ጦርነትና የጤና ተቋማት ተደራሽነት
ሐሙስ፣ ግንቦት 22 2016ዓለም አቀፉ የቀይመስቀል ኮሚቴ (ICRC) ትናንት ባወጣው መግለጫ እንዳመለከተው በአገሪቱ አንዳንድ አካባቢዎች የተፈጠረው የሰላም መደፍረስ በተለይም በገጠሩ አካባቢዎች ለሚገኙ የጤና ተቋማት አገልግሎቱ ተደራሽ እንዳይሆን አድርጎታል ብሏል፡፡
በዚህም የታመሙ ሰዎችነ አቅመ ደካሞችን፣ ህፃናትን፣ አካል ጉዳተኞችን፣ ነብሰጡሮችንና ወላዶችን መድረስ እንዳልተቻለ ነው ድርጅቱ ያስታወቀው፡፡ በአለፈው ዓመት በአማራ ክልል በተፈጠረው ቀውስ የህክምና ቁሳቁሶችን እና መድሀኒቶችን መቀላሉ ለማጓገዋዝ እንቅፋት ሆኗል ነው ያለው፡፡
በኦሮሚያ ክልል ያለው ሁኔታም በእጅጉ አስቸጋሪ እንደሆነ ያመለከተው ዓለም አቀፉ የቀይመስቀል ኮሚቴ፣ በትግራይ ክልል ተፈጥሮ የነበረው ጦርነትም ጥሎት የሄደው ጠባሳ በቀላሉ የሚታይ እንዳልሆነ አመልክቷል፡፡
በኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ የቀይ መስቀል ኮሚቴ የኮሙዩነኒኬሽን አስተባባሪ ሮቢን ዋዱ ባህር ዳር ውስጥ ለዶይቼ ቬሌ በሰጡት መግለጫ የሰላም እጦቱ በተለይ በአማራና ኦሮሚያ ክልሎች አንዳንድ አካባቢዎች ለመንቀሳቀስ አስቸጋሪ ሆኗል፣ በመሆኑም እገዛ የሚፈልጉ ሰዎችን በቀላሉ መድረስ አልተቻለም ብለዋል፡፡
“በአማራና ኦሮሚያ ክልልሎች አንዳንድ አካባቢዎች ያለው የሰላም እጦት የህክምናና ሌሎች የሰብአዊ እርዳታዎችን ለማድረስ አስቸጋሪ አድርጎታል፣ እናቶች፣ ህጻናት፣ አካል ጉዳተኞች ተፈላጊውን ድጋፍ ማግኘት አልቻሉም፡፡”
የዓለም አቀፍ ቀይ መስቀል ኮሚቴ ሰራተኞች ተንቀሳቅሰው ሰብአዊ እርዳታዎን እንዲያደርጉ የደህንነት ዋስትና እንዲሰጥ ከመንግስትና ከመንግስት ጋር ከሚዋጉ ኃይሎች ጋር ውይይት እንደሚደረግም አስተባባሪው ሮቢን ተናግረዋል፡፡
“የሰብአዊ እርዳታ ቁሳቁሶችን እርዳታ ለሚፍልጉ አካላት ማድረስ የሚያስችል የደህንነት ዋስትና እንዲሰጠን ከመንግስትና መንግስትን ከሚዋጉ አካላትጋር ውይይት ለማድረግ ጥረት እየተደረገ ነው፡፡”
ይህም ሆኖ በርካታ መድኃኒቶችን በሚሊዮን ለሚቆጠሩ ወገኖች ማድረስ መቻሉንሮቢን አመልክተዋል፣ በእርግጥ የፀጥታ ችግር ብቻ ሳይሆን ከመንግስት ጋር የሚዋጉ አካላትን አግኝቶ ማነጋገርም በእጅጉ ፈታኝ እንደሆነ ነገር ግን ደግሞን ጥረታቸውን እንደሚቀጥሉ አብራርተዋል፡፡
አጠቃላይ በአገሪቱ ውስጥ በተለይ ደግሞ በአማራና በኦሮሚያ ያለው ወቅታዊ የፀጥታ ሁኔታ እንዳሳሰበው ዓለም አቀፉ የቀይ መስቀል ኮሚቴ ባወጣው መግለጫ ጠቅሷል፣ የመገናኛ ስርዓቱም በአግባቡ አገልግሎት ባለመስጠቱ የጤና ተቋማቱ ለሚሰጡት አገልግሎት ተጨማሪ ድጋፍ ለማድረግ አላስቻለም ሲል አክሏል፡፡
ዓለምነው መኮንን
ዮሃንስ ገብረእግዚአብሄር
እሸቴ በቀለ