1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

በትግራይ የክትባትና የመድኃኒት አቅርቦት ችግር

ሐሙስ፣ መስከረም 26 2015

በትግራይ ከጦርነቱ ወዲህ በትግራይ ከተወለዱ ህፃናት መካከል 80 በመቶዎቹ ሊሰጣቸው ይገባ የነበረ ተከታታይ ክትባት አያገኙም ተብሏል። ችግሩ በገጠሪቱ ትግራይ የባሰ መሆኑም ተገልጿል። የመቀሌው ዘጋቢያችን ሚሊዮን ኃይለ ሥላሴ እንደሚለው በትግራይ በመድሃኒቶች እጦት ምክንያት በርካቶች ለሞትና በሽታ እየተጋለጡ ነው።

https://p.dw.com/p/4Hr8L
Tigray Imfung Kinder
ምስል Million Haile Selassie/DW

በትግራይ የክትባትና የመድኃኒት አቅርቦት ችግር


ከጦርነቱ ወዲህ ወደ ትግራይ የሚገባ መደበኛ የመድሃኒት አቅርቦት በመደናቀፉ በክልሉ የሚኖሩ ዜጎች ለከፍተኛ ችግር እየተጋለጡ መሆኑን ይናገራሉ። በተለይም የህፃናት ክትባት አቅርቦት በትግራይ ለረዥም ግዜ እየተቆራረጠ በመሆኑ ህጻናት ለዘላቂ ችግር የሚጋለጡበት አጋጣሚ ተጋርጦባቸዋል።የትግራይ ጤና ቢሮ በቅርቡ አጥንቶ ይፋ ያደረገው መረጃ እንደሚያመለክተው፣ ከጦርነቱ ወዲህ ባለው ግዜ በትግራይ ከተወለዱ ህፃናት መካከል 80 በመቶዎቹ ከተወለዱ እስከ አንድ ዓመት ከሶስት ወር ድረስ ሊያገኙት ይገባ የነበረ ተከታታይ ክትባት እያገኙ እንዳልሆነ ይገልፃሉ። ይህ አሃዝ በትግራይ ገጠሩ ክፍል የባሰ መሆኑ ተመላክቷል። እንደ የትግራይ ጤና ቢሮ መረጃ በአሁኑ ወቅት በመላው ትግራይ መሰረታዊ የሚባለው የህፃናት ክትባት አቅርቦት የለም። በመቐለ ካሰች ጤና ጣብያ ያነጋገርናቸው የሕፃናት ህክምናና ክትባት አስተባባሪ ሲስተር ለተብርሃን ገብረመስቀል፣ ከዚህ በፊት ለህፃናት ይሰጡት የነበረ ክትባት በጤና ጣብያቸው እንደሌለ ያስረዳሉ። ሲስተር ለተብርሃን "ቢሲጂ እና የፖሎዮ ክትባት ህፃናት እንደተወለዱ የሚሰጡ ክትባቶች ነበሩ። አሁን የሉንም። ፔንታ፣ ፒሲዩ፣ ሩታ የተባሉት ክትባቶች ከጤና ጣብያችን ከጠፉ ወራት አልፈዋል" ይላሉ።
በአጠቃላይ በትግራይ ከፍተኛ የመድኃኒቶች እጥረት መኖሩ ባለሙያዎች እና ተጠቃሚዎች ይገልፃሉ። በመቐለ እንደታዘብነው ለስኳር በሽተኞች የሚሆን ጨምሮ የተለያዩ መድሃኒቶች ከአጎራባች ክልሎች በኮንትሮባንድ ነጋዴዎች ገብቶ በውድ ዋጋ ለተጠቃሚዎች ይሸጣል። እንደ የትግራይ ፋርማሲስቶች ማሕበር ገለፃ በዓለም አቀፍ እርዳታ ሰጪ ተቋማት የገባ ጨምሮ አሁን ላይ በትግራይ ያለው አጠቃላይ የመድሃኒት አቅርቦት መጠን ከ5 ነጥብ 2 በመቶ አይዘልም።

ሚሊዮን ኃይለ ሥላሴ 

ኂሩት መለሰ

እሸቴ በቀለ