1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የኢትዮጵያውያን ታላቁ የአፍሪቃ ሩጫ በአሌክሳንደሪያ ከተማ ተካሄደ።

ሰኞ፣ ጥቅምት 7 2015

ዘንድሮ በተካሄደው ውድድር የሚገኘው ገቢ በአርቲስት ሰለሞን ቦጋለ የሚመራውን"ኅብረት ለበጎ"የተሰኘውን የበጎ አድራጎት ማኀበር ለማገዝ ይውላል ተብሏል።

https://p.dw.com/p/4IIGu
USA „Great African Run” in Virginia
ምስል Tariku Hailu/DW

ታላቁ የፍሪካውያን ሩጫ

"አብሮነት መሻል ነው"በሚል መሪ ቃል በተካሄደው ውድድር፣በአሜሪካ የኢትዮጵያ አምባሳደር ስለሺ በቀለ፣የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ፕሬዚዳንት ምክትል ኮሚሽነር አትሌት ደራርቱ ቱሉ፣ሌሎች ታዋቂ አትሌቶች እንዲሁም "የእረኛዬ" ድራማ ተዋንያን ተሳትፈውበታል።

የአትላንታው ዘጋቢያችን ታሪኩ ኃይሉ ዝርዝሩን ልኮልናል

በአሜሪካ ቨርጂኒያ ግዛት አሌክሳንደሪያ ከተማ ባለፈው ቅዳሜ የተከናወነው የአምስት ኪሎ ሜትር የጎዳና ላይ ሩጫ፣ዘንድሮ ለአራተኛ ጊዜ የተካሄደ ነው።

ግራንድ አፍሪቃ ራን ወይንም የአፍሪቃ ሩጫ፣በአሜሪካ የኢትዮጵያ አምባሳደር ዶክተር ስለሺ በቀለ፣የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ፕሬዚዳንት አትሌት ደራርቱ ቱሉና ሌሎች የኦሎምፒክ ባለሜዳሊያ ኢትዮጵያውያን አትሌቶችን አሳትፏል።

አትሌት ቀነኒሳ በቀለ፣አትሌት ፋጡማ ሮባ፣አትሌት ሚሊዮን ወልዴ፣አትሌት ታሪኩ በቀለና ቁጥሬ ዱለቻም ይገኙበታል።

በሺዎች የሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያን እና ትውልደ ኢትዮጵያውያንም ታድመውበታል።

የዝግጅቱ አስተባባሪ ዶክተር ጋሻው አበጋዝ በተለይ ለዶይቸ ቨለ እንደተናገሩት፣የዘንድሮው ውድድር ሦስት ዓላማዎችን አንግቦ የተዘጋጀ ነበር።

ዘንድሮ በተካሄደው ውድድር የሚገኘው ገቢ በአርቲስት ሰለሞን ቦጋለ የሚመራውን"ኅብረት ለበጎ"የተሰኘውን የበጎ አድራጎት ማኀበር ለማገዝ ይውላል።

ማኀበሩ አዲስ አበባ ውስጥ የኩላሊት ሕክምና አገልግሎት መስጫ ሆስፒታል የመገንባት ውጥን ያለው ሲሆን፣አርቲስት ሰለሞን ቦጋለ እና ሌሎች "የእረኛዬ"ድራማ ተዋንያንና ደራሲያኑ በዝግጅቱ ላይ ተገኝተዋል።

የታላቁ አፍሪቃ ሩጫ ቦርድ በሚያካሄደው ምርጫ መሠረት፣በየዓመቱ በሚካሄደው ዝግጅት ላይ፣ እንግዶች እንደሚጋበዙ አስተባባሪው አመልክተዋል።

በቀጣይም፣የአፍሪቃ ታላቁ ሩጫ የኢትዮጵያውያንን አብሮነት የሚያጠናክሩ ሥራዎች የማካሄድ ዕቅድ መያዙን አስተባባሪው አመልክተዋል።

በአዋቂዎች የአምስት ኪሎ ሜትር እንዲሁም በህፃናት የአንድ ኪሎ ሜትር ሩጫ፣በተካሄደበት የዘንድሮው ውድድር ሁሉም ተሳታፊዎች ሜዳሊያ ተበርክቶላቸዋል።

ታሪኩ ሃይሉ 
ዮሐንስ ገብረእግዚአብሄር
ኂሩት መለሰ