1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ዓብይዓዲ የሚገኙ ተፈናቃዮች ስሞታ

ሐሙስ፣ ሐምሌ 13 2015

"ምንጣፍ የለን፣ የምንበላው የለን፣ ባዶ ሆዳችንን ተኝተን እንዳናድር እንኳ ተባዮች አያስተኙን" በማለት ተፈናቃይዋ ለዶቼቬለ ተናግረዋል።ተፈናቃዮቹ «መንግስት ችግራችንን ተረድቶ እንዲፈታልን በተደጋጋሚ አቤት ብንልም የሚሰማን አጥተናል»ይላሉ።የትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር በረሃብ አደጋ ላይ ላሉ ተፈናቃዮች እህል ገዝቼ ለማቅረብ ወስኛለሁ ብሎ ነበር።

https://p.dw.com/p/4UAzV
Äthiopien Tigray | Vertriebene Menschen
ምስል Million Hailesilasse/DW

"ምንጣፍ የለን፣ የምንበላው የለን፣ ባዶ ሆዳችንን ተኝተን እንዳናድር እንኳ ተባዮች አያስተኙን" የዐቢይዓዲ ተፈናቃይ

በትግራይ ክልል በጦርነቱ ምክንያት ከቀዬአቸው የተፈናቀሉ ዜጎች ለከፍተኛ ችግር እንደተዳረጉ ገለጹ።  በክልሉ ተንቤን ዓብይዓዲ የሚገኙ ተፈናቃዮች በረሃብና ተያያዥ ምክንያቶች በርካቶች ለበሽታ መጋለጣቸው፣ የተፈናቃይ አስተባባሪዎች በሚባሉት መረጃ ደግሞ ጥቂት የማይባሉ እየሞቱ መሆኑ ተገልጿል።የክልሉ ግዚያዊ አስተዳደር ተፈናቃዮችን ከረሃብ አደጋ ለመታደግ እህል ገዝቶ ለማቅረብ መወሰኑን አስታውቋል። ከጦርነቱ መቆም 8 ወራት በኃላም ቢሆን ወደ ቀዬአቸው የመመለስ እድል ያላገኙ በትግራይ የሚገኙ ተፈናቃዮች የክረምት ወራት መግባትና የእርዳታ አቅርቦት መቋረጡን ተከትሎ ችግራቸው ወደ ከፋ ደረጃ እየተሸጋገረ መሆኑን ይገልፃሉ። በተለይም ከምዕራብ ትግራይ ተፈናቅለው በተለያዩ ትምህርት ቤቶች፣ ጊዚያዊ መጠልያዎች ያሉ ዜጎች ለከፍተኛ ረሃብ፣ በሽታ እና እርዛት መዳረጋቸው ይጠቁማሉ።የትግራይ ተፈናቃዮች የዕርዳታ ጥሪ

ሰሞኑን በተመለከትነው በተንቤን ዓብይዓዲ የሚገኙ በአብዛኛው ከምዕራብ ትግራይ ዞን የተለያዩ አካባቢዎች የተፈናቀሉ ዜጎች የኑሮ ሁኔታዎች አስከፊ ነው። በዓብይዓዲ መጠልያዎች ላሉ እስከ 80 ሺህ ይገምታሉ የተባሉ ተፈናቃዮች የምግብ ድጋፍ ከተደረገ ወራት ያለፉ ሲሆን፣ የሕክምና እና ንፁህ የመጠጥ ወሃ አገልግሎት ባለመኖሩ ደግሞ በየመጠልያው በርካቶች ታመው ይታያሉ።በዓብይዓዲ ከተማ በሚገኝ በተለምዶ ፕሪ ተብሎ የሚታወቅ የቀድሞ ትምህርት ቤት የአሁን የተፈናቃዮች መጠልያ ውስጥ ታማ ያገኘናት፣ ከምዕራብ ትግራይ ዞን ቆራሪት አካባቢ በ2013 ዓመተምህረት የተፈናቀለችው የሁለት ልጆች እናት ደበሱ ገብረሕይወት ፥ በመጠልያው ስላለው ህይወት ነግራናለች። "ምንጣፍ የለን፣ የምንበላው የለን፣ ባዶ ሆዳችን ተኝተን እንዳናድር እንኳ ተባዮች አያስተኙን" በማለት ወይዘሮዋ የከፋ ሕይወታቸውን ትገልፃለች። ተፈናቃዮቹ ችግራችንን ተረድቶ መንግስት እንዲፈታልን በተደጋጋሚ አቤት ብንልም የሚሰማን አጥተናል ይላሉ።

Äthiopien Tigray | Vertriebene Menschen
ምስል Million Hailesilasse/DW

ዓብይዓዲ በሚገኙ የተፈናቃዮች መጠልያዎች ውስጥ በአንድ ጠባብ የማስተማሪያ ክፍለ አስከ 50 ሰዎች ተጨናንቀው ሲኖሩ ይስተዋላል። አቶ ሐጎስ ገብረመድህን ከምዕራብ ትግራይ ዞን ፀገዴ ወረዳ በ2013 ዓመተምህረት ከመላ ቤተሰባቸው ጋር የተፈናቀሉ ናቸው። አሁን ዓብይዓዲ በሚገኙ መጠልያቸው የተፈናቃዮች አስተባባሪ ናቸው። ተፈናቃዩ አቶ ሐጎስ ለመጨረሻ ግዜ እርዳታ የተሰጠን ከሰባት ወር በፊት ነበር ይላሉ። በመጠልያቸው እስካሁን በርካቶች በረሃብ እና ተያያዥ በሽታዎች በርካቶች መሞታቸውን የገለፁልን አቶ ሐጎስ፥ ካለፈው ይልቅ የሚመጣው ግዜ አሳሳቢ ነው ይላሉ።የትግራይ ሴት ተፈናቃዮች

የትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር ፣ተፈናቃዮችን ወደ ቀዬአቸው በዘላቂነት ለመመለስ ከሚያደርገው ስራ በተጨማሪ በአሁኑ ጊዜ በረሃብ አደጋ ላይ ያሉ ተፈናቃዮችን ለመርዳት እህል ገዝቶ ለማቅረብ መወሰኑን የግዚያዊ አስተዳደሩ ፕሬዝደንት ጌታቸው ረዳ በቅርቡ ተፈናቃዮች አስመልክተው ሲናገሩ ጠቁመዋል።ያነጋገርናቸው ተፈናቃዮች በአፋጣኝ ከሚሹት የምግብ እርዳታ አቅርቦት በተጨማሪ ወደ ቀዬአቸው የሚመለሱበት አግባብ ማመቻቸት የመንግስት ቀዳሚ ተግባር እንዲሆን ይጠይቃሉ።

 

ሚሊዮን ኃይለ ሥላሴ

ኂሩት መለሰ

ዮሐንስ ገብረ እግዚአብሔር