1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

እንወያይ፤ ሃሳብን በነፃነት የመግለፅ መብት ዛሬ በኢትዮጵያ እንዴት ይገመገማል?

እሑድ፣ መስከረም 26 2017

ኢትዮጵያ ውስጥ ከስድስት ዓመታት በፊት የመናገር ነጻነት ከፍተኛ መሻሻል የታየበት ዓመት ለመሆን በቅቶ ነበር። ይሁንና ሀገራዊ ፖለቲካዊና በኢኮኖሚያዊ ጉዳዮች ላይ መረጃ የሚያቀርቡ ጋዜጠኞ፤ ትንታኔ የሚሰጡ የፖለቲካ ተንታኞች፤ ብሎም የኪነጥበብ ባለሞያዎች ጫና ላይ እየደረሰ መሆኑን የሰብዓዊ መብት ተከራካሪዎች በየጊዜዉ መግለጫ ያወጣሉ።

https://p.dw.com/p/4lS0x
ሃሳብን በነፃነት የመግለፅ መብት
ሃሳብን በነፃነት የመግለፅ መብትምስል YAY Images/IMAGO

እንወያይ፤ ሃሳብን በነፃነት የመግለፅ መብት ዛሬ በኢትዮጵያ እንዴት ይገመገማል?

እንወያይ፤ወቅታዊዉ ሃሳብን በነፃነት የመግለፅ መብት በኢትዮጵያ እንዴት ይገመማል?

ኢትዮጵያ ውስጥ ከስድስት ዓመታት በፊት - በ 2010 ዓ.ም የመናገር ነጻነት ከ20 ዓመታት በኋላ ከፍተኛ መሻሻል የታየበት እና የዓለም የፕሬስ ነጻነት የተከበረበት ዓመት ለመሆን በቅቶ ነበር። በአሁኑ ወቅት ግን በኢትዮጵያ ጋዜጠኞች፣ የሰብዓዊ መብት ተማጋቾች እንዲሁም ትችት እና ቅሬታ በሚያቀርቡ ዜጎች ላይ የሚደርሰዉ ወከባ፣ እሥር፣ እንግልት፣ ዛቻና ማስፈራሪያ እየጨመረ መምጣቱ ዜጎችን ጨምሮ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶችአሳሳቢ ሲሉ መግለጫ እያወጡ ነዉ። ሀገራዊ ፖለቲካዊ እና በኢኮኖሚያዊ ጉዳዮች ላይ መረጃ የሚያቀርቡ፤ ትንታኔ የሚሰጡ የነበሩ ጋዜጠኞች ፤ የፖለቲካ ጉዳይ ተንታኞች፤ እንዲሁም የበይነ መረብ የመገናኛ አውታር ባለሙያዎች ለእስር ተዳርገዋል፤ አልያም እየተባባሰ በመጣዉ ጫና ሥራቸውን ትተው ከአገር ተሰደዋል ያልቻሉትም በር ዘግተዉ ከሙያቸውም ተለያይተው ተቀምጠዋል ሲሉ የተለዩ ዘገቦች ይፋ እየሆኑ ነዉ።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ወደ ሥልጣን በመጡ ማግስት ታስረው የነበሩ በርካታ ጋዜጠኞች፤  ጦማሪያን ከእስር ተለቀዋል፣ ተሰደው የነበሩትም ወደ ሀገራቸው ተመልሰዋል፣ የግል መገናኛ ብዙሃን ቁጥርም በብዛትም በአይነትም ጨምሮ ነበር። በዚያዉ ሰሞን ኢትዮጵያ አንድም እስረኛ ጋዜጠኛ ያልተመዘገበባት፤ ሀገሪቱ  የመናገር ነጻነትን ያሻሻለችበት ዓመት መሆኑ ታምኖበት የዓለም የፕሬስ ነጻነት ቀን በመንግሥታቱ ድርጅት ይሁንታ በአዲስ አበባ ላይ ተከብሮም ነበር። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ወደ ሥልጣን እንደመጡ ታይቶ የነበረውየመገናኛ ብዙኃን ሥራ የነፃነት ዐውድ "በማንነት እና የእርስ በርስ ግጭቶች ሳቢያ ተቀልብሶ አሳሳቢ ሁኔታ ተፈጥሯል ሲል ድንበር የለሹ የጋዜጠኞች ተሟጋች ድርጅት  በተደጋጋሚ መግለፁ ይታወሳል።

ሀሳብን በነጻነት የመናገር መብት
ሀሳብን በነጻነት የመናገር መብትምስል Udo Herrmann/CHROMORANGE/picture alliance

ሀሳብን በነጻነት የመናገር መብት ኢትዮጵያ ዉስጥ ዛሬ  እንዴት ይገመገማል? የኢትዮጵያ የመናገር ነጻነት ወዴት?

በዚህ ፍሬ ርእሠ ጉዳይ ላይ ለመወያየት እና ሀሳባቸዉንም ሊያጋሩን

1ኛ. ሃይማኖት አሸናፊ ፤ በዓለም ዓቀፉ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅት - አምነስቲ ኢንተርናል የአፍሪቃ ቀንድ ተመራማሪ

2ኛ. አቶ ያሬድ ኃይለማርያም ፤ የኢትዮጵያ የሰብዓዊ መብቶች ተሟጋቾች ማዕከል ዋና ዳይሬክተር 

3ኛ. ጋዜጠኛ በላይ ማናዬ፤ በቅርቡ ከአገሩ የተሰደደ   "የኢትዮ ኒውስ” የበይነ መረብ የመገናኛ ዐውታር መሥራች  እንዲሁም

4ኛ. አያና ፈይሳ፤  በፖለቲካዉ ወቅታዊ ጉዳዮች ላይ ተንታኝ ቀርበዋል።

እንግዶቻችን ሀሳባችሁን ስላካፈሉን በማመስገን ሙሉዉን ዉይይት እንዲከታተሉ እንጋብዛለን።

አዜብ ታደሰ