1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የሩስያ ቅጥረኛ ወታደሮች በማሊ አማጺያን ብርቱ ጉዳት ደረሰባቸው

ቅዳሜ፣ ሐምሌ 27 2016

ዋግነር የተባለው የሩስያ ቅጥረኛ ተዋጊ ቡድን ምዕራብ አፍሪቃዊቷ ማሊ ውስጥ ብርቱ ጉዳት እንደደደረሰበት ከሰሞኑ ተዘግቧል ። የቅጥረኛ ወታደር ቡድኑ ወደ ዐሥር የሚጠጉ ወታደሮች በቱዋሬግ አማጺያን ተገድለዋል አለያም ተማርከዋል ተብሏል። የማሊ ጦር ሠራዊት ጦሩ ተከብቦ ብርቱ ጉዳት እንደደረሰበት በሀገሪቱ ብሔራዊ ማሠራጪያ ጣቢያ በመግለጫ አስነብቧል።

https://p.dw.com/p/4j3eT
 የሩስያ ቅጥኛ የዋግነር ቡድን ተዋጊዎች ፤ ማሊ
ማሊ ውስጥ ወደ ዐሥር የሚጠጉ የሩስያ ቅጥኛ የዋግነር ቡድን ተዋጊዎች በቱዋሬግ ተገንጣዮች ሳይገደሉ ወይ ሳይማረኩ አልቀረምምስል French Army/AP/picture alliance

የሩስያ ቅጥረኛ የዋግነር ቡድን ተዋጊዎች በቱዋሬግ ተገንጣዮች ሳይገደሉ ወይ ሳይማረኩ አልቀረም

ዋግነር የተባለው የሩስያ ቅጥረኛ ተዋጊ ቡድን ምዕራብ አፍሪቃዊቷ ማሊ ውስጥ ብርቱ ጉዳት እንደደደረሰበት ከሰሞኑ ተዘግቧል ። የቅጥረኛ ወታደር ቡድኑ ወደ ዐሥር የሚጠጉ ወታደሮች በቱዋሬግ አማጺያን ተገድለዋል አለያም ተማርከዋል  ተብሏል ። ጉዳቱ የደረሰው የማሊ አማጺያን ቅንጅት በመፍጠር የማሊ ጦር ሠራዊትን ከብበው ጥቃት በሰነዘሩበት ወቅት ነው ተብሏል ።  የማሊ ጦር ሠራዊት ጦሩ ተከብቦ ብርቱ ጉዳት እንደደረሰበት በሀገሪቱ ብሔራዊ ማሠራጪያ ጣቢያ በመግለጫ አስነብቧል ። መግለጫውንም የማሊ ራዲዮ እና ቴሌቪዥን ጽ/ቤት ጋዜጠኛ ካህዲዳቱ ኮኔ እንዲህ አንብባለች ።

«ሐሙስ ሐምሌ 18 የማሊ ጦር ሠራዊት ለመጀመሪያ ጊዜ በአሸባሪዎች ጥቃት ደርሶበታል የጦሩ ፈጣን ርምጃም አሸባሪዎች በፍጥነት እንዲሸሹ ከማድረጉም ባሻገር ጠላት ብርቱ የሰብአዊ እና ቁሳዊ ጉዳት እንዲደርስበት አስችሏል የተዳከመው ጠላት እየሸሸ ነበር ከዚህ የአሸባሪዎች የመጀመሪያ ሙከራ በኋላ የአየር ንብረቱ ከፍተና አስተዋጽኦ አድርጓል ሌሊቱን የነበረው ኃይለኛ አሸዋ የቀላቀለ አውሎ ንፋስ አሸባሪዎች እና ተባባሪዎቻቸው ዳግም ኃይላቸውን እንዲያሰባስቡ እና በቀጣናው ካሉ አሸባሪ ድርጅቶች ሁሉ ድጋፍ አግኝተው እንዲደራጁ አስችሏቸዋል ።»

