1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል
መቅሰፍትኢትዮጵያ

ተደጋጋሚ የተፈጥሮ አደጋዎች ያስከተሉት ጉዳት እና የመከላከል ሥራዎች በኢትዮጵያ

እሑድ፣ ነሐሴ 26 2016

በኢትዮጵያ ከሰሞኑ የተከሰቱ ተደጋጋሚ የተፈጥሮ አደጋዎች ለበርካቶች ሞት እና መፈናቀል ሰበብ ሆነዋል ። በጎፋ የመሬት መንሸራተት ከሁለት መቶ አምሳ በላይ ሰዎች መቀጠፋቸው ያጫረው የሐዘን ጠባሳ ገና አልጠገገም ። ሦስት ምሑራን እና ባለሞያዎች የተሳተፉበትን ሙሉውን ውይይት በድምፅ ማዕቀፉ መከታተል ይቻላል ።

https://p.dw.com/p/4k7Jq
Überschwemmungen in der Silte Zone in Zentraläthiopien
ምስል Silite Zobe Government communication

የሰሞኑ ተደጋጋሚ የተፈጥሮ አደጋዎች የበርካቶችን ሕይወት ቀጥፏል

በኢትዮጵያ ከሰሞኑ የተከሰቱ ተደጋጋሚ የተፈጥሮ አደጋዎች ለበርካቶች ሞት እና መፈናቀል ሰበብ ሆነዋል ።  በጎፋ የመሬት መንሸራተት  ከሁለት መቶ አምሳ በላይ ሰዎች መቀጠፋቸው ያጫረው የሐዘን ጠባሳ ገና አልጠገገም ። ጎንደር፤ ሰሜን ሸዋ ዞን፤ ኦሮሚያ ክልል ዶዶላ ወረዳ፤ መካከለኛው ኢትዮጵያ ሥልጤ ዞን፤ ደቡባዊ የኢትዮጵያ አካባቢዎች በዎላይታና በጋሞ ዞኖችንም ሰሞኑን ተከታታይ የጎርፍ እና የመሬት መንሸራተት አደጋዎች ከተከሰቱባቸው አካባቢዎች የሚጠቀሱ ናቸው ።

አደጋዎቹ በሰው ሕይወት እና ንብረት ላይ ከፍተኛ ጉዳት አድርሰዋል ። በአዝርእት እና ሰብሎች ምርት ላይ ብርቱ ጉዳትን አስከትለዋል ። በእርግጥ የተፈጥሮ አደጋዎችን ሙሉ ለሙሉ መከላከል አይቻልም ። ሆኖም በየትኛውም የዓለማችን ክፍሎች ሊከሰቱ የሚችሉ አደጋዎችን እና መጠናቸውን በተመለከተ ግን በሳይንሳዊ ትንታኔ ቅድመ ትንበያ የሚሰጡ ተቋማት አሉ ።  በኢትዮጵያም አደጋዎችን የመለየት እና የቅድመ ጥንቃቄ ርምጃዎች እንዲወሰዱ የሚያሳስቡ፤ አደጋ ከደረሰ በኋላም ምላሽ የሚሰጡ ተቋማት እንቅስቃሴ ያደርጋሉ ።

የኢትዮጵያ አደጋ ሥጋት ሥራ አመራር ኮሚሽን፤ የአየር ጠባይ ትንበያ ላይ የሚሠራው የሜትሪዮሎጂ ኢንስቲትዩት እንዲሁም፤ በዩኒቨርሲቲ ደረጃም ምርምሮችን እና ጥናቶችን የሚያከናውነው የከርሰ ምድር ጥናት ተቋም ተጠቃሾች ናቸው ። ከሦስቱም ተቋማት ባልደረባ የሆኑ ኃላፊዎች እና አጥኚዎች በዛሬው የእንወያይ መሰናዶ ተካፋይ ናቸው ። «ተደጋጋሚ የተፈጥሮ አደጋዎች ያስከተሉት ጉዳት እና የመከላከል ሥራዎች በኢትዮጵያ» የዛሬው እንወያይ መሰናዶ ዐቢይ ትኩረት ነው ።

ጎፋ ። ፎቶ፦ ከማኅደር
በጎፋ የመሬት መንሸራተት በርካቶች ሕይወታቸውን አጥተዋል ። ፎቶ፦ ከማኅደርምስል MICHELE SPATARI/AFP/ Getty Image

በዶዶላ የጣለው ከባድ ዝናብ ያስከተለው የከፋ ጉዳት

በውይይቱ 3 እንግዶች ተሳታፊ ናቸው ።  እንግዶቻችን፦ 1-ፕሮፌሰር አታላይ ዓየለ፦ በአዲስ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ፤ የጂኦ ፊዚክስ፤ ሕዋ ሣይንስ እና አስትሮኖሚ ተቋም የመሬት መንቀጥቀጥ ሳይንስ ተመራማሪ እና መምሕር እንዲሁም የሴስሞሎጂ ክፍል ኃላፊ፤ 
2-ዶ/ር አሳምነው ተሾመ፦ በኢትዮጵያ  ሜትሪዮሎጂ ኢንስቲትዩት የሜትሪዮሎጂ ትንበያ እና ቅድመ ማስጠንቀቂያ ምርምር ዘርፍ ምክትል ዋና ዳይሬክተር፤ እንዲሁም
3-አቶ አታለል አቡሀይ፦ የኢትዮጵያ አደጋ ሥጋት ሥራ አመራር ኮሚሽን የሕዝብ ግንኙነት እና የኮሙኒኬሽን ተወካይ ሥራ አስፈጻሚ ናቸው ። 

ሙሉውን ውይይት በድምፅ ማዕቀፉ መከታተል ይቻላል።

ማንተጋፍቶት ስለሺ

ነጋሽ መሐመድ