1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

በደህንነት ስጋት ለተፈናቃዮች ዕርዳታ ማድረስ አለመቻሉ

ዓርብ፣ ሐምሌ 8 2014

በመንገድ መዘጋት ጸጥታ ችግር ለካማሺ ዞንና አሶሳ ዞን የተወሰኑ ቦታዎች ለሚገኙ ተፈናቃዩች እርዳታ ማድረስ አለመቻሉን የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል የአደጋ ስጋት ሥራ አመራር ኮሚሽን አስታወቀ፡፡ በጊምቢና ነቀምቴ አካባቢ ድጋፍ የጫኑ ከባድ ተሽከርካሪዎች ከወር በላይ በመቆዩታቸው የድጋፍ እጥረት እንዳጋጠማቸውም ተመልክቶዋል፡፡

https://p.dw.com/p/4ECdP
Äthiopien | Tarekegn Tassissa Benishangul-Gumuz
ምስል Negassa Dessalegn/DW

እርዳታዉን በኮማንድ ፖስት ድጋፍ ለማምጣት ንግግር እየተደረገ ነዉ

ከሚያዚያ ባለፈዉ ሚያዝያ ወር ወዲህ በመንገድ መዘጋት ጸጥታ ችግር ለካማሺ ዞንና አሶሳ ዞን የተወሰኑ ቦታዎች ለሚገኙ ተፈናቃዩች እርዳታ ማድረስ አለመቻሉን የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል የአደጋ ስጋት ሥራ አመራር ኮሚሽን አስታወቀ፡፡ በጸጥታ ችግር ምክንያት በተለይ ጊምቢና ነቀምቴ አካባቢ ድጋፍ የጫኑ ከባድ ተሽከርካሪዎች ከወር በላይ በመቆዩታቸው የድጋፍ እጥረት እንዳጋጠማቸው ተመልክቶዋል፡፡ እርዳታ የጫኑ ተሸከርካሪዎችን በመከላከያ እጅባ ወደ ተፈናቃዮቹ ለማምጣት ከአስቸኳይ ጊዜ አስተዳደር / ኮማንድ ፖስት/ ጋር ንግግር እየተደረገ መሆኑ ነዉ ከስፍራዉ የደረሰን መረጃ የሚያሳየዉ። ዝርዝሩን ነጋሳ ደሳለኝ ከአሶሳ ልኮልናል።  

በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል አሶሳ ዞን እና ካማሺ ዞን ውስጥ ለሚገኙት ተፈናቃዩች ከሚያዚያ ወር ወዲህ በተወሰኑ ቦታዎች  በሚስተዋሉት የጸጥታ ችግሮች ምክንያት ሰብአዊ  ድጋፍ የጫኑ ተሸከርካሪዎች ወደ ክልሉ ባለመግባታቸው እርዳታ ማድረስ አለመቻሉን የቤኒሻንል ጉሙዝ ክልል የአደጋ ስጋት ስራ አመራር ኮሚሽን አመልክተዋል፡፡ የኮሚሽኑ ኃላፊ አቶ ታረቀኝ ታሲሳ   በጊምቢ ዕርዳታ የጫኑ 10 ከባድ ተሸከርካሪዎች ለረዥም ጊዜ በመቆየታቸው ለተፈናቀሉ ዜጎች ድጋፍ በወቅቱ ለማድረስ አልተቻለም ብለዋል፡፡  በአካባቢው ከሚገኘው የአስቸኳይ ጊዜ አስተዳደር ወይም ኮማንድ ፖስት ጋር በመሆን በእጀባ እርዳታ ወደ ክልሉ እንዲገባ ጥረት እየተደረገ እንደሚገኝ ጠቁሟል፡፡

Äthiopien  Metekel, Wonbera, Gondi Kebele
ምስል Negassa Desalegn/DW

በአሶሳ ዞን ባምባሲ ወረዳ በአንድ መጠለያ ጣቢያ ውስጥ የሚገኙና ከ 9 ወር በፊት ወደ መጠለያ ጣቢያ እንደመጡ የነገሩን ሁለት ነዋሪዎች ባለፉት ሶስት ወራት ገደማ ሰብአዊ ድጋፍ እንዳላገኙ ተናግረዋል፡፡ በአንድ ወቅት በግል ድርጅች በኩል ድጋፍ መቅረቡ የተገለጸ ሲሆን ባለፉት 9 ወራት  3 ጊዜ ድጋፍ እንዳገኙም ጠቁመዋል፡፡

የክልሉ የአደጋ ስጋት ሥራ አመራር ኮሚሽን ኃላፊ አቶ ታረቀኝ ታሲሳ በክልሉ በሶስት ዞኖች ውስጥ በሰው ሰራሽና የተፈጥሮ አደጋ ሳቢያ ፈናቅሎ የሚገኙ ተፈናቃዩችን መልሶ የማቋቋም ስራም በተሰወኑ ወረዳዎች መጀመሩን ገልጸዋል፡ 80ሺ የሚደርሱ ሰዎች በዳንጉር፣ጉባና ሌሎች ወረዳዎች ውስጥ ወደ ቀያአቸው መመለሳቸውንም አስታውቋል፡፡

በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል በአሁኑ ጊዜ ከ 442 ሺ በላይ ዜጎች በተለያዩ ምክንያች ተፈናቅለው በመጠለያ ጣቢያ ውስጥ እንደሚገኙ የክልሉ የአደጋ ስጋት ስራ አመራር ኮሚሽን ኃላፊ አቶ ታረቀኝ ታሲሳ ዛሬ ለመገናኛ ብዙሐን በሰጡት መግለጫ አመልክዋል፡፡ በሰኔ ወር/2014 ዓ.ም በክልሉ ባሎጅጋንፎይ ወረዳ ሴኔ ቀበሌ ( ቦታው ጊምቢ ወረዳ ቶሌ ቀበሌ አጠገብ የሚገኝ ነው) ሌሎች 2 በሚደርሱ ስፍራዎች በነበረው የጸጥታ ችግር ከ2ሺ 500 በላይ ሰዎች ተፈናቅሎ አርጆ ጉዳቱ እንደሚገኙም አክለዋል፡፡

 

ነጋሳ ደሳለኝ

አዜብ ታደሰ

እሸቴ በቀለ