1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የኤርትራ የነፃነት ቀንና የፕሬዝደንት ኢሳያስ መልዕክት

ሐሙስ፣ ግንቦት 17 2015

የቀድሞዉ የኤርትራ ሕዝብ ነፃ አዉጪ ግንባር (EPLF) ወይም ሻዕቢያ አስመራን የተቆጣጠረበት 32ኛ ዓመትና ኤርትራ በይፋ ከኢትዮጵያ ተገንጥላ የራስዋን ነፃ መንግስት የመሰረተችበት 30ኛ ዓመት በዓል ትናንት ኤርትራ ዉስጥ በተለያዩ ሥርዓቶች ተከብሯል።

https://p.dw.com/p/4RpAE
Eritrea Asmara Poster Patriotismus
ምስል Getty Images/AFP/J. Vaughan

የቀድሞዉ የኤርትራ ሕዝብ ነፃ አዉጪ ግንባር (EPLF) ወይም ሻዕቢያ አስመራን የተቆጣጠረበት 32ኛ ዓመትና ኤርትራ በይፋ ከኢትዮጵያ ተገንጥላ የራስዋን ነፃ መንግስት የመሰረተችበት 30ኛ ዓመት በዓል ትናንት ኤርትራ ዉስጥ በተለያዩ ሥርዓቶች ተከብሯል። ኤርትራን ላለፉት 32 ዓመታት የገዙት ፕሬዝደንት ኢሳያስ አፈወርቂ ለህዝባቸዉ ባሰሙት ንግግር የዘንድሮዉ በዓል በትግል የተገኙ ድሎች ደምቀው መታየት በጀመሩበት ወቅት እየተከበረ ነዉ ብለዋል።የመቀሌዉ ወኪላችን ሚሊዮን ኃይለስላሴ ንግግሩን ተከታትሎ ተከታዩን ዘገባ ልኮልናል።

የኤርትራ ነፃነት ቀን በተከበረበት ይፋዊ መድረክ ንግግር ያደረጉት ፕሬዝደንት ኢሳያስ ጠላት ያሏቸው የውጭ ሀይሎች አሁንም ኤርትራን መፈተን እንዳላቆሙ እና ይህ ለመከላከል ፕሬዝደንቱ አዲስ የትግል ዘይቤ እንደሚያስፈልግ አስታውቀዋል። ያነጋገርናቸው በኤርትራ ያለው ስርዓት የሚቃወሙ ከሀገራቸው ውጭ ያሉ ኤርትራውያን በበኩላቸዉ ሀገሪቱ በከፋ ጭቆና ውስጥ መሆን ይገልፃሉ። 

አስመራ ከተማ
አስመራ ከተማምስል Reuters/T. Mukoya

ኤርትራ ከኢትዮጵያ የተለየችበት 32ኛ የነፃነት በዓል በተለያዩ የዓለም ክፍሎች የሚገኙ ኤርትራውያን እያከበሩት ይገኛሉ። በውጭ ሀገራት ከተደረጉ የኤርትራ ነፃነት ቀን መታሰቢያ ስነስርዓቶች በተጨማሪ ትላንት ግንቦት 16 ቀን በሀገሪቱ ዋና ከተማ አስመራ፣ የተለያዩ እንግዶች እና በርካታ የሀገሪቱ ዜጎች የታደሙበት ይፋዊ የአከባበር መድረክ መካሄዱ የኤርትራ መንግስታዊ ቴሌቭዥን አስመልክቷል። በትላንትናው መድረክ ንግግር ያሰሙት፣ ከነፃነትዋ ጀምሮ ሀገሪቱን እየመሩ ያሉ የኤርትራው ፕሬዝደንት ኢሳያስ አፈወርቂ፥ የዘንድሮው የነፃነት ቀን በተካሄደ ትግል የተገኙ ድሎች ደምቀው መታየት በጀመሩበት ወቅት እየተከበረ ያለ ነው ሲሉ ገልፀውታል። ጠላት ያሏቸው የውጭ ሀይሎች አሁንም ኤርትራን መፈተን እንዳላቆሙ ያስታወቁት ፕሬዝደንቱ "ይህ ለመመከት አዲስ የትግል ዘይቤ" እንደሚያስፈልግ በንግግራቸው አንስተዋል። 

ለበርካታ ዓስርት ዓመታት ኤርትራ እና ኢትዮጵያ ግጭት ውስጥ እንደሚቆዩ እየሰራች ነበር በማለት አሜሪካን የከሰሱት ፕሬዝደንት ኢሳያስ፣ ባለፊት ዓምስት ዓመታት የታየው ለውጥም ለማደናቀፍ 'የዋሺንግተን ቡድን' ያሉት አካል በወኪሎቹ በኩል ጦርነት እስከ መክፈት የደረሰ ተግባራት መፈፀሙ ገልፀዋል። ፕሬዝዳንቱ የሱዳን ጉዳይ በንግግራቸው ያነሱ ሲሆን ሀገሪቱ ወደከፋ ሁኔታ እያመራች መሆኑ በማውሳት ቀጠናዊ መፍትሔ ለሱዳን ችግር እንደሚያስፈልግ ጠቁመዋል። 

Karte Eritrea Äthiopien
ኢትዮጵያ ምስል AP Graphics/DW

ይህ በእንዲህ እንዳለ የኤርትራ የነፃነት ቀን ከኤርትራውያን ዘንድ የተለያዩ አስተያየቶች ይሰጡበታል።የሀገሪቱ የነፃነት ቀን አስመልክተን ያነጋገርናቸው ከሀገራቸው ውጭ የፖለተካ ድርጅት አቋቁመው በኤርትራ ያለው ስርዓት ለመጣል የሚታገሉ ኤርትራውያን የነፃነት ቀን በዓሉ የተደበላለቀ ስሜት እንደሚጥርባቸው ይናገራሉ። የኤርትራውን ጥምረት ሀገራዊ ግንባር የተባለ ድርጅት አባል እና አመራር የሆኑት ኤርትራዊው አቶ ዮናስ አሸብር፥ ኤርትራ ላለፉት 32 ዓመታት በአንድ ቡድን እና ግለሰብ የጭቆና አገዛዝ ላይ መቆየትዋ በማንሳት፥ በሀገሪቱ ያለው ስርዓት ያወግዛሉ። አቶ ዮናስ ጨምረውም በትግል የተገኘው ነፃነት በአንድ ቡድን ከህዝብ ተነጥቋል፣ ይህ ለመቀየር ቀጣይ ትግል ይፈልጋል ሲሉ ያክላሉ። ከኢትዮጵያ ከተነጠለች 32 ዓመታት ያስቆጠረችው ኤርትራ በታሪኳ ምርጫ ተደርጎባት አይታወቅም። ዓለምአቀፍ የመብት ተሟጋች ድርጅቶች በሀገሪቱ ከፍተኛ የሰብአዊ እና ዴሞክራሲያዊ መብት ጥሰት መኖሩ በየግዜው የሚያወጡት ሪፖርት ያመለክታል። 

ሚሊዮን ኃይለሥላሴ

ነጋሽ መሐመድ

አዜብ ታደሰ