1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

«በሰሞኑ ጥቃት ከ250 ሺህ በላይ ሰዎች ተፈናቅለዋል»

ሐሙስ፣ ጥቅምት 11 2014

በደሴ ከተማ ያሉ ተፈናቃዮች የመኝታና የምግብ እጥረት እንዳጋጠማቸው ገልጠዋል።የደቡብ ወሎ ዞን አደጋ መከላከልና ምግብ ዋስትና ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ መሳይ ማሩ የሚገኘው እርዳታ ከተፈናቃዩ ቁጥር ጋር ስለማይመጣጠን አንዳንዴ ይህ የቅሬታ ምንጭ የሚሆንበት ጊዜ እንዳለም ጠቁመዋል፡፡በአማራ ክልል በጦርነቱ የተፈናቀሉት ከ1 ሚሊዮን 700 ሺህ በላይ ናቸው።

https://p.dw.com/p/41xxk
Internally displaced Persons in Dessie
ምስል Alemnew Mekonnen/DW

«ከ1 ሚሊዮን 700 ሺህ በላይ ሰዎች በአማራ ክልል በጦርነቱ ተፈናቅለዋል።

ሰሞኑን በደቡብ ወሎ ዞን አንዳንድ ወረዳዎች እንደ አዲስ ባገረሸው ውጊያ ሰበብ እጅግ ቁጥሩ የበዛ ተፈናቃይ የደሴ ከተማን ማጨናነቁን የከተማ ነዋሪዎችና ተፈናቃዮች ተናገሩ። አንዳንድ ተፈናቃዮች መጠለያና ምግብ አላገኘንም ሲሉ፣ የዞኑ አስተዳደር ደግሞ አስፈላጊው ነገር ሁሉ እየቀረበ ነው ብሏል።ህወሓት በአማራ ክልል የሚያደርገውን ወረራ በማስፋት በደቡብ ወሎ አንዳንድ ወረዳዎች ሰሞኑን በከፈተው ጥቃት ባለፈው ሳምንት ብቻ ከ250 ሺህ በላይ ወገኖች ከቀያቸው መፈናቀላቸውን የደቡብ ወሎ ዞን አደጋ መከላከልና ምግብ ዋስትና ጽ/ ቤት ሰሞኑን አስታውቋል፡፡ 
ቀደም ሲል ከቆቦ ተፈናቅላ በደሴ አዲስ ፋና ትምህርት ቤት ተጠልላ የምትገኘው ሌላዋ ተፈናቃይ በትምህርት ቤቱ 700 ሆነው ይኖሩ እንደነበር አመልክታ ሰሞኑን በተፈጠረው ችግር 300 ተፈናቃዮች እንዲጨመሩ ሆኖ በተጨናነቀ ሁኔታ ላይ እንደሆኑ አስረድታለች።በአማራ ክልል የደቡብ ወሎ ዞን አደጋ መከላከልና ምግብ ዋስትና ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ መሳይ ማሩ በበኩላቸው አንዳንድ ረጂ ተቋማትና ግለሰቦች ከመስሪያ ቤታቸው እውቅና ውጪ በተናጠል እርዳታ ያደርጉ እንደነበርና ይህም የፍትሐዊነት ጥያቄ በማስነሳቱ ማነኛውም እርዳታ በተቋቋመው “Incident Command Post” በኩል እንዲያልፍ በመደረጉ ችግሩ እየተፈታ ነው ብለዋል፡፡
አንዳንዴ የሚገኘው እርዳታ ከተፈናቃዩ ቁጥር ጋር ስለማይመጣጠን በመስፈርት ቅድሚያ ለሚሰጣቸው ስለሚሰጥ አንዳንዴ ይህ የቅሬታ ምንጭ የሚሆንበት ጊዜ እንዳለም ጠቁመዋል፡፡
የመኖሪያና የእለት የምግብ እርዳታን በተመለከተ አሁን ሁሉም ተፈናቃዮች በተገኘው መጠለያ እንዲገቡ መደረጉን ጠቁመው ሆኖም አንዳንድ ሰዎች ድንኳን ውስጥ አንገባም ከሚሉት ውጪ ችግሩ እየተፈታ መሆኑንና የእለት እርዳታም በትራንስፖርት ችግር መዘግየት የነበረ ቢሆንም ከትናንት ጀምሮ እየቀረበ መሆኑን ነው ያመለከቱት፡፡
በአማራ ክልል በጦርነቱ ምክንያት ብቻ ከ1 ሚሊዮን 700 ሺህ በላይ ወገኖች ተፈናቅለዋል፡፡
ዓለምነው መኮንን

Internally displaced Persons in Dessie
ምስል Alemnew Mekonnen/DW

ኂሩት መለሰ

ነጋሽ መሐመድ