1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የኢትዮጵያ አየር መንገድ የተቀላቀለው የኢ-ኮሜርስ ካርጎ አገልግሎት

ሐሙስ፣ የካቲት 21 2016

የአየር ካርጎ አገልገሎቱ ወደ ኢ-ኮሜርስ አገልግሎት ማደግ አለበት ያሉት አቶ መስፍን ጣሰው ዛሬ ግንባታው ተጠናቆ የተመረቀው የካርኮ መጋዘን ከተለመደው የሚለየው፤ ትናንሽ እቃዎች በጥቅል መጥተው ግን እዚህ ተበትነው ለደንበኞች የሚደርሱበት አሰራር የሚዘረጋ በመሆኑ ነው በማለት አየር መንገዱ ዘርፉን መቀላቀሉን አረጋግጠዋል።

https://p.dw.com/p/4d2nk
Ethiopian Airlines EAL CEO Inauguration, Addis Abeba, Ethiopia
ምስል Seyoum Getu/DW

የኢትዮጵያ አየር መንገድ የኢ-ኮሜርስ ካርጎ አገልግሎትን ተቀላቀለ

የኢትዮጵያ አየር መንገድ የተቀላቀለው የኢ-ኮሜርስ ካርጎ አገልግሎት

የኢትዮጵያ አየር መንገድ የኢ-ኮሜርስ ካርጎ (የኢንተርኔት ግብይት አቅርቦት) አገልግሎትን ተቀላቀለ፡፡ አየር መንገዱ በቦሌ ዓለማቀፍ አየር ማረፊያ ያስገነባው የኢ-ኮሜርስ አገልግሎት መሰረተ ልማቱን አጠናቆ ዛሬ አስመርቋል፡፡ በ15 ሺህ ሄክታር መሬት ላይ በ55 ሚሊየን ዶላር የተገነባው ይህ ዘመናዊ የካርጎ አገልግሎት ማሳለጪ ማዕከል በየዓመቱ 150 ቶን እቃዎችን ተቀብሎ ለደንበኞች ማቅረብ የሚስችል ነው ተብሏል፡፡ አየር መንገዱ ይህን ዘመናዊ የአገልግሎት ማዕከል ገንብቶ ለማጠናቀቅ 2 ዓመት ተኩል እንደፈጀበትም ተነግሯል፡፡

የኢ-ኮሜርስ አገልግሎት ምንነት

“የኢ-ኮሜርስ አገልግሎት ወይም የእቃዎች የኦንላይን ግብይት ዛሬ በዓለማችን እየሰፋ የመጣው የንግድ አገልግሎት ነው፡፡ የኢትዮጵያ አየር መንገድ እስካሁን ሲሰጥ የነበረው የካርጎ አገልግሎት ደንበኞች እኛ ባለንበት አምጥተው አስረክበውን ወስደን ስልክ ደውለን የምናስረክብበት የተለመደ አሰራር ነው” ብለዋል የኢትዮጵያ አየር መንገድ ዋና ስራ አስፈጻሚ መስፍን ጣሰው ፡፡
ዛሬ ግን አየር መንገዱ በተለያዩ አገራት እየተለመደ የመጣውን የኢ-ኮሜርስ አገልግሎት በይፋ መቀላቀሉን ስገልጽ ለአገልግሎቱ የሚውል ዘመናዊ የኢ-ኮሜርስ ካርጎ አገልግሎት መስጪ ማዕከሉን በይፋ በማስመረቅ ነው፡፡ ኢትዮጵያን ጨምሮ በ17 አገሮች የአፍሪካ አንድ ወጥ የአየር ትራንስፖርት ገበያ ሊጀመር ነውእንደ ዋና ስራ አስፈጻሚው ገለጻ አየር መንገዱ አሁን የተቀላቀለው የኢ-ኮሜርስ አገልግሎት ከተለመደው አሰራር እጅግ ይሰፋል፡፡ “ይህ አገልግሎት ደንበኞች እቃቸውን ኦንላይን ፈልገው በእራሳቸው አዝዘው ገዝተው እቃው እቤታቸው ድረስ የሚደርስበት አሰራር ነው” ያሉት አቶ መስፍን እያደገ የመጣውን መሰል ግብይት አየር መንገዱ አሁን ላይ መቀላቀሉ አስፈላጊ ነው ብለዋል፡፡

