1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ለሦስተኛ ዙር ቀጠሮ የተያዘለት የኢትዮጵያ እና የሶማሊያ ውይይት በቱርክ

ረቡዕ፣ ነሐሴ 8 2016

ኢትዮጵያ እና ሱማሊያ የገቡበትን ውዝግብ ለመፍታት በማለም ሰኞ እለት እና ትናንት በቱርክ አንካራ የተደረገው ውይይት ተጨባጭ መፍትሔ ሳይገኝበት ለሦስተኛ ዙር ውይይት ቀጠሮ በመያዝ ተጠናቋል።

https://p.dw.com/p/4jS8U
Türkei | Stadt Ankara Luftverschmutzung
ምስል Dogukan Keskinkilic/AA/picture alliance

የኢትዮጵያ እና የሶማሊያ ውይይት በቱርክ

የማሸማገል ሚናውን የወሰደችው ቱርክ የውጭ ጉዳይ ሚንስትሯ ሐካን ፊዳን ትናንት በሰጡት መግለጫ "በአንዳንድ መሠረታዊ" ያሏቸው መርሆዎች ዙሪያ በሁለቱ ሀገራት መካከል መግባባት መኖሩን አመልክተዋል። የሁለቱ ሀገራት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮችም ሀገራቱ የገቡበት የግንኙነት መሻከር በቀጣዩ ውይይት ይፈታል የሚል ተስፋ እና እምነት እንዳላቸው በየፊናቸው ገልፀዋል። ቱርክ ውስጥ ይቀጥላል የተባለው ሦስተኛው ዙር ንግግር መስከረም 7 እንዲካሄድ የተወሰነ ሲሆን፣ በዚህም ዘላቂ ስምምነት ላይ ለመድረስ ውጥን መያዙ ተነግሯል።

የሁለተያውን ዙር ውይይት በተመለከተ ቱርክ የሰጠችው መግለጫ


ኢትዮጵያ ራስ ገዝ ከሆነችው፣ ነገር ግን ሶማሊያ የሉዓላዊ ግዛቴ አንድ አካል ናት ከምትላት ሶማሊላንድ ጋር የባሕር በር ሊያስገኛት የሚችለውን የመግባቢያ ስምምነት ከወራት በፊት መፈረሟ ከሶማሊያ ጋር ሆድና ጀርባ አድርጓታል።


ይህንን የግንኙነት መሻከር ለማስወገድ "ሸትል" በሚባለውና ተወያይ ወገኖች ፊት ለፊት በማይገናኙበት ወይም ቀጥተኛ ያሆነው የዲፕሎማሲ የአሠራር መርህ የማሸማገል ሚናውን በወሰደችው ቱርክ ሁለቱ ሀገራት ለሁለት ቀናት በአንካራ ሁለተኛ ዙር ውይይት አድርገዋል። ተጨባጭ ውጤት አልባ ሆኖ በተጠናቀቀው ውይይት ማብቂያ ላይ የቱርኩ የውጭ ጉዳይ ሚንስትር ሐካን ፊዳን ምን ምን እንደሆኑ በግልጽ ባይዘረዝሩም በአንዳንድ መሠረታዊ መርሆዎች መግባባት እንደተፈጠረ ተናግረዋል። 

 "የተወያየንባቸው ጉዳዮች ቁጥር ከመጀመሪያው ዙር ጋር ሲነጻጸር በከፍተኛ ሁኔታ መጨመሩ አስደስቶኛል። በአንዳንድ ዋና ዋና መርሆች ላይ እንደ ልዩ ሁኔታዎች አስፈላጊ የሆኑ ተጨባጭ እርምጃዎች ዝርዝሮች እና ቴክኒኮች ላይ ማተኮር ችለናል። ይህ ጉልህ መሻሻልን ያካትታል። አላማችን ነባር ሥጋቶችን በማስታረቅና ክፍተቶችን በማስተካከል ለሶማሊያና ለኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን ለቀጣናው ጭምር የሚጠቅም ሥራ ማከናወን ነው። የጋራ እና ገንቢ መፍትሔ በእጃችን ላይ ነው ብለን እናምናለን። ሂደቱን በተሳካ ሁኔታ እንደምናጠናቅቅ ተስፋ በማድረግ ለሦስተኛው ዙር መስከረም 17 ቀን በአንካራ እንሰበሰባለን።"


የኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ሚንስቴር መግለጫ


የኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ሚንስቴር አሸማጋይዋ ቱርክ የኢትዮጵያን "ተገቢነት ያለው ፍላጎት እና አስተማማኝ የባሕር በር ለማግኘት በሰላማዊ መንገድ የያዘችውን አካሄድ ትገነዘባለች" ብላ እንደምታምን ባወጣው መግለጫው ጠቅሷል። የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ታዬ ዐዕቀ ሥላሴ ኢትዮጵያ የተፈጠረውን ውጥረት ለማርገብ እንዲሁም ሰላማዊ ግንኙነቶች እንዲቀጥሉ ፍላጎት እንዳላት ገልፀዋል።

ሶማሌላንድ በርበራ ወደብ
ሶማሌላንድ በርበራ ወደብምስል Eshete Bekele/DW

"ኢትዮጵያ ውጥረቱን ለማርገብ እና የቀጠናውን ግንኙነት ወደነበረበት ለመመለስ ጥረት አድርጋለች። አሁን ያሉ ልዩነቶችን ለመፍታት እና መደበኛ ግንኙነቶችን ወደነበሩበት ለመመለስ የሚረዳንን ቀጣይ ተሳትፎ እንጠባበቃለን። ቀጣይነት ባለው ተሳትፎ ታላላቅ ነገሮችን መወሰን እንደሚቻል በእርግጥ እናውቃለን። ስለዚህ በአዎንታዊ መልኩ መቀጠል በኛ ላይ ኃላፊነት ነው። አሁን ካለው ሁኔታ በላይ ወደፊት ብዙ እንጠብቃለን። ከሶማሊያ ወንድሞቻችን ጋር በእርግጥም በቱርክ እርዳታ እና አመቻችነት የበለጠ ፍሬያማ የሆነ የሶስተኛ ዙር ውይይት እንጠብቃለን። እኛ ሁሌም ከተስፋ ጋር እንጂ ከተስፋ መቁረጥ ጋር አይደለንም።"


የሶማሊያ ምለሽ 

የሶማሊያ የውጭ ጉዳይ እና ዓለም አቀፍ ትብብር ሚኒስትር አህመድ ሞሊም በበኩላቸው የቀጣዩ ውይይት ወደ መፍትሔ እንደሚያመራቸው ተስፋ እንደሚያደርጉ ገልፀዋል።

ሶማሌላንድ በርበራ ወደብ
ሶማሌላንድ በርበራ ወደብምስል Eshete Bekele/DW

"በዚህ የውይይት ዙር መሻሻል የታየ ሲሆን ሶማሊያ ሉዓላዊነቷን፣የግዛት አንድነትዋን እና አንድነቷን ለማስጠበቅ ቁርጠኛ መሆኗን ቀጥላለች። ለሶስተኛው ዙር ድርድር ስንዘጋጅ የያዝነው መነሳሳት ወደ መጨረሻው መፍትሔ እንደሚያመራን ተስፋ እናደርጋለን። የሶማሊያ ፌዴራላዊ መንግስት የሶማሊያን ሕዝብ ክብር እና ሃብት የሚጠብቅ በዓለም አቀፍ ሕግ እና በተባበሩት መንግስታት የባሕር ሕግ ስምምነት መሰረት ሰላማዊ እና ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ያለው ውጤት ለማምጣት ቁርጠኛ ነው።"

ስለ ቱርክ ጥረት የተንታኝ አስተያየት

ምንም እንኳን ሶማሊያ ኢትዮጵያ እና ሶማሊላንድ ያደረጉትን የመግባቢያ ስምምነት የሉዓላዊነቴ እና የግዛት አንድነቴ ሥጋት ነው ብትለውም ኢትዮጵያ የሕልውናዬ ጉዳይ ነው በሚል የባሕር በር ማግኛ ስምምነቱን መፈረሟን ገልጻለች። ያነጋገርናቸው የጅኦ ፖለቲካ ተንታኝ፣ የሁለቱ ሀገራት ሁኔታ የቱርክን ጥረት አጋዥ አይመስልም።

ቱርክ በሶማሊያ ግዙፍ የባሕር ኃይል የጦር ሰፈር ያቋቋመች እንዲሁም የመከላከያ እና የኢኮኖሚ ትብብር ስምምነት የፈረመች ሲሆን፣ ለኢትዮጵያም የሀገሯ ምርት የሆኑ ሰው አልባ የጦር አውሮፕላን - ድሮኖችን የምትሸጥ፣ በቀጣናውም ከፍተኛ ፍላጎት ያላት ሀገር ናት።

ሰለሞን ሙጩ
ልደት አበበ
ኂሩት መለሰ