የቱዋሬግ አማፂያን
የቱዋሬግ አማፂያን የሩሲያ ዋግነር ቡድን ቅጥረኛ ወታደሮች ላይ ከባድ ጉዳት እንዳደረሱ ተነግሯልምስል Souleymane Ag Anara/AFP

ከአልቃይዳ ጋ ግንኙነት እንዳለው የሚነገርለት ጃማአት ኑስራት ኧል-ኢስላም ዋል ሙስሊሚን (JNIM) የተባለው አሸባሪ ቡድን የማሊ ጦር ሠራዊት ላይ ጥቃት መሰንዘሩን ዐሳውቋል ። ለሁለት ቀናት በተከታታይ ነበር በተባለው ብርቱ ውጊያ የማሊ ጦር መጠነ ሰፊ የሰብአዊ እና ቁሳዊ ጉዳት እንደደረሰበት አልሸሸገም ።

«ዓርብ ሐምሌ 19 ውጊያው እጅግ ተጠናክሮ ቀጥሏል ታጣቂ አሸባሪዎቹ እስላማዊ መንግሥት በታላቁ ሠሃራ ከተሰኙት ጥቅመኛ ተባባሪዎቻቸው እና ከከአልቃይዳ ግንኙነት ካለው ጃማአት ኑስራት ኧል-ኢስላም ዋል ሙስሊሚን በመጣመር ጦራችን ላይ በርካታ ጥቃት ሰንዝረዋል በሳኅል አሸባሪ ቡድኖች ጥምረት የተከበበው የማሊ ጦር ሠራዊት ተጨማሪ ኃይል እስኪደርስለት ድረስ ብርቱ ተጋድሎ አድርጓል የወታደሮቻችን አብነት የሌለው ጀብድ በሰው እና በንብረት ላይ የደረሰውን ጥፋት መከላከል አልቻለም »

የማሊ ኹንታ ዋና አዛዥ ኮሎኔል አሲሚ ጎይታ
የማሊ ኹንታ ዋና አዛዥ አሲሚ ጎይታ እንደ ጎርጎሪዮስ አቆጣጠር በ2021 በሳህልን ግዛት ሥልጣን ተቆጣጥረዋልምስል OUSMANE MAKAVELI/AFP/Getty Images

ከዚያም ባሻገር ታጣቂ ቡድኑ ከጦሩ ጋ አብረው ሲዋጉ የነበሩ ያላቸው የሩስያ ዋግነር ቅጥረኛ ወታደሮችን ደቡብ ቲንዛውቴኔ ውስጥ ማጥቃቱን ይፋ አድርጓል ። ለእስልምና አክራሪ የቱዋሬግ ቡድን  አባላት የሩስያ ቅጥረኛ ወታደሮች ያሉበትን ሁኔታ መረጃ በማቀበል የስለላ ተግባር የፈጸመችው ዩክሬን መሆኗም ተገልጧል ። ድርጊቱ ሩስያ እና ዩክሬን በብዙ ሺህ ኪሎ ሜትር ርቀት ከውቅያኖስ ማዶ በአፍሪቃ ምድር የእጅ አዙር ፍልሚያ መጀመራቸውን ማሳያ ተደርጎ ሊወሰድ ይችላል ።

በማሊ ከጎርጎሪዮሱ 2020 ጀምሮ በመፈንቅለ መንግስት ሥልጣኑን የተቆጣጠረው ወታደራዊ ሁንታ ከምዕራባውያኑ ጋር የነበረውን ወታደራዊ ትብብር አቋርጧል ። በአካባቢው ሰፍረው የቆዩ የምዕራባውያን ወታደሮች ጦር ሰፈሮቻቸውን ለቅቀው ለመውጣት ከተገደዱ ቆይቷል ።  የማሊ ወታደራዊ ሁንታ  ከሩስያ ጋር አዲስ ትብብር መጀመሩም የሚታወስ ነው ።

ልፋተ-ዐልቦ ።

ማንተጋፍቶት ስለሺ

አዜብ ታደሰ