1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የወለጋዉ ጥቃትና የኢሰመጉ ጥሪ

ረቡዕ፣ ጥር 3 2015

በታህሳስ 13 ቀን 2015 ዓ.ም በምዕራብ ወለጋ ቤጊ ወረዳ ሼክ ኡስማኤል ሀሰንና አብደላ የሚባሉ ግለሰቦች በአንድ ቤት ዉስጥ መገደላቸውን፣በወረዳው ጦቢ ቀበሌ አቶ ሽብሩ ቂጠሳ የሚባል ግለሰብ በመኖሪያ ቤቱ ውስጥ መገደሉን፣ በተመሳሳይ በላሎ ቀበሌ ቱሻ የሚባል ግለሰብ በመኖሪያ ቤቱ መገደሉን በመግለጫው ተገልጸዋል፡፡

https://p.dw.com/p/4M0pp
Äthiopien | Oromiya Region
ምስል G. Fischer/blickwinkel/picture alliance

የኢሰመጉ ጥያቄ፣የወለጋ ግጭትና ግድያ

የኢትዮጵያ መንግስት ተቃዋሚ ፖለቲከኞችን ማሰር፣ማንገላታትና መብታቸዉን  መጣሱን እንዲያቆም የኢትዮጵያ የሰብአዊ መብቶች ጉባኤ (ኢሰመጉ) ጠየቀ።ገለልተኛዉ የመብት ተሟጋች ጉባኤ ትናንት ባወጣዉ መግለጫ እንዳለዉ ርዕሰ ከተማ አዲስ አበባን ጨምሮ  በተለያዩ የሐገሪቱ ክፍሎች የሚንቀሳቀሱ የተቃዋሚ ፓርቲ መሪዎችና አባላት ያለ ሕጋዊ ምክንያትና ሥርዓት ይታሰራሉ።

ጉባኤዉ እንደሚለዉ ምዕራብ ወለጋና ምስራቅ ወለጋ ዞኖች ዉስጥ በሚገኙ 6 ወረዳዎች ደግሞ የመንግስት ፀጥታ ኃይሎች ኦነግ-ሸኔን ለማጥፋት በከፈቱት ዘመቻ ሰላማዊ ሰዎች ተገድለዋል፤ ተዘርፈዋል፣ የተለያየ የሰብአዊ መብት ጥሰት ደርሶባቸዋልም።የአሶሳዉ ወኪላችን ነጋሳ ደሳለኝ የኢሰመጉን መግለጫ ከዓይን ምስክሮች አስተያየት ጋር ደብሎ ያጠናቀረዉን ዘገባ ልኮልናል።

በታህሳስ 13 ቀን 2015 ዓ.ም በምዕራብ ወለጋ ቤጊ ወረዳ ሼክ ኡስማኤል ሀሰንና አብደላ የሚባሉ ግለሰቦች በአንድ ቤት ዉስጥ መገደላቸውን፣በወረዳው  ጦቢ ቀበሌ አቶ ሽብሩ ቂጠሳ የሚባል ግለሰብ በመኖሪያ ቤቱ ውስጥ መገደሉን፣ በተመሳሳይ በላሎ ቀበሌ ቱሻ የሚባል ግለሰብ በመኖሪያ ቤቱ መገደሉን በመግለጫው ተገልጸዋል፡፡

