በፈረንሳይ ቀኝ ጽንፈኛው ፓርቲ የመጀመርያ ዙር የፓርላማ ምርጫን አሸነፈ
ሰኞ፣ ሰኔ 24 2016በፈረንሳይ ቀኝ ዘመሙ ፓርቲ የመጀመርያ ዙር የፓርላማ ምርጫን አሸነፈ
የአዉሮጳ ህብረት ምርጫ ውጤትን ተከትሎ በፈረንሳይ ትናንት በተካሄደዉ የመጀመርያ ዙር የምክር ቤት ምርጫ ናሽናል ራሊ» የተባለዉ ቀኝ ጽንፈኛ ፓርቲ አሸነፈ። የድምፅ ቆጠራዉ ተጠናቆ አሸናፊዉ እንደታወቀ፣ የፕሬዝዳንት ማክሮን ስብሰብ “ተጥረግርጎ ወጥቷል” ሲሉ ማሪን ለ ፔን ለደጋፊዎቻቸው ንግግር አድርገዋል። የላፔን ፓርቲ እስከዛሬ አግኝቶት የማያዉቀዉን 33 በመቶ ድምፅ በማግኘት ነዉ የመጀመርያዉን ዙር ምርጫ ትናንት ያሸነፈዉ። ግራ ዘመሙ ጥምር ፓርቲ 28.1 በመቶ ድምፅ ማግኘቱ ይፋ ሆንዋል።
በሦስተኝነት ዉድድሩን ያጠናቀቀዉ የፕሬዚደንት ኢማኑዌል ማክሮ ፓርቲ ደግሞ 20 በመቶ ድምጽ ብቻ ማግኘቱን የፈረንሳይ የሀገር ውስጥ ጉዳይ ሚኒስትቴር ዛሬ ይፋ ባደረገው ውጤት ተረጋግጧል። ቀኝ ጽንፈኛው የራሊ ናሽናል ፓርቲ ሌላዉ አመራር ጆርዳን ባርዴላ “ፈረንሳይዊያን ድምጻቸውን ከሰጡን የሁሉም ፈረንሳዊ ጠቅላይ ሚኒስትር እሆናለሁ” ብለዋል። በፈረንሳይ ታሪክ በፓርላማ ምርጫ ቀኝ ጽንፈኛ ፓርቲ አብላጫ ድምጽ አግኝቶ አያውቅም።
ይህ የፈረንሳይ ምርጫ የተደረገው ከታቀደለት ጊዜ ቀድሞ ነው። ከጥቂት ሳምንታት በፊት የፈረንሳዩ ፕሬዝዳንት ኤማኑኤል ማክሮ ተቀናቃኛቸው በአውሮጳ ኅብረት አገራት የፓርላማ ምርጫ ላይ ስኬት ማግኘታቸውን ተከትሎ የፈረንሳይ ፓርላማን በትነው አስቸኳይ ምርጫ መጥራታቸው ይታወሳል። በፈረንሳይ ፖለቲካ ውስጥ የማክሮ ተቀናቃኝ የሆኑት የማሪን ለ ፔን ቀኝ ጽፈኛ ናሽል ራሊ ፓርቲ በአውሮፓ የፓርላማ ምርጫ ስኬትን አስመዝግቧል። በአውሮፓ ፓርላማ ምርጫ ከፈረንሳዩ በተጨማሪ የጀርመን፣ የግሪክ፣ የፖላንድ እና የስፔን ቀኝ ዘመም ፓርቲዎች ስኬታማ መሆናቸው ይታወሳል። ስቱድዮ ከመግባታችን በፊት በፈረንሳይ ስለተካሄደዉ የፓርላማ ምርጫ እና ዉጤቱ ከፓሪስዋ ወኪላችን ጋር ቃለ መጠይቅ አድርገናል።
ሃይማኖት ጥሩነህ / አዜብ ታደሰ
ዮኃንስ ገብረእግዚአብሔር