በአማራ ክልል የኦሮሞ ብሔረሰብ አስተዳደር አዲስ አስተዳደር
ሰኞ፣ ሐምሌ 8 2016
በአማራ ክልል የኦሮሞ ብሔረሰብ አስተዳደር አፈጉባኤ ወ/ሮ ፋጡማ ሞላ ዛሬ ለዶይቼ ቬሌ እንደተናገሩት የብሔረሰብ አስተዳደሩ ምክርቤት ትናንት ባደረገው አስቸኳይ ጉባኤ የብሔረሰብ አስተዳደሩን አዲስ አስተዳዳሪና ሌሎች መምሪያ ኃላፊዎችን ሹመት አፅድቋል።
ምክር ቤቱ ወደ 12 አዳዲስ መምሪያ ኃላፊዎችን ሹመት ማፅደቁን የብሔረሰብ አስተዳደሩ የኮሙዩኒኬሽን መምሪያ ለዶይቼ ቬሌ የላከው የጽሑፍ መልዕክት ያመለክታል። ይህ ሹም ሽር ከቀድሞው የብሔረሰብ አስተዳደሩ ግድያ ጋር የተያያዘ እንደሆነ የጠየቅናቸው ወ/ሮ ፋጡም፣ «ግንኙነት የለውም፣ ግን እውቀትና ልምድ ያላቸው ወጣቶችን ወደ አመራር ለማምጣት ካለ ፍላጎት የመጣ ነው።» ብለዋል።
አዲሶቹ አመራሮች ከወረዳዎችና ከብሔረሰብ አስተዳደሩ የመጡ እንደሆኑ የገለጡት ወ/ሮ ፋጡማ፣ አዲሱ የብሔረሰብ አስተዳደር ተቀዳሚ ምክትል አስተዳዳሪ ሆነው የተሾሙት አቶ አህመድ አሊ አባፍሮም በዞንና በወረዳ በአመራርነት የሠሩ ወጣት መሪ እንደሆኑ አመልክተዋል።
ባለፈው ሰኔ 28 ቀን 2016 ዓም ከዓርብ ጸሎት ሲመለሱ በሰው እጅ በተገደሉት የቀድሞው ዋና አስተዳዳሪ አቶ አህመድ አሊ ኢብራሂም ሞት የብሔረሰብ አስተዳደሩ ሕዝብ በከፍተኛ ሀዘን ውስጥ እንደነበር ነው አፈ ጉባኤዋ ያመለከቱት። ሆኖም አሁን ኅብረተሰቡ ከነበረበት ሀዘን እየወጣ፤ በአካባቢውም ሰላምና መረጋጋት እየተፈጠረ ነውም ብለዋል።
አዲስ የብሔረሰብ አስተዳደሩ ተቀዳሚ ምክትል ዋና አስተዳዳሪ ሆነው የተሸሙት አቶ አህመድ አሊ አባፍሮ፣ የአዲሱ ካቢኔ ዋና ሥራ በብሔረሰብ አስተዳደሩ ሰላምና ፀጥታ ማስፈን እንደሆነ ለመገናኛ ብዙኀን ተናግረዋል፡፡
አስተያየት የሰጡ የአካባቢው ነዋሪዎች አዲሶቹ ወጣት አመራሮች ብሔረሰብ አስተዳደሩን ወደ ተሻለ ሰላምና መረጋጋት ያመጡታል ያሉ ሲሆን የቀድሞው ዋና አስተዳዳሪ ከአጎራባች ዞንና ወረዳ ነዋሪዎች ጋር የጀመሩትን አንድነት የማስቀጠል ኃላፊነትም አለባቸውም ብለዋል።
ዓለምነው መኮንን
ሸዋዬ ለገሠ
ታምራት ዲንሳ