የፊት ለፊቱ ንግግር አንድምታ እና የኢትዮጵያ መሻት
እሑድ፣ መጋቢት 15 2016ጠቅላይ ሚንስትር ዐቢይ አህመድ የትግራዩ ጦርነት ካበቃ በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ ከተለያዩ ክልሎች የህዝብ ተወካዮች እና የኃያማኖት ተቋማት ጋር በተከታታይ ውይይት እያደረጉ ነው።
በየውይይቱ ክልሎቹም ሆኑ የኃይማኖት ተቋማቱ በተናጥል እና የጋራ ወቅታዊ የሃገራዊ ጉዳዮች ላይ ሃሳብ ፣ አስተያየት እና ጥቆማ ሰጥተዋል፤ አፋጣኝ ምላሽ ይሻሉ ያሏቸውንም ጥያቄዎች አንስተዋል።
ሰሞኑን በአማራ ክልል የተካሄዱ ህዝባዊ ዉይይቶች ላይ የተሰጡ አስተያየቶች
ግጭት ጦርነት እንዲቆም ፤ ፖለቲካዊ ንግግር በአፋጣኝ እንዲጀመር ፤ ተፈናቃዮች ወደ ቀዬአቸው እንዲመለሱ ፣ በድርቅ እና በረሃብ የተጎዱ አካባቢዎች ተገቢው እርዳታ እንዲደርስ፣ ሰላም እና መረጋጋት የራቃቸው አካባቢዎች ትኩረት እንዲያገኙ የዋጋ ግሽበት ያስከተለው የኑሮ ውድነት አጋዥ መፍትሄ እንዲያገኙ ተሳታፊዎች አጽንዖት ከሰጡባቸው ጉዳዮች ውስጥ ተጠቃሾች ናቸው ።
በየውይይቱ ሁሉም አጽንዖት ሰጥተው ካነሷቸው ጉዳዮች ውስጥ ሃገሪቱ ከገባችበት ሁለንተናዊ ቀውስ መውጣት እንድትችል የመንግስት እና የሌሎቹን ጥረት እና ቁርጠኝነት የጠየቁበት ይገኙበታል ።
መሰረታዊ ኤኮኖሚያዊ እና ማህበራዊ ችግሮችም በዚያው ልክ እልባት እንዲያገኙ ማስቻልም እንዲሁ ትኩረት አግኝተዋል። ጠቅላይ ሚንስትር ዐቢይ አህመድ በሀገሪቱ ሰላም መረጋጋት እንዲፈጠር የታጠቁ ኃይሎችን ጨምሮ ከተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች ጋር ያለቅድመ ሁኔታ ለመነጋገር መንግስታቸው ቁርጠኛ መሆኑን ገልጸዋል።
ኢትዮጵያ ካለችበት ተጨባች ማህበረ ፖለቲካ ኢኮኖሚያዊ ቀውስ ለመውጣት መሰል የፊት ለፊት ንግግር ሚና እንዳላቸው በበጎ የተመለከቱ እንዳሉ ሁሉ ውይይቱ የይስሙላ ነው በሚል ያጣጣሉም አልጠፉም ።
የዚህ ሳምንት የእንወያይ ዝግጅታችን «ጠቅላይ ሚንስትር ዐቢይ አህመድ ከተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች ጋር የጀመሯቸው የፊት ለፊት ንግግር አንድምታ እና የኢትዮጵያ መሻት » በሚል ርዕስ ተወያዮችን ጋብዞ አወያይቷል።
ታምራት ዲንሳ