1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ወባን ጨምሮ የህብረተሰብ ጤና አደጋ የሆኑ ወረርሽኞች በኢትዮጵያ

ሐሙስ፣ ሐምሌ 25 2016

በጸጥታ ችግር በተጠቁ አከባቢዎች የሚዳረሰው የወባ መከላከል ቁሳቁሶች አነስተኛ በመሆኑ በበሽታው ስርጭት ክፉኛ እየተጎዱ መሆኑን ነዋሪዎች አመለከቱ፡፡ የወባ ተጠቂዎቹ እንደሚሉት በሽታው ከጸጥታው ችግር የከፋ አደጋ ደቅኖባቸዋል፡፡

https://p.dw.com/p/4j0qu
Dr Mekdes Daba, Minister of Health, Ethiopia
ዶክተር መቅደስ ዳባ የኢትዮጵያ የጤና ሚኒስትር ፣ዶክተር ደረጀ ድጉማ የጤና ሚኒስትር ዴታ እና ዶክተር መሳይ የኅብረተሰብ ጤና ተቋም ሃላፊ ጋዜጣዊ መግለጫ ሲሰጡ ምስል Seyoum Getu/DW

ወባን ጨምሮ የኅብረተሰብ ጤና አደጋ የሆኑ ወረርሽኞች በኢትዮጵያ

 
“የወባ በሽታ እየተባባሰ ነው የመጣው፡፡ በፊት አጎበር ይሰጣል፡፡ ሰው በጸጥታው ችግር በመፈናቀሉ በቂ ምግብም የለም፡፡ በዚህ ላይ ችግሩ ስታከል የከፋ ጉዳት አለው” ያሉት የወባ ተጠቂ የምዕራብ ወለጋ ዞን ነዋሪነ ናቸው፡፡ ሌላም አስተያየት ሰጪ የወባ ወረርሽኙ ከፀጥታው ችግሩ በከፋ ጨርሶናል ይላሉ፡፡ “ከቤት ውስጥ ሰባት ስምንት ሰው በወባ ተኝተው ልታገኝ ትችላለህ፡፡ ስርጭቱም እየጨመረ እንጂ እየቀነሰ አይደለም የሚሄደው፡፡ ወባ ከፀጥታውም ችግር በከፋ እየጨረሰን ነው” ብለዋል፡፡

በትናንትናው እለት የኢትዮጵያ ጤና ሚኒስቴር በአገሪቱ እየተከሰቱ ያሉ የጤና አደጋዎችን በማስመልከት በወረርሽኞች ዙሪያ ከህብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት እና ከክልሎች ጤና ቢሮዎች ጋር እየተሰሩ ነው ባለው ጉዳይ ላይ ለመገናኛ ብዙሃን መግለጫ ስሰጥ ወባን ጨምሮ ሌሎች ወረርሽኞች እያስከተሉ ነው ባለው አደጋ ላይ ማብራሪያ ሰጥቷል፡፡ 
የዝናብ ወራቶች ማለፍን ተከትሎ መሬት ላይ ተጠራቅመው በሚተኛ ውሃ የሚባባሰው የወባ ወረርሽኝ ባለፉት ሁለት አስርት ዓመታት በተሰራው ጥብቅ ስራ በከፍተኛ ሁኔታ መቆጣጥር መቻሉን አስታውሰው ማብራሪያ የሰጡት የጤና ሚኒስትሯ ዶ/ር መቅደስ ዳባ በቅርቡ ግን በተፈጠረው አደጋውን የመዘንጋት ሁኔታ ወረርሽኙ መስፋፋቱን ጠቁመዋል፡፡ 
“አሁን ላይ በአገራችን እየተስፋፋ ላለው የወባ ተጋላጭነት ከአየር ሁኔታው በተጨማሪ የህብረተሰቡ መዘናጋትና ለወባ መከላከል የሚሰጡ ግብዓቶችን የአለመጠቀም ዝንባሌ በሽታውን ከሚያስፋፉ ምክንያቶች አንዱ ተደርጎ ይወሰዳል” ብለዋል ሚኒስትሯ፡፡አማራ ክልል በ1ዓመት ከ1 ሚሊዮን በላይ ሰዎች በወባ ተጠቅተዋል

