በሁለት የምርጫ ክልሎች ምርጫ ለጊዜዉ ተቋረጠ
ማክሰኞ፣ ሰኔ 15 2013ማስታወቂያ
በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል በሁለት ምርጫ ክልሎች ማለትም አሶሳ ሁሐ እና አሶሳ መንጌለ የሚባሉ በአጠቃላይ 102 የምርጫ ጣቢያዎች ትናንት የተካሄደው ምርጫ ለጊዜው እንዲቆም ተደረገ። ምርጫው ለጊዜው የተቋረጠው በትናንትናው ዕለት በአጋጠመው የድምጽ መስጫ ወረቀት እጥረት እና ይህንንም ችግር በዕለቱ ለማስተካከል የተደረገው ሙከራ ሳይሳካ በመቅረቱ እንደሆነ በብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ቅርንጫፍ ጽ/ቤት ኃላፊ የሆኑት አቶ ታደሰ ለማ አብራርተዋል።የምርጫ ቦርድ ቅርንጫፍ ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ታደሰ አክለውም ድምጽ አሰጣጡ እንደገና የሚካሄድበት ቀን የምርጫ ቦርድ በሚሰጠው ውሳኔ መሰረት ይሆናል ብለዋል።በትናንትናው ዕለት ምርጫ በተካሄደባቸዉ በሌሎች ስድስት የምርጫ ክልሎች ምርጫው በሰላማዊና በተሟላ ሁኔታ መካሄዱንም ገልፀዋል። በቤኒሻንል ጉሙዝ ክልል ከሚንቀሳቀሱት ተፎካካሪ ፖለቲካ ፓርቲዎች መካከል አንዱ የሆነው የቦሮ ዴሞክራሲያ ፓርቲ የምርጫ ቦርድን ውሳኔ እንደሚደግፍ ገልጸዋል። የፓርቲ የፖለቲካ ዘርፍ ኃላፊ አቶ ዩሐንስ ተሰማ ውሳኔውን ትክክለኛ ፍታዊ ነው ብለዋል። በአሶሳ ዞን ከ360ሺ በላይ ዜጎች በላይ ምርጫ ካርድ መውሰዳቸው ተነግሯል።
ነጋሳ ደሳለኝ
ኂሩት መለሰ