1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

«ቁጥራቸው 200 ሺህ የሚጠጋ ዜጎች ድጋፍ ይደረግላቸዋል»

ረቡዕ፣ ሐምሌ 20 2014

በምሰራቅ ወለጋ ዞን ኪራሙ ወረዳ በርካታ የተፈናቀሉ ዜጎች እንደሚገኙ የዞኑ አስተዳደር ገልጸዋል፡፡ ወደ ከተማ ተፈናቅለው የነበሩ ዜጎችም ወረዳውን ከሌላ አካባቢ ጋር የሚያገናኝ መንገድ ለረጅም ጊዜ በመዘጋቱ ለችግር መጋለጣቸውን በተደጋጋሚ ሲገልጹ ቆይተዋል፡፡ በወረዳው የሐሮ ቀበሌ ነዋሪ እንዳሉት ድጋፍ የሚያገኙት አልፎ አልፎ ነው።

https://p.dw.com/p/4Ej1E
Äthiopien Assosa Flüchtlinge
ምስል Negassa Dessalegn/DW

የምሥራቅ ወለጋ ተፈናቃዮች ይዞታ

የምስራቅ ወለጋ "ቡሳ ጎኖፋ" ጽ/ቤት የቀድሞ  የአደጋ ስጋት ስራ አመራር ፣ በዞኑ በነበረው የፀጥታ ችግር ምክንያት የተፈናቀሉ 2 መቶ ሺ የሚጠጉ ዜጎች በድጋፍ እንደሚተዳደሩ ገለጸ፡፡ በዞኑ በሰው ሰራሽ አደጋዎች  በዚህን ዓመት ሰዎች ከገጠራማ ስፍራ እየተፈናቀሉ በየከተማው ተጠልለው ቆይተዋል።ከተፈናቀሉት መካከል 110ሺሁ ወደቤታቸው የተመለሱ እና ድጋፍ የሚሰጣቸው መሆናቸውን  የምሥራቅ ወለጋ ዞን ቡሳ ጎኖፋ ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ዳኜ ለቺሳ ተናግረዋል፡፡ በዞኑ ውስጥ ከተፈናቀሉት በተጨማሪ ከአጎራባች ምዕራብ ወለጋ እና ቤኒሻንጉል ጉሙዝ የተፈናቀሉ 30ሺ ተፈናቃዩች በዞኑ ውስጥ ይገኛሉ ብሏል፡፡

ከጥቅምት/2014 ዓ.ም አንስቶ በምስራቅ ወለጋ ዞን የተለያዩ ወረዳዎች ውስጥ በፀጥታ ችግር ምክንያት በሺዎች የሚቆጠሩ ዜጎች ተፈናቅለው እንደነበር የዞኑ ቡሳ ጎኖፋ ጽ/ቤት አስታውቋል፡፡ በዞኑ ስር ከሚገኙት 17 ወረዳዎች መካከል በ13ቱ ወረዳዎች ውስጥ ሰዎች በፀጥታ ችግርም ሆነ በስጋት መፈናቀላቸውን የዞኑ ቡሳ ጎኖፋ ወይም የአደጋ ስጋት ስራ አመራር ኃላፊ አቶ ዳኜ ላቺሳ ለዶይቼ ቬለ ተናግረዋል፡፡ በምስራቅ ወለጋ ዞን እና  ዞኑን ከሚያዋስኑ አካባቢዎች የተፈናቀሉ ዜጎች በሐሮ ሊሙ፣ በሳሲጋ ወረዳ፣ ኪራሙ የሚባሉና ሌሎች 10 በሚደርሱት ወረዳዎች ውስጥ ተጥለልው እንደሚገኙም አመልክተዋል፡፡ የዞኑ አስተዳደርና በዞኑ ውስጥ በሚንቀሰቀሱ የግል ተቋማት በኩል ለተፈናቀሉ ዜጎች ሰብአዊ ድጋፍ መሰራጨቱን ኃላፊው ገልጸዋል፡፡

