ኛ ደቂቃ ላይ ዴክላን ራይስ በቀይ ካርድ ከሜዳ የተሰናበተበት አርሰናል ከብራይተን ጋ አንድ እኩል ተለያይተዋል ።

በጀርመናዊው አማካይ ካይ ሐቫርትስ ቀዳሚውን ግብ ያስቆጠረው በሜዳው ኤሚሬትስ ስታዲየም የተጫወተው አርሰናል ነበር ። ከረፍት መልስ ጃዎ ፔድሮ ብራይተንን አቻ አድርጎ ነጥብ ለመጋራት ያስቻለውን ኳስ ከመረብ አሳርፏል ። በሁለት ቢጫ ካርድ ከሜዳ የተሰናበተው ዴክላን ራይስ ጉዳይ አጨቃጭቋል ። ጨዋታው ዳግም እንዳይጀምር ሆን ብሎ ለቅጣት የተመቻቸችውን ኳስ ጨረፍ አድርጎ በመምታት አዘግይቷል በሚል ነበር ዳኛው በሁለተኛ ቢጫ ቀይ ካርድ ያስወጡት ። በርካታ ደጋፊዎች ሆን ብሎ ቅጣት ምቱን አላጨናገፈም ሲሉ ተከራክረዋል ።

ኧርሊንግ ኦላንድ ሦሰት ኳሶችን ከመረብ አሳርፎ ሔትሪክ በሠራበት ግጠሚያ ማንቸስተር ሲቲ ዌስትሐም ዩናይትድን በሜዳው ኦሎምፒያስታዲዮን 3 ለ1 አሸንፏል ። ማንቸስተር ሲቲ በመጀመሪያው አጋማሽ አንድ እኩል በሆነበት ወቅት ምናልባትም 3 አለያም 4 ለዜሮ መምራትም ይችል ነበር ። የባከነው ደቂቃም ተጨምሮ ጨዋታው ሊጠናቀቅ ሲልም የግብ ቀበኛው ኧርሊንግ ኦላንድ አራተኛ ግቡ ሊሆን የሚችል ኳስ በግብ ጠባቂው ተጨናግጦበታል ። እስካሁን 7 ኳሶችን ከመረብ በማሳረፍ በብቸኝነት እየገሰገሰ ነው ። የሊቨርፑል አጥቂ ሉዊስ ዲያዝ እና የብሬንትፎርድ አማካይ ብሪያን ምቤውሞ ሦስት ግብ አላቸው ።

የኤርቤ ላይፕትሲሽ  የስሎቬኒያ አማካይ ኬቪን ካምፕል
የኤርቤ ላይፕትሲሽ የስሎቬኒያ አማካይ ኬቪን ካምፕልምስል UWE KRAFT/AFP via Getty Images

ሊቨርፑል እና ማንቸስተር ሲቲ በሦስት ግጥሚያ ዘጠኝ ነጥብ ሰብስበው አንደኛ እና ሁለተኛ ናቸው ። ሁለቱ ቡድኖች ሰባት ተመሳሳይ የተጣራ ግብ ክፍያ ሲኖራቸው፥ ሊቨርፑል እስካሁን የግብ ክልሉ አልተደፈረም ። ብራይተን፤ አርሰናል እና ኒውካስል በሦስት ጨዋታዎች እስካሁን ሰባት ሰባት ነጥብ ሰብስበው ከሦስተኛ እስከ አምስተኛ ደረጃ ተደርድረዋል ።   የሐምሌ 22 ቀን፣ 2016 ዓ.ም የስፖርት ዘገባ

ቡንደስሊጋ

ከታችኛው ዲቪዚዮን ያደገው ሐይደንሀይም ገና ከሁለት ጨዋታዎች በኋላም ቢሆን ምሥጋና ለባዬርን ሙይንሽን እያለ በደረጃ ሰንጠረዡ አናት ላይ ሰፍሯል ። ከባዬርን ሙይንሽን በውሰት ለሐይደንሀይም የሚጫወተው የ18 ዓመቱ ፖል ቫነር 9ኛ ደቂቃ ላይ በቀዳሚነት ያስቆጠራት ተደምራ አውግስቡርግን 4 ለ0 ጉድ አድርጓል ።

ሐይደንሀይም፤ ባዬርን ሙይንሽን እና ኤር ቤ ላይፕትሲሽ እያንዳንዳቸው በስድስት ነጥብ ቀዳሚው ስፍራ ላይ ናቸው ። ዶርትሙንድ እና ዑኒዮን ቤርሊን በ4 ነጥብ አራተኛ እና አምስተኛ ደረጃ ላይ ሰፍረዋል ።

ቶማስ ሙይለር እጅግ ስሜታዊ ያደረገውን ምርጥ ግብ ተቀይሮ ከገባ በኋላ 78ኛ ደቂቃ ላይ ነበር ያስቆጠረው
ቶማስ ሙይለር እጅግ ስሜታዊ ያደረገውን ምርጥ ግብ ተቀይሮ ከገባ በኋላ 78ኛ ደቂቃ ላይ ነበር ያስቆጠረው ምስል Sven Hoppe/dpa/picture alliance

ባዬርን ሙይንሽን ፍራይቡርግን ትናንት 2 ለ0 ድል አድርጓል ። ቀዳሚዋን ኳስ ሐሪ ኬን ከመረብ አሳርፏል ። ሔሪ ኬን የአውሮጳ ምርጥ ግብ አግቢ በሚል በተሸለመው ወርቃማ ጫማ ነበር ፍጹም ቅጣት ምቱን በተረጋጋ መልኩ በግሩም ሁኔታ ያስቆጠረው ። የሐምሌ 15 ቀን፣ 2016 ዓ.ም የስፖርት ዘገባ

ቶማስ ሙይለር እጅግ ስሜታዊ ያደረገውን ምርጥ ግብ ተቀይሮ ከገባ በኋላ 78ኛ ደቂቃ ላይ ነበር ያስቆጠረው ። ሠርጌ ግናብሬ ያሻማውን ኳስ ቶማስ ሙይለር በቀኝ እግሩ ተቆጣጥሮ ሰውነቱን በማዞር በግራ እግሩ በቀጥታ ከመረብ አሳርፏል ። የባዬር ሙይንሽን አዲሱ አሰልጣኝ ቪንሰንት ኮምፓኒንም ሆነ የቡድኑ አመራርን ከመቀመቻቸው ብድግ አስብሎ እንዲያጨበጭቡ ያስደረገ ግብ ። በዚህ ውብ ግብ የ34 ዓመቱ ቶማስ ለ710ኛ ጊዜ በመሰለፍ ከግብ ጠባቂው ሴፕ ማየር በአንድ በልጦ ክብረ ወሰን መስበር ችሏል ።

ማንተጋፍቶት ስለሺ

እሸቴ በቀለ