1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ዉይይት፣ የኢትዮጵያ ጦር ለቅቆ ወጣ ወይስ ተሸነፈ

እሑድ፣ ሰኔ 27 2013

የሐገሪቱ ባለስልጣናት ጦሩን ከየአካባቢዎቹ ለማስወጣታቸዉ ከጠቀሷቸዉ ምክንያቶች፣ ሕወሓት ሥጋትነቱ በመቀነሱ፣ ትግራይ ዉስጥ ለሚደርሰዉ ጥፋት ሁሉ መንግስት ብቻ ተጠያቂ በመሆኑ፣ ገበሬዉ የዘንድሮዉን መሕር እንዲያዘምርበት፣ ሰብአዊ ርዳትም እንዲደርስ፣ ከዉጪ መንግስታት ከፍተኛ ጫና በመደረጉ ነዉ የሚሉት ጥቂቶቹ ናቸዉ።

https://p.dw.com/p/3vxXb
Äthiopien | Jubel beim Einmarsch der TDF in Mekelle
ምስል DW

የጦርነቱ የኃይል ሚዛን ለዉጥና ሥጋቱ

 

የኢትዮጵያና የኤርትራ መንግስታት ወታደሮች ከቀድሞዉ የትግራይ  ገዢ ፓርቲ ከሕዝባዊ ወያኔ ሓርነት ትግራይ (ሕወሓት) ታጣቂዎች ጋር ካለፈዉ ጥቅምት ጀምሮ ትግራይ ዉስጥ የገጠሙት ዉጊያ ባለፈዉ ሰኞ የ8 ወሩ የኃይል ሚዛን፣መልክና ባሕሪዉም ተለዉጧል።

የኢትዮጵያ መንግስት የተናጥል ተኩስ አቁም አዉጆ ትግራይ ርዕሠ-ከተማ መቀሌን ይቆጣጠር የነበረዉን ጦሩንና የክልሉን ጊዚያዊ አስተዳደር ባለስልጣናትን ባለፈዉ ሰኞ ከከተማይቱ አስወጥቷል።የኤርትራ ጦርም አድዋን፣ አክሱምንና ሽሬን የመሳሰሉ ትላልቅ ከተሞችን ለቅቆ መዉጣቱ ተዘግቧል።የሕወሓት ባለስልጣናትና ተዋጊዎች ባንፃሩ የተለቀቁን አካባቢዎች መቆጣጠራቸዉ እየተዘገበ ነዉ።እንደሰማነዉ የየከተማዉ ሕዝብም አማፂያኑን በጭፈራና ፌስታ ተቀብሏቸዋል።

የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚንስትር ዓብይ አሕመድን ጨምሮ የሐገሪቱ ባለስልጣናት ጦሩን ከየአካባቢዎቹ ለማስወጣታቸዉ ከጠቀሷቸዉ ምክንያቶች፣ ሕወሓት ሥጋትነቱ በመቀነሱ፣ ትግራይ ዉስጥ ለሚደርሰዉ ጥፋት ሁሉ መንግስት ብቻ ተጠያቂ በመሆኑ፣ ገበሬዉ የዘንድሮዉን መሕር እንዲያዘምርበት፣ ሰብአዊ ርዳትም እንዲደርስ፣ ከዉጪ መንግስታት ከፍተኛ ጫና በመደረጉ ነዉ የሚሉት ጥቂቶቹ ናቸዉ።ጦሩን ከትግራይ አካባቢዎች  የማስወጣቱ ዉሳኔም ፖለቲካዊ እንደሆነ የመንግስት ባለስልጣናት አስታዉቀዋል።

የሕወሓት ባለስልጣናት ሮይተርስን ለመሰሉ በስልክ ለሚያገኟቸዉ መገናኛ ዘዴዎች እንደገለፁት ግን የሁለቱም ሐገራት ወታደሮች ከየአካባቢዉ ለቅቀዉ የወጡት «ተሸንፈዉ ነዉ» ባይ ናቸዉ። የሕወሓት  ቃል አቀባይ አቶ ጌታቸዉ ረዳ ከዚሕም በተጨማሪ «እያንዳዷ ኢንች የትግራይ ግዛት ከጠላት እጅ ነፃ እስክትወጣ» ድረስ ዉጊያዉ እንደሚቀጥል ዝተዋልም።

Äthiopien I Konfliktregion Tigray
ምስል Ethiopian News Agency/AP/picture alliance

የኢትዮጵያ መከላከያ ሚንስቴር የሠራዊት ግንባታዎች ዋና አስተባባሪ ሌትናንት ጄኔራል ባጫ ደበሌ ባለፈዉ ሮብ ለዛቻዉ የሰጡት አፀፋ ዛቻ ነዉ።ጦሩ ከተጠቃ «ጁንታ» ያሉትን ሕወሓትን «የገባበት ገብቶ ይመታል»፤ ድንበር አያግደዉም ብለዋልም።እዉነቱ የትኛዉ ነዉ? ደግሞስ 8ት ወር ባስቆጠረዉ ዉጊያ  ብዙ ሠላማዊ ሰዉ እንዳለቀ፤ እንደተራበ፣ እንደተፈናቀለ ሁሉ የዉጊያ፣ ዛቻ፣ ፉከራዉ መካረር የሌላ ጥፋት ምልክት መሆኑም እያሰጋ ነዉ።እዉነቱ፣ ሥጋትና እንዴትነቱ ያፍታ ዉይይታችን ትኩረት ነዉ።ሶስት እንግዶች አሉን።

Äthiopien I Konfliktregion Tigray
ምስል Minasse Wondimu Hailu/AA/picture alliance

ነጋሽ መሐመድ