1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የጋዛው ጦርነት በአካባቢው ጽንፈኝነትን ያባብስ ይሆን?

ዓርብ፣ ታኅሣሥ 12 2016

የአረብ ሀገራት ወጣቶች በጋዛ የሚሆነውን በመገናኛ ብዙሀን ሲከታተሉ ቁጣቸው መባባሱ አልቀረም። ምዕራባውያን መንግሥታት ጦርነቱን መደገፋቸው ብዙዎችን ከሚያስቆጡ ጉዳዮች መካከል ነው።አንድ ግብጻዊ ጋዜጠኛ እንዳለው በግብጽ ይህ እየተንጸባረቀ ነው።ለምሳሌ እሥራኤል በጋዛ ለምታካሂደው ጦርነት ጀርመን የምትሰጠው ገደብ የለሽ ድጋፍ ግብጾችን አበሳጭቷል።

https://p.dw.com/p/4aUvx
Gazastreifen | Israelische Soldaten im Gazastreifen
ምስል GIL COHEN-MAGEN/AFP/Getty Images

የጋዛው ጦርነት በአካባቢው ጽንፈኝነትን ያባብስ ይሆን?

የእሥራኤልና የአረብ ሀገራት ግንኙነት ከቀድሞው የመሻሻሉ ተስፋ፣ እሥራኤል በጋዛ በቀጠለችው ድብደባ ምክንያት እየደበዘዘ በመሄድ ላይ ነው። ከዛሬ ሁለት ወራት በፊት አንስቶ እሥራኤል በጋዛ የምታካሂደው ድብደባ የአረብ ሀገራት ህዝብን በእጅጉ አስቆጥቷል። ይህም በመካከለኛው ምሥራቅ ጽንፈኝነትን እንዳያባብስ አስግቷል። ዮርዳኖስ የሚኖረው ወጣቱ የፊልም ዳይሬክተር ኦማር ራማል የምእራባውያንን ቋንቋ መናገር፣ ፊልሞቻቸውን ማየት ፣ታዋቂ ሰዎቻቸውን ሳይቀር በማኅበራዊ መገናኛ ዘዴዎች መከተል እንደማይፈልግ በኢንስታግራም ጽፏል። 800 ሺህ ተከታዮች ባሉት በኢንስታግራም ገጹ  «ሁሉም አንድ ናቸው። እውን ሀማስን ሙሉ በሙሉ «ማጥፋት» ይቻላል?ልባቸው እንደ ድንጋይ ነው። እኛን ከሰው አሳንሰው ነው የሚያዩን።» ሲል መጻፉን የዶቼቬለ ካትሪን ሻሀር ዘግባለች ።ራማል በትውልድ ፍልስጤማዊ በመሆኑ ከሌሎች የመካከለኛው ምሥራቅ ሰዎች የበለጠ ለጋዛ ግጭት ቅርብ ሳይሆን አይቀርም። እንዲህ አይነት ሐሳብ የሚያንጸባርቀው ግን እሱ ብቻ አይደለም። 

የጋዛ ድብደባን በመቃወም በቤይሩት የፈረንሳይ ኤምባሲ ፊት ለፊት የተካሄደ ሰልፍ
የጋዛ ድብደባን በመቃወም በቤይሩት የፈረንሳይ ኤምባሲ ፊት ለፊት የተካሄደ ሰልፍ ምስል ANWAR AMRO/AFP/Getty Images

ጀርመን፣ የአውሮጳ ኅብረት እና ዩናይትድ ስቴትስ አሸባሪ ሲሉ የፈረጁት ሀማስ መስከረም 26 ቀን 2016 ዓ.ም. በእሥራኤል ላይ ጥቃት ከፈጸመበት ጊዜ አንስቶ እሥራኤል በጋዛ የምታካሂደው ድብደባ ቀጥሏል። ባለፉት ሁለት ወራት ያለማቋረጥ ከጋዛ የሚወጡ ፎቶዎች ብዙዎችን አስደንግጠዋል። በጦርነቱ የሚሞተው ሰው ቁጥር በየጊዜው ማሻቀብ በመካከለኛው ምሥራቅ የህዝቡ አመለካከት በፍጥነት እንዲቀያየር ማድረጉን መቀመጫውን ዩናይትድ ስቴትስ ያደረገ የአረብ ባሮሜትር የተባለ የጥናት ተቋም አስታውቋል። የዮርዳኖሱ ንጉስ ዳግማዊ አብደላ በኅዳር አጋማሽ ከአውሮጳ ኅብረት ባለሥልጣናት ጋር ባካሄዱት ውይይት ላይ የጋዛው ጦርነት በአካባቢው ሀገራት ጽንፈኝነትን ለአሥርት ዓመታት ማቀጣጠሉ አይቀርም ሲሉ አስጠንቅቀው ነበር።በሃማስ የታገቱ ጥቂት እስራኤላዉያን ተለቀቁ

