1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

እንወያይ፣ የኢትዮጵያዉን ተፈናቃዮች ፈተና፣ የለጋሾች ዳተኝነት

ማክሰኞ፣ ሰኔ 25 2016

የተባበሩት መንግስታት ድርጅት፣ መንግስታት፣ ድርጅቶችና ሕዝብ ከ«ከስደተኞች ጋር እንዲተባበሩ በሚቀሰቅስበት ወቅት ታጣቂዎች አማራ ክልል የሠፈሩ የሱዳን ስደተኞችን መዝረፍ፣ቢያንስ አንዷን መግደላቸዉ ተዘግቧል።የትግራዩ ተፈናቃዮች ወደቀያቸዉ በየከተሞቹ አደባባዮች ተሰልፈዉ ነበር። አማራ ክልል የሠፈሩ ዜጎች ደግሞ ርዳታ እንዲደረግላቸዉ እየጠየቁ ነዉ

https://p.dw.com/p/4heNJ
በአብዛኛዉ ከኦሮሚያ የተፈናቃሉ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ሰዎች በቂ እርዳታ እንደማይደርሳቸዉ በተደጋጋሚ እያስታወቁ ነዉ
አማራ ክልል ጃራ መጠለያ ጣቢያ የሠፈሩ ተፈናቃዮች በቂ ርዳታ እንዲደረግላቸዉ በመጠየቅ ያደረጉት ሠልፍምስል Alemenw Mekonnen/DW

እንወያይ፣ የኢትዮጵያዉን ተፈናቃዮች ፈተና፣ የለጋሾች ዳተኝነት

የተባበሩት መንግስታት ድርጅት «ከስደተኞች ጋር እንተባበር» ባለዉ መሪ መፈክር የዘንድሮዉን የዓለም የስደተኞችና የተፈናቃዮችን ቀን ባለፈዉ ሳምንት አክብሯል።ድርጅቱ እንዳስታወቀዉ እስካለፈዉ ታሕሳስ ድረስ ከየቤት ንብረቱ ተገድዶ የተፈናቀለና የተሰደደዉ ሕዝብ ቁጥር ወደ 118 ሚሊዮን ደርሷል።
OCHA በሚል የእንግሊዝኛ ምሕፃረ ቃል የሚጠራዉ የተባበሩት መንግስታት የሠብአዊ ርዳታ ማስተባበሪያ ቢሮ የዛሬ ሁለት ሳምንት ግድም እንዳስታወቀዉ ኢትዮጵያ እስካለፈዉ ታሕሳስ ድረስ ወደ አንድ ሚሊዮን የሚሆኑ የዉጪ ስደተኞችን ታስተናግዳለች።አሁንም እስካለፈዉ ታሕሳስ ድረስ ጦርነት፣ ግጭት፣ ጥቃት፣ ድርቅና ጎርፍ ከቤት ንብረቱ ያፈናቀለዉ ኢትዮጵያ ቁጥር ደግሞ 4.5 ሚሊዮን ነዉ

የተባበሩት መንግስታት ድርጅት፣ መንግስታት፣ ድርጅቶችና ሕዝብ ከ«ከስደተኞች ጋር እንዲተባበሩ በሚቀሰቅስበት ወቅት ታጣቂዎች አማራ ክልል የሠፈሩ የሱዳን ስደተኞችን መዝረፍ፣ማጥቃት ቢያንስ አንዷን መግደላቸዉ ተዘግቧል።በትግራዩ ጦርነት ወቅት የተፈናቃሉ የክልሉ ነዋሪዎች ወደቀያቸዉ የሚመልሳቸዉ አጥተዉ ባለፈዉ ሳምት በየከተሞቹ አደባባዮች ተሰልፈዉ ነበር።ከኦሮሚያ ክልል ተፈናቃለዉ አማራ ክልል የሠፈሩ ዜጎች ደግሞ ርዳታ እንዲደረግላቸዉ በተደጋጋሚ እየጠየቁ ነዉ።

በተለይ ደቡብ ወሎ የሠፈሩ ተፈናቃዮች ፀጥታዉ በቅጡ ወዳልተረጋጋዉ የቀድሞ ቀያቸዉ እንዲመለሱ የሚደረግባቸዉን ጫና ባለመቀበላቸዉ ወትሮም በጣም አነስተኛ የሆነዉን የምግብና የዉሐ እርዳታ እንኳ ተነፍገናል እያሉ ነዉ።አብዛኛዉ ኢትዮጵያዊ ግን የዉጪዎቹ ተገን ጠያቂዎችም ሆነ የተፈናቃይ ወገኖቹ ብዛት፣ ችግርና ሥቃይ ብዙም ያሳሰባቸዉ አይመስልም።

 የስደተኛና የተፈናቃዮች ፈተና፣ የመፈናቀላቸዉ መሠረታዊ ምክንያቶችና መርዳት የሚችልና የሚገባዉ ወገን ቸልተኝነት  የዛሬ ዉይይታችን ትኩረት ነዉ።
የኢትዮጵያ የአደጋ ዝግጁነት ሥራ አመራር ኮሚሽን ባለሥልጣናት በዉይይቱ እንዲካፈሉ ለመጋበዝ ለሁለት ቀናት በተደጋጋሚ ስልክ ደዉለን ነበር።በስተመጨረሻ ያነጋገሩን የመስሪያ ቤቱ ቃል አቀባይ የተባሉ ግለሰብ መታወቂያና ጥያቄ አስቀድማችሁ ካላካችሁ የሚል ቅድመ ግዴታ ደርድረዉ ቀርተዋል።አራት እንግዶች አሉን።
1.ወይዘሮ ራኬብ መለሰ-----የኢትዮጵያ የሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን ምክትል ዋና ኮሚሽነር

ተፈናቃዮቹ እንደሚሉት በየሰፈሩበት መጠለያ ጣቢያ በቂ ርዳታ አያገኙም፣ ወደቀያቸዉ መመለስም አልቻሉም
በትግራይ ክልል በተደረገዉ ጦርነት ከቤት ንብረታቸዉ የተፈናቀሉ የክልሉ ነዋሪዎች ወደቀያቸዉ እንዲመለሱ ባደባባይ ሰልፍ ጠይቀዋል።ምስል Million Hailesilassie/DW

2.ዶክተር ሰናይት ደረጀ----ተመራማሪና የዘርማጥፋት ተከላካይ ድርጅት በኢትዮጵያ 

3.ዶክተር ሙከረም ሚፍታሕ-----የሲቪል ሰርቪስ ዩኒቨርስቲ መምሕርና የፖለቲካ ተንታኝ

4.አቶ ገረሱ ቱፋ-------የምሥራቅ አፍሪቃ ተነሳሽነት ለለዉጥ የፕሮግራም ኃላፊ ናቸዉ።
እንግዶቻችን በዚሕ ዉይይት ለመካፈል ፈቃደኛ በመሆናችዉ አመሰግናለሁ።

ነጋሽ መሐመድ