1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የአፍሪቃና ጀርመን የመረጃ ማዕከል በሐምቡርግ

ማክሰኞ፣ ጥቅምት 2 2014

በ«አፍሪቃና ጀርመን የመረጃ ማዕከል»እርዳታ የትምሕርት ማስረጃዎቻቸው እውቅና አግኝተው በሙያቸው ስራ መያዝ የቻሉ ተጨማሪ ትምሕርትና ስልጠና የማግኘት እድል የገጠማቸው ብዙ ሴት አፍሪቃውያን አሉ።በአሁኑ ጊዜም የትምህርት ማስረጃዎቻቸውን ለማዕከሉ አቅርበው በጀርመን የሰነዶቻቸውን እውቅናና የስራ እድል በመጠባበቅ ላይ ያሉ ስደተኞች ጥቂት አይደሉም።

https://p.dw.com/p/41adj
BG Deutschland steht still | Hamburger Hafen
ምስል Getty Images/AFP/M. Mac Matzen

የአፍሪቃና ጀርመን የመረጃ ማዕከል በሐምቡርግ

ሰሜን ጀርመን የምትገኘው ሀምቡርግ ከአስራ ስድስቱ የጀርመን ፌደራል ክፍላተ ሀገር አንዷ ናት። ይህች ትልቅ የወደብ ከተማ በህዝብ ብዛት ቀዳሚውን ቦታ ከሚይዘው ከጀርመን ዋና ከተማ በርሊን ቀጥሎ ሁለተኛ ደረጃ ላይ ትገኛለች። ሽሌሽቪግ ሆልሽታይንና ኒደርዛክሰን በሚባሉት ሁለት የጀርመን ግዛቶች የተከበበችው ሀምቡርግ ከኔዘርላንዱ ሮተርዳምና ከቤልጂጉ አንትወርፕ ቀጥሎ በአውሮጳ በትልቅነት ሦስተኛ ደረጃን የምትይዝ ወደብም ናት። በከተማይቱ የአማርኛና የግዕዝ ቋንቋ ትምሕርትና ጥናትና ምርምር የሚካሄድበት የሐምቡርግ ዩኒቨርስቲም ይገኛል።ሐምቡርግ የተሰናባቿ የጀርመን መራኂተ መንግሥት የአንጌላ ሜርክልና የቀድሞው የጀርመን መራኄ መንግሥት ሄልሙት ኮል የትውልድ ስፍራም ናት።እግረ መንገዴን ስለሐምቡርግ ጥቂት አነሳሁ እንጂ የዛሬው ዝግጅት ትኩረት በከተማይቱ ሴት አፍሪቃውያን ስደተኞችን ለማገዝ የተቋቋመ መንግሥታዊ ያልሆነ ድርጅትና ኢትዮጵያዊቷ የድርጅቱ ባልደረባ ሳልሳዊት አሰፋ ናቸው። 
ከሌሎች የጀርመን ግዛቶች ጋር ሲነጻጸር በሀምቡርግ ያላቀ ቁጥር ያላቸው አፍሪቃውያን ይገኛሉ።ከመካከላቸው የሴት አፍሪቃውያን የትምህርት ማስረጃዎች በጀርመን እውቅና እንዲሰጣቸው በመርዳት የስራ እድል የሚያገኙበትን መንገድ ማመቻቸት ዋነኛው ተግባሩ የሆነው«የጀርመን አፍሪቃ የመረጃ ማዕከል» አገልግሎቱን እንዴት እንደሚሰጥም የገለጸችው ሳልሳዊት የድርጅቱ ባልደረቦች ከተለያዩ የአፍሪቃ አገሮች የመጡ መሆናቸው ሴት አፍሪቃውያኑን ለመርዳት አመቺ ሁኔታ ፈጥሮልናልም ትላለች። ለወላጆችዋ ሶስተኛና የመጨረሻ ልጅ የሆነችው ሳልሳዊት ጀርመን ከመምጣትዋ በፊት ከአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ በስርዓተ ፆታና ልማት ጥናት የመጀመሪያ ዲግሪ አግኝታለች።ለአንድ ዓመት በኢትዮጵያ ሲቪል ሰርቪስ ዩኒቨርስቲ በአማካሪነት፣በመምህርነትና እና በጥናትና ምርምር ከሰራች በኋላ የነጻ ትምህርት እድል አግኝታ በመጣችበት በጀርመን ደግሞ በፐብሊክ ፖሊሲ ሁለተኛ ዲግሪ ይዛለች። የሳልሳዊት የሁለተኛ ዲግሪ መመረቂያ ጽሁፍና ሌሎችም በጀርመን የስራ ገበያ የአፍሪቃውያን ሴቶች ተሳትፎ ላይ ያተኮሩ ጥናቶች ፣በስራ ገበያው አፍሪቃውያን ሴቶችን የማገዙን አስፈላጊነት ያመለክታሉ። 
ሳልሳዊት እንደምትለው በ«አፍሪቃና ጀርመን የመረጃ ማዕከል» እርዳታ የትምሕርት ማስረጃዎቻቸው እውቅና አግኝተው በሙያቸው ስራ መያዝ የቻሉ ተጨማሪ ትምሕርትና ስልጠና የማግኘት እድል የገጠማቸው ብዙ ሴት አፍሪቃውያን አሉ። በአሁኑ ጊዜም የትምህርት ማስረጃዎቻቸውን ለማዕከሉ አቅርበው በጀርመን የሰነዶቻቸውን እውቅናና የስራ እድል  በመጠባበቅ ላይ ያሉ ስደተኞች ጥቂት አይደሉም። ከመካከላቸው ኢትዮጵያውያንና ኤርትራውያን ስደተኞች ይገኙበታል።
 

Symbolbild I CUM EX Der Hauptsitz der Privatbank M.M.Warburg & CO
ምስል Hanno Bode/imago images

ኂሩት መለሰ