የአረብ ሀገራት ወጣቶች በጋዛ የሚሆነውን በመገናኛ ብዙሀን ሲከታተሉ ቁጣቸው መባባሱ አልቀረም። ምዕራባውያን መንግሥታት ጦርነቱን መደገፋቸው ብዙዎችን ከሚያስቆጡ ጉዳዮች መካከል ነው። አንድ ግብጻዊ ጋዜጠኛ እንዳለው በግብጽ ይህ እየተንጸባረቀ ነው።ለምሳሌ እሥራኤል በጋዛ ለምታካሂደው ጦርነት ጀርመን የምትሰጠው ገደብ የለሽ ድጋፍ ግብጾችን አበሳጭቷል። ታዲያ ይህን መሰሉ ቁጣ ወደ ኃይል እርምጃ ሊቀየር ይችል ይሆን? የአረብ ባሮሜትር ከዚህ ቀደም ባካሄደው ጥናት ፖለቲካዊ ጉዳዮችን ለማሳካት ኃይል መጠቀም ብዙዎች የሚያወግዙት ነበር።

የዮርዳኖሱ ንጉስ ዳግማዊ አብደላ
የዮርዳኖሱ ንጉስ ዳግማዊ አብደላ ምስል picture alliance/dpa

ተቋሙ ከጋዛው ጦርነት በፊት በቱኒዝያ ባካሄደው የዳሰሳ ጥናት መሠረት በፍልስጤምና በእሥራኤል መካከል ሰላም ለማውረድ ከሁለት ሦስተኛ በላይ ቱኒዝያውያን የሁለት መንግሥታት መፍትሄን ደግፈው ነበር።  ኃይልን መጠቀምን የመረጡት ደግሞ 6 በመቶ ብቻ ነበሩ። የጋዛው ጦርነት ከቀጠለ በኋላ ግን የትጥቅ ትግልን መፍትሄ ያሉት ቁጥር ወደ 36 በመቶ አድጓል።የአመለካከት ለውጡ ለእስራኤል ቅርብ በሆኑ ሀገራት ከተስፋፋ አስቸጋሪ እንደሚሆን ተመራማሪዎች ስጋታቸውን ገልጸዋል። በአሁኑ ጊዜ አል ቃይዳን እና በእንግሊዘኛ ምሃጻሩ ISIS ወይም ራሱን እስላማዊ መንግሥት ብሎ የሚጠራውን ቡድን የመሳሰሉ ድርጅቶች፣ ግለሰቦች በአይሁዶች ላይ ጥቃት እንዲፈፅሙ ጥሪ እንደሚያቀርቡ ሄግ ኔዘርላንድስ በሚገኘው በዓለም አቀፍ የፀረ ሽብር ማዕከል ከፍተኛ ተመራማሪ ታንያ ሜህራ ለዶቼቬለ ተናግረዋል።ማሕደረ ዜና፣ የጋዛ እልቂት፣ የምዕራባዉያን ድምፀት መለወጥ

« በእሥራኤልና በሀማስ መካከል የሚካሄደው ግጭት በረዘመ ቁጥር ለአይ ሲ ስ አባላትን ለመመልመል መሳቢያ ነው የሚሆነው። ስለዚህ እኔ እንደሚመስለኝ ጦርነቱ ቶሎ ካበቃ ምልመላው እንዲቀንስ ሊያደርግ ይችላል።ያ ካልሆነ ግን ለምልመላ ዓላማቸው፣ ጥቅም ላይ ሊያውሉትና አጋነው  ሊያስተዋውቁትም ይችላሉ።»

በእስራኤል ድብደባ የወደመ የጋዛ ሰርጥ አካባቢ
በእስራኤል ድብደባ የወደመ የጋዛ ሰርጥ አካባቢምስል Ronen Zvulun/REUTERS

ሜህራ እንደሚሉት የተለያዩ ቡድኖችም አሁን ጋዛ የተፈጠረውን ሁኔታ ለራሳቸው እንደሚሆን አድርገው ሊጠቀሙበት ይችላሉ። ፀረ ስደተኞች እና ጸረ ሴማዊነት ስሜቶችን ለማቀጣጠል የሚፈልጉ ቀኝ ጽንፈኛ ቡድኖች ጦርነቱን የጥቅማቸው ማስፈጸሚያ ሊያደርጉት እንደሚችሉም ነው የተናገሩት።
«እኔ የማስበው ለምሳሌ መንግሥታት የሀማስን ግጭት ለራሳቸው ጥቅም ማራመጃ ለማድረግ እንደሚሞክሩ ጠለቅ አድርገን ማየት አለብን። ቀኝ ጽንፈኞችም ግጭቱን በመጠቀም ሙስሊም ጠልነትንና ፀረ ሴማዊነትን ለማስፋፋት ይጠቀሙበታል። »በሜህራ ገለጻ መሠረት የጋዛው ግጭት በደቡብና በደቡብ ምሥራቅ እስያ ጽንፈኝነት እንዲስፋፋ እያደረገ ነው።

ካትሪን ሻሀር

ኂሩት መለሰ

እሸቴ በቀለ