1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የጀርመን እንደራሴዎች ጉብኝት በኤርትራ

ማክሰኞ፣ ታኅሣሥ 2 2011

ወይዘሮ እንዲሪያ ሊንድሆልስ እንደሚሉት የዉጪዉ ዓለም ሥለ ኤርትራ ሁል ጊዜ አሉታዊ ጉዳዮችን ብቻ ያነሳል የሚል ቅሬታ አላቸዉ።ሌላዉ ቀርቶ ኤርትራ እና ኢትዮጵያ የገጠሙትን ጠብ እና ጦርነት ለማስወገድ በቅርቡ ላደረጉት ስምምነት ተመስጋኙ፣እና ተደናቂዉ ኢትዮጵያ እና የኢትዮጵያ አዳዲስ መሪዎች መሆናቸዉ አስመሮችን አላስደሰተም።

https://p.dw.com/p/39tf5
Andrea Lindholz, MdB
ምስል Karpf! Kreativ

Dtl.Bundestag fact-finding mission in Ertrea - MP3-Stereo

 

በጀርመን ምክር ቤት የሐገር ዉስጥ ጉዳይ ቋሚ ኮሚቴ የመልዕክተኞች ቡድን በኤርትራ ያደረገዉን ጉብኝት አጠናቅቆ ተመልሷል።የቋሚ ኮሚቴዉ ሊቀመንበር ወይዘሮ አንድሪያ ሊንድሆልስ የመሩት ቡድን በኤርትራ ቆይታዉ ከተለያዩ የሐገሪቱ መንግሥት ባለሥልጣናት፣ ከማሕበራት እና ድርጅት መሪዎች ጋር ተወያይቷል።ወይዘሮ ሊንድሆልስ DW እንደነገሩት ዉይይቱ በስደተኞች፣ በሰብአዊ መብት ይዞታ፣ በብሔራዊ አገልግሎት እና በአካባቢዉ ሠላም ላይ ያተኮረ ነበር።ሊንድሆልስን ሉድገር ሻዶምስኪ በስልክ አነጋግሯቸዋል።ነጋሽ መሐመድ አጠናቅሮታል።

«ኤርትራ፣ ከዋና ዋና የስደተኞች መፍለቂያ ሐገራት አንዷናት» ይላሉ፣ የእንደራሴዎቹ ጓድ ሊቀመንበር ወይዘሮ አንድሪያ ሊንድሆልስ፣«ፖለቲካዊ ግንኙነቱ ደግሞ ከባድ ነዉ።» አሁን ብዙ ዉይይቶች፤ ድርድሮች ይደረጋሉ እና ጊዜዉ ለ«እዉነት ፍለጋ» Fact Findling የሰጠ ነዉ-በእንደራሴዋ እምነት።በጊዜዉ ለመጠቀም አምስት የቋሚ ኮሚቴ አባሎቻቸዉን መርተዉ ባለፈዉ እሁድ አስመራ ገቡ።አርብ በርሊን።

በአምስቱ ቀን ቆታቸዉ ከፕሬዝደንቱ አማካሪ እስከ ሰራተኞች ማሕበር መሪ ያሉ ባለሥልጣናት እና ተወካዮችን አነጋግረዋል።«ከሠራተኛ ማሕበራት ተወካዮች፤ ከወጣት እና ሴቶች ማሕበራት ተጠሪዎች ጋር ተነጋግረናል።ከዉጪ ጉዳይ ሚንስትር፣ ከማስታወቂያ ሚንስትር፣ ከፕሬዝደንቱ አማካሪ ጋር ተወያይተናል።»

ከንግግር ዉይይቱ አብይት ርዕሶች ቀዳሚዎቹ፣ ይዘረዝራሉ፣-«የስደተኞች፤ከስደት ተመላሾች ጉዳይ፣የሰብአዊ መብት ይዞታን የተመለከቱ የሁል ጊዜ ርዕሶችን ማንሳት በመቻላችን አብረን ለተጓዝነዉ አምስት ሰዎች ጥሩ ግንዛቤ ያገኘንበት ነዉ።(ኤርትራዎቹም) ጥሩ የሐገር ዉስጥ መርሕ ገቢር ማድረግ ከፈለጉ፣ለዉጪ እና ለልማት ተራድኦ መርሕም ጥሩ እይታ ሊኖራቸዉ ይገባል።»
 

