1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የብሪክስ ጉባኤ በጁሐንስበርግ-ደቡብ አፍሪቃ

ረቡዕ፣ ነሐሴ 17 2015

በዓለማቀፉ የንግድ ልውውጥ፤ የፋይናንስ ተቁማትና ሌሎችም ላይ የሚነሱት ጥይቄዎች ተጠንክረው እንዲቀርቡና በሂደትም አዲስ አለማቀፍዊ ስርዓት እንዲፈጠር የሚያስችል ሊሆን ይችላል በማለትም ተንታኞች በቀጣይ ሊካሂድ የሚችለውን የፖለቲካ ትግልና የኃይል አሰላለፍ ለውጥ ያመላክታሉ።

https://p.dw.com/p/4VVvS
በጁሐንስበርጉ ጉባኤ ላይ በአካል የተሳፉት የብሪክስ አባል ሐገራት 4 መሪዎችና የሩሲያ ዉጪ ጉዳይ ሚንስትር
በጁሐንስበርጉ ጉባኤ ላይ በአካል የተሳፉት የብሪክስ አባል ሐገራት 4 መሪዎችና የሩሲያ ዉጪ ጉዳይ ሚንስትር ምስል Alet Pretorius/REUTERS

የብሪክስ ጉባኤ

ብራዚል፣ ሩሲያ፣ ህንድ፣ ቻይናና ደቡብ አፍርካ የተካተቱበት በዓለማችን  በፍጥነት በማደግ ላይ ያሉ አገሮች ስብሰብ በእንግሊዝኛ ምህጻሩ ብሪክስ 15ኛ ጉባኤ በደቡብ አፍርካ ጆሀንስበርግ ከተማ ከትናንት ጀምሮ ለሦስት ቀናት በመካሄድ ላይ ነው።
የጉባኤው አስተናጋጅ አገር ደቡብ አፍርቃ መሪ ፕሬዝዳንት ራማፉዛ  በጉባኤው መክፈቻ ባሰሙት ንግግር፤ የዚህ ዓመቱን ጉባኤ መርኆዎች አመላክተዋል። “ዐስራ አምስተኛው የብሪክስ ጉባኤ መርኆዎች፤ የብሪክስና አፍርቃ የጋራ እድገት፣  ዘላቂ ልማትና አቃፊ አለማቀፍዊነት የሚሉት ናቸው” በማለት ብሪክስ  በመንግስታት መከካል ያለውን ብቻ ሳይሆን፤ የህዝብ ለህዝብ ግንኑነቶችን ጭምር ለማጠናከር የሚሰራ መሆኑን ገልጸዋል። 
በጉባኤው እንዲገኙ  ለ 67 አገሮችና በርካታ ዓለማቀፍ ድርጅቶች ተወክዮችና ባለሐብቶች የግብዣ ጥሪ የተላለፈ ሲሆን፤  ከአምሳ በላይ የአገር መሪዎችና ተወካዮች፤ በርካታ የቢዝነስና የፋይናንስ መሪዎች  ተገኝተዋል።  ከብሪክስ አባል አገሮች ፕሬዝደንት ፑቲን ብቻ በዓለማቀፉ ፍርድ ቤት ከተመስረተባቸው ክስ ጋር በተያያዘ  በውጭ ጉዳይ ሚኒስትራቸው ተወክለዋል። 
የብሪክስ ጉባኤ በየዓመቱ በዙር የሚካሄድ ቢሆንም የዚህ ዓመቱ ጉባኤግን ከመቸውም ጊዜ ይበልጥ  የዓለምን ትኩረት የሳበና በተለይ አሜሪካና አውሮፓ በአንክሮ የሚመለክቱት ሁኗል። በጆህንስ በርግ ዩኒቨርስቲ የዓለማቀፍ ግንኑነት ኤስክፐርት የሆኑት ፕሮፈሰር ድቪድ ሞንየ እንደሚሉትም አሁን በጆሃንስበርግ እየተካሄደ ያለው የብሪክስ ጉባኤ ከቀድሞዎቹ የለያል። “ይህ ጉባኤ ከሌሎች የተለየ ነው። ምክኒያቱም በዩክሬን ጦርነት እየተካሄደ ባለበት ወቅት የሚካሄድ በመሆኑንና በኃያላኑ መንግስታት መካከልም በአየር ንብረት በመሳሰሉትና ሌሎች አጀንዳዎች ውጥረት ባየለበት ግዜና  በርካታ አገሮችም  ብሪክስን ለመቀላቀል  ጥያቄ እያቀረቡ ባለበት ወቅት የሚካሂድ በመሆኑ ነው`` ሲሉ ገልጸዋል።
