የኢትዮጵያ የምርጫ ፣የፖለቲካ ፓርቲዎች ምዝገባና የምርጫ ስነ ምግባር ማሻሻያ አዋጅና ፋይዳው
እሑድ፣ ሰኔ 9 2016የኢትዮጵያ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ባለፈው ሳምንት ማክሰኞ ባካሄደው መደበኛ ስብሰባ የኢትዮጵያ የምርጫና የፖለቲካ ፓርቲዎች ምዝገባና የምርጫ ስነ ምግባር አዋጅን አሻሽሎ አጽድቋል። በተሻሻለው አዋጅ በተለይ «ኃይልን መሠረት ያደረገ አመጽ ውስጥ የተሳተፈ ፓርቲ ተግባሩን ማቆሙና ሕገ መንግሥታዊ ዴሞክራሲያዊ ስርዓትን አክብሮ ለመንቀሳቀስ መስማማቱ በሚመለከተው የመንግሥት አካል ከተረጋገጠ በልዩ ሁኔታ እንደ ፖለቲካ ፓርቲ መመዘገብ እንደሚችል ተጠቅሷል። በአብላጫ ድምጽ የጸደቀው አዋጁ የኢትዮጵያ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በአሸባሪነት ፈርጆት የነበረውን የህወሓትን ሕጋዊ ሰውነት መልሶ የሚሰጥ ነው ። የኢትዮጵያ የፍትህ ሚኒስትር ግድዎን ጢሞትዮስ ፣ግጭት በሚካሄድባቸው ክልሎች ለሚንቀሳቀሱ ሀገራዊ ምክክር መድረክ ውስጥ መሳተፍ ለሚፈልጉ ታጣቂ ቡድኖችና ድርጅቶችም እድል የሚሰጥ መሆኑን አስረድተዋል።
በተሻሻለው አዋጅ ላይ አዎንታዊም አሉታዊም አስተያየቶች እየተሰጡ ነው። ማሻሻያውን የደገፉ እርምጃው በኢትዮጵያ የትጥቅ ትግል የሚያካሂዱ ቡድኖች ወደ ሰላማዊ ትግል እንዲገቡ የሚያበረታታ ሲሉ የማሻሻያው ተቃዋሚዎች ደግሞ ወደ አማራና አፋር ክልሎች ተስፋፍቶ በነበረው በትግራዩ ጦርነት የተፈጸሙ ወንጀሎች ፍትህ ሳያገኙ ተድበስብሰበው እንዲቀሩ የሚያደርግ ሲሉ ይቃወማሉ። የኢትዮጵያ የምርጫ የፖለቲካ ፓርቲዎች ምዝገባና የምርጫ ስነ ምግባር አዋጅ ማሻሻያ ፋይዳ ፣ተግዳሮቶቹና አማራጭ መፍትሄዎች የዛሬው እንወያይ የሚያተኩርበት ጉዳይ ነው። በዚህ ውይይት ላይ የሚሳተፉ ሦስት እንግዶችን ጋብዘናል ። እነርሱም አቶ ደያሞ ዳሌ «ግሎባል ፒስ ባንክ» የተባለው የፖለቲካ ተንታኝ ፣ ዶክተር ገብረ እየሱስ ተክሉ በመቀሌ ዩኒቨርስቲ የግጭትና የግጭት መፍትሄዎች ተመራማሪ እና አቶ ተክለሚካኤል አበበ ካናዳ የሚኖሩ የሕግ ባለሞያ ናቸው ።ሙሉውን ዝግጅት ለማዳመጥ ከታች የሚገኘውን ማገናኛ ይጫኑ
ኂሩት መለሰ