Eine afrikanische Insel der Architektur
ምስል DW/Y.Tegenewerk

ኤርትራዉያን ተቃዋሚ ፖለቲከኞች፣ የመብት ተሟጋቾች፣ ስደተኞች ሆኑ ዓለም አቀፍ የመብት ተሟጋች ተቋማት የኤርትራ መንግስትን በሰባዊመብት ረጋጭነት ደጋግመዉ ይወቅሳሉ።ወቃሾቹ ደጋግመዉ ከሚያነሷቸዉ ጉዳዮች አንዱ ገደብ የለሹ ብሔራዊ አገልግሎት ነዉ።ወጣቶች ያለፍላጎታቸዉ ገደብ የለሽ ወታደራዊ እና የሲቢል አገልግሎት እንዲሰጡ መገደዳቸዉ፣በስልጠና እና በአገልግሎቱ ወቅት ይደርስባቸዋል የሚባለዉ ግፍ ወጣቶች ሐገራቸዉን ለቅቀዉ በገፍ እንዲሰደዱ ዋና ምክንያት መሆኑም በተደጋጋሚ ይጠቀሳል።

የኤርትራ መንግሥት ለወቃሽ ተቺዎቹ የሚሰጠዉ መልስ ብሕራዊ አገልግሎቱን በሥራ ላይ ያዋለዉ ከኢትዮጵያ ሊሰነዘር የሚችል ጥቃትን ለመከላከል ነዉ-የሚል ነዉ።አሁንስ?

«(ከኢትዮጵያ ጋር ከተደረገዉ) የሠላም ስምምነት ከፈነጠቀዉ ተስፋ ጋር ጋር አያይዘን ተነጋግረናል። ስምነቱ ዳር ከዘለቀ ተጨማሪ ወጣት ሴቶች እና ወንዶች አገልግሎት እንዲሰጡ አይገደዱም።አስፈላጊ አይደለም። የወጣቶቹ ተወካዮችም ልክ እንደኛ ሁሉ መንግስት አገልግሎቱን ያስቀራል፣ ይሕ ቢቀር  እንኳ ወደ አስራ ስምምት ወራት ዝቅ ያደርገዋል የሚል ተስፋ አላቸዉ።ይሕ ማለት ግን ባንድ ንጋት ግዳጁ ወደ አስራ-ስምምንት ወራት ዝቅ ይላል ማለት አይደለም።ከኢትዮጵያ ጋር የተደረገዉ የሠላም ዉል ከፀና ግን የአገልግሎት ግዳጁም ይቀየራል የሚል እምነት አለኝ።ለዉጡን ሕዝቡም ይጠብቀዋል።»

 

ወይዘሮ እንዲሪያ ሊንድሆልስ እንደሚሉት የዉጪዉ ዓለም ሥለ ኤርትራ ሁል ጊዜ አሉታዊ ጉዳዮችን ብቻ ያነሳል የሚል ቅሬታ አላቸዉ።ሌላዉ ቀርቶ ኤርትራ እና ኢትዮጵያ የገጠሙትን ጠብ እና ጦርነት ለማስወገድ በቅርቡ ላደረጉት ስምምነት ተመስጋኙ፣እና ተደናቂዉ ኢትዮጵያ እና የኢትዮጵያ አዳዲስ መሪዎች መሆናቸዉ አስመሮችን አላስደሰተም።

Eritrea, Hauptstadt Asmara, Busbahnhof
ምስል picture-alliance

በተለይ የጀርመኑ ዉጪ ጉዳይ ሚንስትር ሐይኮ ማስ ባለፈዉ ጥቅምት መጀመሪያ ሥለስምምነቱ ለጀርመን ምክር ቤት ባደረጉት ንግግር፣ ስምምነቱን አድንቀዉ ኤርትራን በሰብአዊ መብት ረጋጭነት መዉቀሳቸዉን የኤርትራ መሪዎች አጥብቀዉ ተቃዉመዉታል።«በየዉይይቱ ሁሉ ያነሱት ነበር» አሉ ሊንድሆልስ «የማስ አስተያየት ባልተፈለገ ሥፍራ ነዉ ያረፈዉ» አከሉ።

                                

«በሠላም ሒደቱ ሁለቱም ተሳታፊዎች ናቸዉ።ኤርትራ የራስዋ ድርሻ ነበራት።አስተዋፅኦ አለመደነቁ ሁል ጊዜ ትችት ብቻ የሚሰነዘርባት ይመስላል።በተቃራኒዉ ኢትዮጵያ ብቻ መሪ ሆና መታየትዋ ጉዳት አድርሷል።በዚሕ ረገድ የማስ ዓረፍተነገር ወይም አስተያየትም ሌላ ሥፍራ ነዉ ያረፈዉ።»

የኤርትራ ስደተኞች ባሁኑ ወቅት ወደሐገራቸዉ ቢመለሱ የወደፊት ኑሯቸዉን የሚመሰርቱበት ምንም ነገር እንደሌላ እንደራሴዋ ተናግራዋል።ሁኔታዉ ግን መሻሻል አለበት ባይ ናቸዉ።

ነጋሽ መሐመድ

እሸቴ በቀለ