1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የወላይታ ዞን የሠራተኞቹን ደሞዝ ከሚቀጥለው ዓመት ተበድሮ ለመክፈል መገደዱ ተገለጸ

ሰኞ፣ ግንቦት 12 2016

የወላይታ ዞን የሠራተኞቹን ደሞዝ ከቀጣይ ዓመት ተበድሮ ለመክፈል መገደዱን የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ሳሙኤል ፎላ ለዶይቼ ቬለ ተናገሩ። የዞኑ የመንግሥት ሠራተኞች ባለፉት ሳምንታት የሦስት ወራት ደሞዛቸው እንዲከፈላቸው አቤት በማለት ይገኛሉ። ከ2009-2012 ባሉት ዓመታት የሠራተኞች ቁጥር ከ23 ሺሕ ወደ 61 ሺሕ ማደጉን አቶ ሳሙኤል ተናግረዋል።

https://p.dw.com/p/4g4mG
Äthiopien | Demonstration in Wolaita Sodo
ምስል Shewangizaw Wegayehu/DW

ዛሬም ያልተመለሰው የደሞዝ ጥያቄ በዎላይታ

የዎላይታ ዞን በሺህዎች የሚቆጠሩ የመንግሥት ሠራተኞች ከባለፈው ሳምንት ጀምሮ ውዝፍ የሦስት ወራት ደሞዝ ክፍያ እንዲፈጸምላቸው እየጠየቁ ይገኛሉ ፡፡  ያምሆኖ እስከአሁን ለጥያቄያቸው ከዞንና ከክልል መስተዳድሮች ተግባራዊ ምላሽ እንዳላገኙ ሠራተኞቹ ተናግረዋል ፡፡ በዚህም የተነሳ አሁን ላይ ከነቤተሰቦቻቸው በችግር ላይ መውደቃቸውን ሠራተኞቹ ተናግረዋል ፡፡

ዞኑ ክፍያውን ለመፈጸም ለምን ተሳነው  ?

የሠራተኞቹን የደሞዝ ይከፈለን ጥያቄ አስመለክቶ ከዶቼ ቬለ ጋር ቃለምልልስ ያደረጉት የዎላይታ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ሳሙኤል ፎላ  ዞኑ ለሠራተኞቹ ደሞዝ መክፈል ያተቸገረው በሁለት ምክንያቶች ነው ይላሉ ፡፡ አንድም የወረዳ መዋቅሮች መሥፋት ሁለትም ሲንከባለል በመጣው የአፈር ማዳበሪያ ዕዳ የተነሳ የበጀት አለመጣጣም በመከሰቱ  ነው ብለዋል  ፡፡

የመንግስት ሰራተኞችን ማዋከብ ይቁም

በተለይም በዞኑ አዳዲስ የወረዳ መዋቅሮች መበራከት  ፣ የሠራተኞች እና ተሾሚዎች ቁጥር መጨመር ለበጀት ጉድለቱ መከሰት ምክንያት መሆኑን የጠቀሱት ዋና አስተዳዳሪው “ በተለይም ባለፉት አራት ዓመታት የአገልግሎት ተደራሽነትን ለመፈጠር ተጨማሪ የወረዳ እና የከተማ አስተዳደሮች ተቋቁመዋል ፡፡ ይህም የሠራተኞውና የተሾሚዎችን ቁጥር እንዲጨምር አድርጓል ፡፡ ለምሳሌ በ2009 ዓም ላይ 23 ሺህ የነበረው የዞኑ ሠራተኞች ቁጥር አሁን ላይ ከ61 ሺህ በላይ ደርሷል ፡፡ ይህ በዕቅድ ላይ ያልተመሠረተ የሠራተኛ ቅጥር በዞኑ ላይ የበጀት ጫና ፈጥሮ ይገኛል “ ብለዋል ፡፡

ዎላይታ ሶዶ ደሞዝ እንዲከፈላቸው በሰልፍ የሚጠይቁ የመንግሥት ሠራተኞች
የዎላይታ ዞን የመንግሥት ሠራተኞች የሦስት ወራት ደሞዛቸው እንዲከፈላቸው እየጠየቁ ይገኛሉ።ምስል Shewangizaw Wegayehu/DW