" በተለያዩ ጊዜያት በዞናችን ውስጥ በተከሰቱት ችግሮች ምክንያት በንብረትና በሰው ህይወት ላይ ጉዳት ደርሷል፡፡ ከምዕራብ ወለጋና ከቤኒሻንል ጉሙዝ ክልልም  ወደ ዞናችን የሸሹም አሉ ድጋፍ እተደረገላቸው ነው፡፡ እስካሁን እነሱን ጨምሮ በዞኑ ያለው የተፈናቃይ ቁጥር ወደ 2 መቶ ሺ የሚጠጋ ነው፡፡ ከሌሎች ስፍራዎች የመጡትን ጨምሮ ለሁሉም አስፈላጊውን ድጋፍ አድረሰናል፡፡ በኪራሙ ወረዳ 62ሺ ተፈናቃይ አለ፡፡ በትንሹ 30 ሺ የሚሆኑት ደግሞ  ከቤኒሻንጉል ጉሙዝ  የመጡ ናቸው፡፡ እነዚህ በሐሮ ሊሙና ሳሲጋ ወረዳ ላይ ይገኛሉ፡፡ ባጠቃላይ በ13 ወረዳዎች ውስጥ የተፈናቀሉ ዜጎች እየተረዱ ነው፡፡  46 ሺ ኩንታል የሚሆን የእህል ድጋፍ  እስካሁን  ለማድረስ ችለናል፡፡" ብሏል፡፡

በምሰራቅ ወለጋ ዞን ኪራሙ ወረዳ በርካታ የተፈናቀሉ ዜጎች እንደሚገኙ የዞኑ አስተዳደር ገልጸዋል፡፡ በወረዳው በነበረው አለመረጋጋት ወደ ከተማ ተፈናቅለው የነበሩ ዜጎችም ወረዳውን ከሌላ አካባቢ ጋር የሚያገናኝ መንገድ ለረጅም ጊዜ በመዘጋቱ ምክንያት ለችግር ተጋልጦ መቆየታቸውን በተደጋጋሚ  ሲገልጹ ቆይተዋል፡፡ በኪራሙ ወረዳ ሐሮ የሚባል ቀበሌ ነዋሪ የሆኑትና ስማቸውን እንዲጠቀስ ያልፈለጉ ነዋሪ ሰብአዊ ድጋፍ አልፎ አልፎ እንደሚደርሳቸው ተናግረዋል፡፡

የምስራቅ ወለጋ ዞን ቡሳ ጎኖፋ ኃላፊ አቶ ዳኜ ለቺሳ  ከዞናቸው ከፍተኛ የተፈናቃይ ቁጥር በኪራሙ ወረዳ እንደሚገኝ ተናግረዋል፡፡ ሰብአዊ ድጋፍ እጥረትን አስመልክቶ ነዋሪው ላቀረቡት ጥያቄ ሲመልሱ፣ በወረዳው ለረጅም ጊዜ በነበረው የጸጥታና የመንገድ ችግር ምክንያት ሰብአዊ ድጋፍ ወቅቱን ጠብቆ እንዳልደረሳቸው አስረድተዋል፡፡

"በኪራሙ ተፈናቅሎ ለሚገኙት ዜጎች ሁለት ዙር ሰብአዊ ድጋፍ  ተሰጥተዋል፡ በበነበረው የጸጥታ ችግር ምክንያት በቶሎ ሰብአዊ ድጋፍ  አለመድረስ ሁኔታዎች ነበሩ፡፡  ሰብአዊ ድጋፎች በትራንስፖርት እጥረትም ለረጅም ጊዜ አንድ ቦታ ተከማችቶ የቆየበት አጋጣሚዎችም ነበሩ፡፡ እስካሁን ግን ከተፈናቀሉት መካከል 110ሺ የሚሆኑት በ13ቱም ወረዳዎች ላይ ወደ ቤታቸው ተመልሰው ቤታቸው ሆነው እየተረዱ ይገኛሉ፡፡" ብለዋል፡፡

በምስራቅ ወለጋ ዞን  በመጋቢት ወር/2014 ዓ.ም  ጊዳ አያና በሚባል ወረዳ ውስጥ ተፈናቅሎ የነበሩ ከ13 ሺ በላይ ዜጎች ወደ ቀድሞ ቀአያቸው መመለሳቸውም ተገልጸዋል፡፡

 

ነጋሳ ደሳለኝ 

ኂሩት መለሰ