1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የጃራ ተፈናቃዮች ተቃውሞ

ዓርብ፣ የካቲት 1 2016

የመንግሥት አካል በአቅራቢያ ባይኖርም እየደረሰ ያለውን የርሀብ አደጋ የሚመለከተው ክፍል አውቆ አስፈላጊውን እገዛ እንዲያደርግ መንገድ በመዝጋት ሰልፍ መካሄዱን ሌላ አስተያየት ሰጪ አስረድተዋል፡፡

https://p.dw.com/p/4cECK
ተፈናቃዮቹ መንገድ በመዝጋት ተቃውሞአቸውን አሰምቷል
ተፈናቃዮቹ መንገድ በመዝጋት ተቃውሞአቸውን አሰምቷልምስል Alemenw Mekonnen/DW

የተፈናቃዮች ሮሮ

ከኦሮሚያና ከቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልሎች ተፈናቅለው በአማራ ክልል ሰሜን ወሎ ዞን ጃራ የመጠለያ ጣቢያ የሚገኙ ተፈናቃዮች የእርዳታ እህል ተቋርጦብናል በሚል ብሶታቸውን በሰላማዊ ሰለፍ ገለጹ። የዞኑ አደጋ መከላከልና ምግብ ዋስትና ጽሕፈት ቤት እርዳታው በቀጣይ 10 ቀናት ውስጥ ይደርሳቸዋል ብሏል፡፡
ባለፉት አራት ዓመታት በኦሮሚያና በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልሎች በነበሩ ግጭቶች ተፈናቅለው በአማራ ክልል ሰሜን ወሎ ዞን ጃራ መጠለያ ጣቢያ የሚገኙ ተፈናቃዮች የምግብ እርዳታ ከተቋረጠባቸው ከሁለት ወራት በላይ በመሆኑ በርሀብ እየተጎዱ እንደሆነ ለዶይቼ ቬሌ ተናግረዋል፡፡

በመሆኑም «ችግራችንን መንግሥትና ህዝብ ይወቅልን» በሚል  ሰልፍ ማካሄዳቸውን ገልፀዋል። ከመካከላቸው ያነጋገርነው አንድ ተፈናቃይ «እርዳታ ከተቋረጠ ከሁለት ወር በላይ ሆኗል በተደጋጋሚ ለዞኑ አደጋ መከላከልና ምግብ ዋስትና ጽሕፈት ቤት ኃላፊዎች ብናመለክትም ምላሽ ሊገኝ አልተቻለም» ነው ያሉት፡፡
ሌላዋ በመጠለያ ጣቢያው የምትገኘው አስተያየት ሰጪም «በርሀብ በጣም የተጎዱ ሰዎች ከመኝታ መነሳት ተስኗቸዋል ርሀቡ እየጎዳቸው ነው» ብለዋል፡፡ በመሆኑም ችግሩን ለሚመለከተው ለማሳወቅ ሰልፍ መውጣታቸውን አመልክተዋል፡፡

ተፈናቃዮቹ መንገድ በመዝጋት ተቃውሞአቸውን አሰምቷል
ተፈናቃዮቹ መንገድ በመዝጋት ተቃውሞአቸውን አሰምቷልምስል Alemenw Mekonnen/DW


የመንግሥት አካል በአቅራቢያ ባይኖርም እየደረሰ ያለውን የርሀብ አደጋ የሚመለከተው ክፍል አውቆ አስፈላጊውን እገዛ እንዲያደርግ ሰልፍ መካሄዱን ሌላ አስተያየት ሰጪ አስረድተዋል፡፡
አማራ ክልል የሰሜን ወሎ ዞን አደጋ መከላከልና ምግብ ዋስትና ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ዓለሙ ይመር ስለጉዳዩ ተጠይቀው ተፈናቃዮች ሰልፍ አካሂደዋል፣ መንገድም ዘግተዋል፣ በሚል ድርጊቱ ተገቢ እንዳልሆነ ነው ያብራሩት። ሆኖም አሁን ከተፈናቃዮች ጋር በመግባባት መንገዶች እንደገና ተከፍተዋል፣ ተፈናቃዮችም ወደ መጠለያቸው ገብተዋል ብለዋል፡፡ በእርግጥ እርዳታ መዘግየቱን ያመኑት አቶ ዓለሙ ከክልልና ከፌደራል አደጋ መከላከልና ምግብ ዋስትና ኃላፊዎች ጋር መነጋገራቸውንና በቀጣይ 10 ቀናት ውስጥ እርዳታ እንደሚደርስ ተስፋ እንዳላቸው ገልጠዋል፡፡
ጉዳዩን አስመልክተን ተጨማሪ አስተያየት ለማካተት ለአማራ ክልል አደጋ መከላከልና ምግብ ዋስትና ማስተባበሪያ ኮሚሽን ኃላፊ  በተደጋጋሚ ያደረግነው የስልክ ጥሪ ስልኩ ባለመነሳቱ አልተሳካም፡፡

ዓለምነው መኮንን
ዮሐንስ ገብረእግዚአብሔር
ሽዋዩ ለገሠ