አስተዳደራዊ  መዋቅርን እንደሥራ ዕድል ፈጠራ 

ዶቼ ቬሌ አስተያየታቸውን የጠየቃቸው በጂንካ ዩኒቨርሲቲ የሥነ ዜጋና የፌዴራሊዝም መምህርና ተመራማሪ አቶ አንዱዓለም ግርማ የወረዳ መዋቅሮች ወደ ተገልጋዩ ለመቅረብና ለመልካም አስተዳደር መስፈን ከፍተኛ አስተዎጽዎ እንዳላቸው ገልጸዋል ፡፡

የቀጠለው የደሞዝ ጥያቄ በዎላይታ ዞን

ይሁንአንጂ አሁን ላይ የአስተዳደር መዋቅሮች  ከአገልግሎት ተደራሽነት ዓላማቸው ይልቅ የወጣቶች የሥራ ዕድል መፍጠሪ አድርጎ የመቁጠር አመለካከት መኖሩን የጠቀሱት አቶ አንዱዓለም  “ባለው በጀት ብቻ  የሚሰፋ ወረዳ የራሱ አደጋ አለው ፡፡ ምክንያቱም የለው ውስን የበጀቱ ሀብት ለደሞዝና ተያያዥ ወጪዎች ብቻ ሥለሚውል የልማት ሥራዎች ይስተጓጎላሉ ፡፡ ይህም ውሎ አድሮ ህዝቡ ከመዋቅሩ ምን ተጠቀምኩ የሚል ጥያቄ እንዲያነሳ ሊያደርግ ይችላል “ ብለዋል ፡፡

ዎላይታ ሶዶ ደሞዝ እንዲከፈላቸው በሰልፍ የሚጠይቁ የመንግሥት ሠራተኞች
የዎላይታ ዞን በሠራተኞች ቁጥር መጨመር እና በማዳበሪያ ዕዳ ምክንያት ደሞዝ ለመክፈል መቸገሩን አስተዳዳሪው ተናግረዋል። ምስል Shewangizaw Wegayehu/DW

ጊዜያዊና ዘላቂ መፍትሄ  

የወረዳና የከተማ አስተዳደሮችን ቁጥር መጨመር የአገልግሎት ተደራሽነትን ለማስፋት አስተዋጽዎ ቢኖረውም ባስከተለው ከፍተኛ የበጀት ጫና የተነሳ ዞኑ አሁን ላይ ለሠራተኞች ደሞዝ ለመክፈል አስቸጋሪ እንዳደረገው የዎላይታ ዞን ዋና አስተዳዳሪው አቶ ሳሙኤል ይናገራሉ  ፡፡

የደሞዝ ይከፈለን ሰልፍ በዎላይታ

በአሁኑ ወቅት አጣዳፊ የሆነውን የሠራተኞችን ደሞዝ ለመክፈል የዞኑ መስተዳድር ከቀጣዩ የ2017 ዓም በጀት ታሳቢ የሚደረግ ብድር በመውሰድ ችግሩን በጊዚያዊነት ለመፍታት እየጣረ እንደሚገኝ ዋና አስተዳዳሪው ተናግረዋል ፡፡

የሥነ ዜጋና የፌዴራሊዝም መምህሩ አቶ አንዱዓለም ግን ከዚህ ይህነ ችግር ለመሻገር ዘላቂ መፍትሄ ያሥፈልጋል ይላሉ ፡፡ የመጀመሪያው የሠራተኛ ቅጥር በዕቅድ እንዲመራ ማድረግ ሲሆን ሁለተኛው የፋይናንስ አቅምን በማሳደግ ዞኑ በሁለት እግሩ እንዲቆም ማድረግ ነው ብለዋል ፡፡ ለዚህም የገቢ መሰብሰብ አቅምን ማጠናከርና ወጪን በመቀነስ በጀትን በአግባቡ መጠቀም እንደሚገባ ጠቅሰዋል ፡፡

ሸዋንግዛው ወጋየሁ 

እሸቴ በቀለ