የበሽታውን ስርጭት ለመግታት የተደረገው ጥረት 

በዚህ ዓመት እንደ አገር የወባ በሽታ እንደ ወረርሽኝ በተነሳባቸው በ10 ክልሎች ውስጥ በሚገኙ 200 ወረዳዎች የተለየ ክትትልና ቁጥጥር ተሰርቶ የበሽታውን ስርጭት ለመቆጣጠር ጥረት ተደርጓል ያሉት ሚኒስትሯ “ባለፈው አንድ ወር ብቻ በወባ የተጠቁ ከ700 ሺህ በላይ ህሙማን ህክምና እንዲያገኙ ተደርጓል” ነው ያሉት፡፡ ለዚህም እለታዊ ክትትሎች መደረጉንና የጸረ ወባ መድሃንቶችና የመከላከያ ቁሳቁሶች አቅርቦት እና ስርጭት እንዲጨምር መደረጉን አንስተዋል፡፡ በነዚህ ጊዜያትም ከ6 ሚሊየን በላይ የጸረ ወባ መድሃኒቶችና ከ7 ሚሊየን የላቀ መመርመሪያ ኪቶችን ወደ አገር ውስጥ በማስገባት ማሰራጨት መቻሉን ጠቁመዋል፡፡ የወባ ወረርሽኝ ፈተና በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ክልል
በሂደቱም ከአቅርቦት ስርጭቱ ባለፈ ጥራቱ ላይ ልዩ ትኩረት ተሰጥቶ መሰራቱም ነው የተጠቆመው፡፡ ከሁሉ የላቀ ደግሞ ግንዛቤን የማስጨበጥ ስራ አስፈላጊ ሆኖ ታይቷል ነው የተባለው፡፡ “በነዚህ ሶስት ዓመታት ስንመለከት ከ30 ሚሊየን በላይ የአጎበር ስርጭቶች ተካህዷል፡፡ ነገር ግን እነዚህን የተሰራጩ አጎበሮችን ሰቅሎ የሚጠቀምባቸው ስለሚያስፈልግ ህብረተሰቡ ይህን ያደርጋል ወይ ብለን ምልከታ ስናደርግ ከ50 በመቶ ያበለጠ ብቻ ትቅም ላይ መዋሉ የግንዛቤው ጉዳይ አሳሳቢ ነው” ብለዋል ሚኒስትሯ፡፡

ዶክተር መቅደስ ዲባባ የኢትዮጵያ ጤና ሚኒስትር
ዶክተር መቅደስ ዲባባ የኢትዮጵያ ጤና ሚኒስትር ምስል Seyoum Getu/DW

ግጭት ባለባቸው አከባቢዎች የወባ ስርጭትና አደጋው

ግጭት በተስፋፋባቸው አከባቢዎች የተባባሰው በተለይም የወባ ስርጭትን ለመግታት የተሰጠው ትኩረት ምንያህል ነው በሚል ከዶይቼ ቬለ ለቀረበላቸው ጥያቄም “ፈጣን የድንገተኛ ምላሾች በሚያስፈልግበት በነዚህ አከባቢዎች በከፍተኛ ገንዘብ ተገዛው መድሃንት ከባለድርሻ አካላት ጋር እዲተላለፍ ተደርጓል” ሲሉ ዶ/ር መቅደስ መልሰዋል፡፡የኬሚካል ርጭቶችን ጨምሮ ተጨማሪ መድሃኒቶችን ወደ አገር ውስጥ የማስገባት ስራዎችም እየተሰራ ነው ተብሏልም፡፡ የወባ በሽታ ወረርሽኝ ስርጭት በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል

የኮሌራ በሽታ ስርጭትና ያሳደረው ስጋት

ባለፈው 2015 የክረምት ወቅት በስፋት የተከሰተው የኮሌራ ወረርሽንም በአምስት ክልሎች በ153 ወረዳዎች ከተስተዋለባቸው አሁን ላይ በ109 ወረዳዎች የበሽታውን ስርጭት መቆጣጠር መቻሉ ነው የተነገረው፡፡ “ይሁንና አሁንም ለሚቀትሉት ስድስት ሳምንታት ልዩ ትኩረቱ ተደርጎ በሽታውን ስርጭት ዜሮ ማድረስ እስከሚቻል ይቀትላል” ብለዋል፡፡ 

የተመድ ህጻናት አድን ድርጅት ማሳሰቢያ 

የተባበሩት መንግስታት የህጻናት አድን ድርጅት ትናንት ባወጣው መረጃ መሰረት በተያዘው የጎርጎሳውያኑ 2024 የተለያዩ የተፈጥሮና ሰውሰራሽ አደጋዎች ተዳምረው ባስከተሉት የበሽታዎች ስርጭት መክፋት ኢትዮጵያ ውስጥ ከ8 ሚሊየን በላይ ህጻናት ከትምህርት ውጪ ሆነው ከ 5 ሺህ 400 በላይ ትምህርት ቤቶች መዘጋታቸውን ጠቁሟል፡፡ ከጥር ወር ወዲህ ብቻ ከ2 ሚሊየን በላይ ሰዎች በወባ መጠቃታቸውንና 371 ያህሉ በወረርሽኙ  መሞታቸውን የገለጸው ሪፖርቱ ኦሮሚያ ክልል የከፋውን አደጋ ማስተናገዱን ጠቁሟል፡፡
በዘጠኝ ክልሎች 151 ወረዳዎች በተከሰተው የኮሌራ ወረርሽኝም ከ21ሺህ በላይ ሰዎች ተጠቅተው 182 ሰዎች በበሽታው መዘዝ ህይወታቸው ማለፉንም የዩኒሴፍ መረጃው አሳይቷል፡፡

ስዩም ጌቱ 
ኂሩት መለሰ

አዜብ ታደሰ