1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል
ትምህርትአፍሪቃ

ከተፈተኑት 96 ከመቶ ተማሪዎች «ወደቁ»

ዓርብ፣ ጥር 19 2015

ያለፉት ግን 30 ሺሕ አይሞላም።ከተፈተነዉ ተማሪ ከ96 የሚበልጠዉ በቂ ዉጤት ያለመጣበት ፈተና የተሰጠዉ እስከ አምና ከነበረዉ በተለየ መንገድ በየከፍተኛ ትምሕርት ተቋማት ነበር

https://p.dw.com/p/4MnbJ
Äthiopien Bildungsministerium gibt ESLCE Endergebnis bekannt
ምስል Solomon MUCHIE/DW

«የትምሕርት ሥርዓቱ ዉድቀት ማሳያ» ብርሐኑ ነጋ

ኢትዮጵያ ዉስጥ አምና የ12ኛ ክፍል ብሔራዊ ፈተና ከወሰዱ ተማሪዎች ከፍተኛ የትምሕርት ተቋማት መማር የሚያስችላቸዉን ዉጤት ያመጡት 3 በመቶ ብቻ መሆናቸዉን የትምሕርት ሚንስቴር አስታወቀ።የ12ኛ ክፍል መልቀቂያ ብሔራዊ ፈተና የወሰዱት ተማሪዎች ቁጥር ለ900 ሺህ ጥቂት  የቀረዉ ነዉ።ያለፉት ግን 30 ሺሕ አይሞላም።ከተፈተነዉ ተማሪ  ከ96 የሚበልጠዉ በቂ ዉጤት ያለመጣበት ፈተና የተሰጠዉ እስከ አምና ከነበረዉ በተለየ መንገድ በየከፍተኛ ትምሕርት ተቋማት ነበር።የትምሕርት ሚንስትር ብርሐኑ ነጋ የዉጤቱን ዝቅተኛነት «የትምህርት ሥርዓቱ ዉድቀት ማሳያ» ብለዉታል።

በ2014 ዓ .ም የትምህርት ዘመን የ12ኛ ክፍል ለብሔራዊ ፈተና ወይም ለምዘና የተመዘገቡት 985 ሺህ 354 ቢሆኑም
77 ሺህ 98 ተማሪዎች ለመፈተን ተመዝግበው ፈተና ሳይወስዱ በመቅረታቸው እና በደንብ ጥሰት ደግሞ 20,170 ስለተቀጡ ለፈተና የተቀመጡት 896 ሺህ 520 ተማሪዎች ናቸው። ውጤቱም አጠቃላይ የኢትዮጵያ የትምህርት ሥርዓት ውድቀት ማሳያ ነው ተብሏል።
የትምህርት ሚኒስትሩ ብርሃኑ ነጋ በዚህ ዓመት ወደ ዩኒቨርሲቲ ገብተው ለመማር የሚያስችል ከ 50 በመቶ በላይ ውጤት ያስመዘገቡት 3.3 ወይም 30 ሺህ ያልሞሉ ተማሪዎች ናቸው። ከፍተኛ ቀጥር ያለው ተማሪ ዝቅተኛ ውጤት ያስመዘገበበት የዚህ ዓመት የ 12 ኛ ክፍል የፈተና ምዘና አሰጣጥ ከዚህ በፊት ከነበረው ለየት ባለ መልኩ ተማሪዎች ከትምህርት ቤቶቻቸው ርቀው በየ ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ገብተው የተፈተኑበት ነበር። የአመቱ ከፍተኛው ውጤት ከተፈጥሮ ሳይንስ ትምህርት የተመዘገበ ሲሆን ከ 700ው 666 ሆኖ ተመዝግቧል። ከ600 ከተያዘው የማህበራዊ ሳይንስ ደግሞ ከፍተኛው ውጤት 524 ሆኗል።

Äthiopien Bildungsministerium gibt ESLCE Endergebnis bekannt
የትምህርት ሚኒስቴር ሚንስትር ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ ምስል Solomon MUCHIE/DW

የትምህርት ሚኒስትሩ እንዳሉት 7 ትምህርት ቤቶች ያስፈተኗቸው ተማሪዎች ሙሉ በሙሉ ከ 50 በመቶ በላይ ውጤት ያስመዘገቡ ሲሆን አጠቃላይ 39.9 በመቶ የሚሆኑ ትምህርት ቤቶች ካስፈተኗቸው ውስጥ ምንም ተማሪ ማሳለፍ አልቻሉም። አዲስ አበባ እና ድሬዳዋ ከተሞች እንዲሁም ሀረሪ ክልል ከሌሎች ክልሎች የተሻለ ውጤት አስመዝግበዋል ያለው ትምህርት ሚኒስቴር አብዛኛዎቹ ክልሎች ግን እጅግ ዝቅተኛና ተቀራራቢ ውጤት የተመዘገበባቸው ናቸው።
ውጤታቸው ዝቅተኛ የሆነባቸው ተማሪዎች ለአንድ አመት ብቻ እንደየ ዩኒቨርሲቲዎቹ  የቅበላ አቅም ገብተው ዳግም ተምረውና ተፈትነው ወደ ዩኒቨርሲቲዎች እንዲገቡ እድል ይሰጣቸዋል ተብሏል።

የተመዘገበው ዝቅተኛ ውጤት ዝዘርፉ ምርምር፣ ጥናት ፣ ውይይት ሊደረግበት የሚገባ እና ከፍተኛ ለውጥ የሚደረግበት መሆኑን በግልጽ ያሳየ ነውም ተብሏል።

ሰለሞን ሙጬ

ነጋሽ መሐመድ

ታምራት ዲንሳ