በምዕራብ ኦሮሚያ በመንግስት ጸጥታ ሐይሎች እና ታጣቂዎች መካከል በሚደረገው ውጊያ  የሰብአዊ መብት ጥሰት እየተፈጸ እንደሚገኝ የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ጉባኤ ትናንት ጥር 2/2015ዓ.ም ባወጣው መግለጫ ገልጸዋል፡፡ በምዕራብ ወለጋ ዞን ቤጊ፣ቆንዳላ፣ባቦ ጋምበል የተባ ሉወረዳዎች ውስጥ  መንግስት በታጣቂዎች ላይ እየወሰደ ባለው እርምጃ በወረዳው በሚኖሩ ሰዎች  ላይ የተለያዩ ሰብአዊ መብት ጥሰት መድረሱን በመግለጫው ጠቁመዋል፡፡ ታህሳስ 12 እና 13 /2015 ዓ.ም በዞኑ ቤጊ ወረዳ 13 ሰዎች ህይወት ማለፉን ከነዚህም መካከል 9ኙ በወረዳው ዳላዱ በተባለ ቀበሌ በአንድ ቦታ መገደላቸውን አክለዋል፡፡

የኢሰመጉ አርማ
የኢሰመጉ አርማምስል Ethiopian Human Rights Council

ከሁለት ሳምንት በፊት አላዱ በሚባል ቀበሌ ውስጥ በመንግስት ጸጥታ ሀይሎችና በሸማቂዎች መካከል ግጭት ተከስ እንደነበር እና ያልታጠቁ ሰዎች ህይወት ማለፉን  የአካባቢው ነዋሪዎች ለዶቸቬለ  ተናግረዋል፡፡ ዘጠኝ ሰዎች በአላዱ በአንድ ቀን ህይወታውን ማለፉንና በኢሰመጉ የተጠቀሱትን ሸክ ኡስማኤል ሀሰን ጨምሮ እንዲዚሁ አራት ሰዎች ህይወት ማለፉን ጠቁመዋል፡፡

የኢትዮጵ ሰብአዊ መብቶች ጉባኤ አሰባስብኩ ባለው መረጃ መሰረት የተለያዩ የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮችና አባላት ላይ  የመብት ጥሰቶች እየደረሱ ነው፡፡ በኦሮሞ ፌዴራላዊ ኮንግረስ(ኦፌኮ)፣ በመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት (መኢአድ) እንዲሁም ሌሎች ፓርቲዎች ላይ

እየተፈጸመ ያለው ከህግ አግባብ ውጪ የሆነ እስር በአስቸኳይ እንዲቆም አሳስበዋል፡፡   የዋስትና መብታቸውን እንዲከበር፣ በስውር ታስረዋል ያላቸውንም የታሰሩበት ስፍራ ለሚመለከተው አካል ግልጽ እንዲሆንም ሲል በመግለጫው አክለዋል፡፡

Äthiopien | Wahlen | Oromia

በጉዳዩ ላይ ማብራሪያ እንዲሰጡን ለሚመለከታቸውን የክልልና የዞን የስራ ኃላፊዎች በስልክ ጥረት ባደረግም ስልካቸውን ለማንሳት ፈቃደኛ አልሆኑም፡፡ በምዕራብ ወለጋ ዞን የተለያዩ ወረዳዎችን ውስጥ ደርሰዋል ስለተባለው የመብት ጥሰትን አስመልክቶ ምላሽ እንዲሰጡን የጠየቅናቸው የምዕራብ ወለጋ ዞን አስተዳደርና ጸጥታ ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ደበላ ኦላና ሰብሰባ ላይ በመሆናቸው ከሰዓት በኃላ እንዲንደውልላቸውን ቃል ቢገቡም በተባለው ሰዓት ስልላካቸውን ለማንሳት ፈቃደኛ ሳይሆኑ ቀርተዋል፡፡ በምዕራብ እና በምስራቅ ወለጋ ዞኖች ውስጥ በሚገኙ የተለያዩ ወረዳዎች ውስጥ በሚንቀሳቀሱ ታጣቂ ቡድኖች እና በመንግስት የጸጥታ ሀይል በሚወሰዱ እርምጃዎች የሚፈጸሙ የሰብዓዊ መብቶች ጥሰቶችን መንግስት እንዲያስቆም ኢሰመጉ ጠይቀዋል፡፡

ነጋሳ ደሳለኝ

ነጋሽ መሐመድ

አዜብ ታደሰ