የኢትዮጵያ አየር መንገድ የኢ-ኮሜርስ ካርጎ አገልግሎት ምረቃ ስነ ስርዓት
የኢትዮጵያ አየር መንገድ የኢ-ኮሜርስ ካርጎ አገልግሎት ምረቃ ስነ ስርዓትምስል Seyoum Getu/DW

የኢ-ኮሜርስ ካርጎ ፋይዳ


የአየር ካርጎ አገልገሎቱ ወደ ኢ-ኮሜርስ አገልግሎት ማደግ አለበት ያሉት የኢትዮጵያ አየር መንገድ ዋና ስራ አስፈጻሚው፤ ዛሬ ግንባታው ተጠናቆ የተመረቀው የካርኮ መጋዘን አገልግሎቱ የሚለይበትን መንገድም አስረድተዋል፡፡ “ዛሬ ያስመረቅነው የካርጎ መጋዘን ከተለመደው የሚለየው፤ ትናንሽ እቃዎችን በጥቅል መጥተው ግን እዚህ ተበትነው ለደንበኞች የሚደርሱበት አሰራር የሚዘረጋ ነው፡፡ የኢትዮጵያ አየር መንገድም እያደገ የመጣውን ዘርፉን መቀላቀሉን አረጋግጧል” ነው ያሉት፡፡ 
አቶ አቤል ዓለሙ ደግሞ በኢትዮጵያ አየር መንገድ የካርጎ እና ሎጂስቲክ አገልግሎት ማኔጂንግ ዳይሬክተር ናቸው፡፡ እሳቸውም አየር መንገዱ ዛሬ የጀመረው የኢ-ኮሜርስ ካርጎ አገልግሎት በዘመናዊ ቴክኖሎጂ የተደገፈና አገልግሎትን የሚያቀላትፍ ነው ይላሉ፡፡ “ከዚህ ቀደም ከተለመደው አሰራር በተጨማሪ ጥቃቅን እቃዎችን ተቀብሎ ወደ ተለያዩ ዓለም የሚልክበት እና ተቀብሎ እዚህም ለደንበኞች የሚከፋፍልበት አሰራር ነው” ብለዋል፡፡

አቶ መስፍን ጣሰው የኢትዮጵያ አየር መንገድ ዋና ስራ አስፈጻሚ
አቶ መስፍን ጣሰው የኢትዮጵያ አየር መንገድ ዋና ስራ አስፈጻሚ ምስል Seyoum Getu/DW

ዘርፉን ለመቀላቀል በአፍሪካ ቀዳሚ አየርመንገድ

 

በተለያዩ የሰለጠኑ አገራት እየተለመደ መምጣቱ የሚነገርለት የኢኮሜርስ ካርጎ አገልግሎትን የኢትዮጵያ አየር መንገድ ዛሬ የተቀላቀለው በአፍሪካ የመጀመሪያው አየር መንገድ በመሆን ነው ተብሏል፡፡ በዚህም አየር መንገዱ ከዘመኑ ቴክኖሎጂ ጋር የመራመድ አቅምና ፍላጎቱን የሚያሳይ ስለመሆኑ ነው የተገለጸው፡፡
የኢትዮጵያ አየር መንገድ ባለፈው ዓመት 6.13 ቢሊየን ዶላር ገቢ አስገኝቷል፡፡ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ምርትና አገልግሎት ከዚህ ውስጥ 30 በመቶውን ድርሻ የሚይዘው የካርጎ አገልግሎት ስለመሆኑም ተገልጿል፡፡ ዛሬ በይፋ የተጀመረው የኢ-ኮሜርስ ካርጎ አገልግሎትም ከዚህ አኳያ የአየር መንገዱን የአገልግሎት አድማስ በማስፋት ገቢውንም ለማሳደግ እንደሚግዝ ታምኗል፡፡
የኢትዮጵያ አየር መንገድ ዛሬ ዘመናዊውን የኢ-ኮሜርስ አገልግሎት ካርጎ ሲያስመርቅ የመንግስት ከፍተኛ ባለስልጣናት፣ ዲፕሎማቶች እና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ታድመዋል፡፡ የኢትዮጵያ አየር መንገድ በተለያዩ ጊዜያት በአገልግሎት ዘርፉ በርካታ ዓለማቀፍ ሽልማቶችን ያሸነፈ ነው፡፡ በዘንድሮው 2023ም አራት ግዙፍ ሽልማቶች መውሰዱ ተነግሯል፡፡

ስዩም ጌቱ
ኂሩት መለሰ
ማንተጋፍቶት ስለሺ