ጉባኤው በዓለም ሰላም፣ በንግድና በአየር ንብረት ለውጥ ፤ በምግብ ዋስትና በመሳሰሉት ወሳኝ አጀንዳዎች እንደሚወያይ  የታወቀ ሲሆን ፤ የቡድኑ አባል ለመሆን እየቀረቡ ባሉት ጥያቄዎችና የአባልነት መስፈርቶች ጉዳይ  ዋናው የጉባኤው አጀንዳ እንደሚሆን ተጠብቋል። የብሪክስ አባል ለመሆን ከአርባ በላይ አገሮች ፍላጎት እንዳስዩ የተገለጸ ሲሆን፤ ሳኡዲ  አረቢያ፤ አርጀንቲና አልጀሪያን፤  ግብጽና ኢትዮጵያን ጨምሮ 23 አገሮች በይፋ ድርጅቱን ለመቀላቀል ጥያቄ ማቅረባቸው ታውቋል።
የብሪክስ አገሮች ከአሜርካ መራሹ የምራባውያን አገሮች አንጻር የቆሙ መሆኑ ቢታምነም፤ በአንድንድ ጉዳዮች በመካከላቸውም ልዩነቶች እንዳሉ ነው የሚነገረው። ያም ሆኖ ግን  የደቡብ አፍሪቃው ኤሚሪት ፕሮፌሰር አንድሬ ቶማሻውዘን  እንደሚሉት፤በዓለም ሰላም፤ ገጭቶችና አለመግብባቶች ሊፈቱ በሚችሉበት ሁኔታ፤ ሁሉም ተመሳሳይ ፍላጎትና አቋም አላቸው። “ አንዱ ትልቁ የሚስማሙበት ነጥብ ሁሉም ልዩነቶችና፣ ግጭቶች በውይይትና በመደማመጥ እንጂ በመጯጯህና በመወጋገዝ የሚፈቱ አለመሆኑን ማመናቸው ነው። ይህ ደግሞ  አሁን የምራቡ ዓለም ከሚያደርገው የተለየ ነው። ምራቡ አለም አስቀድሞ ይበይናል፤ ቀጥሎ ያወግዛል በማለት  የብሪክስ መሪዎች ልዩነቶችና አለመግባባቶች በወታደራዊ ሀይል ሊፈታ  እንደማ ይችል ያምናሉ ብለዋል ። 
ጉባኤው ሲጠናቀቅ በስብስቡ ሊገቡ የሚፈልጉ አገሮች የሚስተናገዱበትን አሠራር ፤ ከዶላር ውጭ በመካከላቸው ያለው ንግድ የሚሳለጥበት  ስልትና የዓለማቀፉ ስርዓት ፍትሐዊ በሆነ መልኩ እንዲሻሻል የሚጠይቁ ውሳኔዎችም የሚተላለፉበት ይሆናል ተብሎ ይጠበቃል። 
 ብሪክስ ለመግባት የሚፈልጉ አገሮች ቁጥር መጨመሩ አሜሪካ ትዘውረዋለች የሚባለው የዓለም የንግድ፣ ፋይናንስና የፖለቲካ ስርዓትን ለማሻሻል የሚደረገውን  ትግል ያጠናክረዋል እየተባለ ነው።  በመንግስታቱ ድርጅት ያለው አሠራርና ውክልና ፤ በዓለማቀፉ የንግድ ልውውጥ፤ የፋይናንስ ተቁማትና ሌሎችም ላይ የሚነሱት ጥይቄዎች ተጠንክረው እንዲቀርቡና በሂደትም  አዲስ አለማቀፍዊ ስርዓት እንዲፈጠር የሚያስችል ሊሆን ይችላል በማለትም ተንታኞች በቀጣይ ሊካሂድ የሚችለውን የፖለቲካ ትግልና የኃይል አሰላለፍ ለውጥ ያመላክታሉ። 
 እእእ ከ2010 ጀምሮ በአሁኑ ቅርጹ እውን የሆነው ብሪክስ አባል አገሮች፤ የዓለማችን ህዝብ 40 ከመቶው የሚገኝባቸው፤ የዓለም  አጠቃላይ ኢኮኖሚ ምርት (GDP) ፤ 26 ከመቶ ባለቤቶችና 16 ከመቶ የዓለም ንግድ የሚካሄድባቸው፤ በተለይ ደግሞ ካለፉት ጥቂት ዓመመታት ወዲህ ዋና የዓለም ኢኮኖሚ እድገት ሞተሮች በመሆን የሚጠቀሱ ናቸው።፡
ገበያው ንጉሤ
ዮሃንስ ገብረእግዚአብሄር
ማንተጋፍቶት ስለሺ

የደቡብ አፍሪቃው ፕሬዚደንት ሲሪልራማፎዛ
የደቡብ አፍሪቃው ፕሬዚደንት ሲሪልራማፎዛ በብሪክስ ጉባኤ የመክፈቻ ንግግር ሲያደርጉምስል Sergei Bobylev/imago images/ITAR-TASS