1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ለዘላቂ ሰላም መስፈን የሲቪክ ድርጅቶች ሚና

ረቡዕ፣ መስከረም 23 2016

ኢትዮጵያ ውስጥ የመብት ረገጣዎች እና አስጊ የደህንነት ሥጋቶች መቀጠላቸውን በተባበሩት መንግሥታት የኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብቶች ባለሙያዎች ቡድን አስታውቋል። ይህም በተለይ በአማራ ፣ በአፋር፣ በትግራይ እና በኦሮሚያ ክልሎች የባሰ መሆኑን የባለሙያዎቹ በድን አመልክቷል።

https://p.dw.com/p/4X7BW
የሲቪል ማኅበራት እና ዜጎች
የሲቪል ማኅበራት እና ዜጎችን በማስተማር ሥራ ላይ የተሰማሩ የትምህርት ተቋማት ብሎም ምሁራኖቻቸው ኢትዮጵያ ውስጥ ዘላቂ ሰላም እውን እንዲሆን ፣የዴሞክራሲ ባህል እንዲጠናከርና ሰብዓዊ መብቶች እንዲጠበቁ በትብብር እንዲሰሩ ጥሪ ቀረበ።ምስል Solomon Muche/DW

ሲቪክ ድርጅቶችና ምሁራን ለዘላቂ ሰላም መስፈን ምን ሠሩ ?

የሲቪል ማኅበራት እና ዜጎችን በማስተማር ሥራ ላይ የተሰማሩ የትምህርት ተቋማት ብሎም ምሁራኖቻቸው ኢትዮጵያ ውስጥ ዘላቂ ሰላም እውን እንዲሆን ፣የዴሞክራሲ ባህል እንዲጠናከርና ሰብዓዊ መብቶች እንዲጠበቁ በትብብር እንዲሰሩ ጥሪ ቀረበ። "ኢትዮጵያ ውስጥ ያሉ ሁሉም ችግሮች፣ ግጭቶች እና አለመግባባቶች በሰላማዊ መንገድ እንዲፈቱ ፣ መቋጫ እንዲያገኙ ውትወታም ጥረትም እናደርጋለን" የሚለው የኢትዮጵያ ሲቪክ ማሕበረሰብ ድርጅቶች ምክር ቤት ይህንን ሰምቶ ተግባራዊ ለማድረግ ወሳኙ እና እርምጃ ወሳጁ ግን መንግሥት ነው ብሏል።
በሌላ በኩል ከአንድ ወር በፊት "የኢዲስ ዓመት የሰላም ጥሪ" ካቀረቡት 35 አገር በቀል የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች መካከል አንዱ ፣ አገር አቀፍ የሰላም መድረክ እንዲመቻች ላቀረብነው ጥያቄ በጎ ምላሽ ባናይም አጥፊዎች የሚዳኙበት ገለልተኛ ምርመራ እና ተጠያቂነት እንዲሰፍን የማድረግ ተነሳሽነትን ግን ከመንግሥት በኩል ማየት ጀምረናል ብሏል። ይህንን ያለው ድርጅት መሪ የሆኑ ሰው ብዙ መመዘኛዎችን አጣርቶ እርምጃ ይወስዳል ያሉት የአውሮጳ ኅብረት ለኢትዮጵያ ከፍተኛ መጠን ያለው የገንዘብ ድጋፍ ለማድረግ ከሰሞኑ እንቅስቃሴ ማድረጉን በአብነት ጠቅሰዋል። በኢትዮጵያ ሊካሔድ በታቀደው አገራዊ ምክክር የሲቪክ ማኅበራት ሚና ምን ይሆናል?

የመብት ጥሰቶች ለምን መቆም አልቻሉም? 

ኢትዮጵያ ውስጥ የመብት ረገጣዎች እና አስጊ የደህንነት ሥጋቶች መቀጠላቸውን በተባበሩት መንግሥታት የኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብቶች ባለሙያዎች ቡድን አስታውቋል። ይህም በተለይ በአማራ ፣ በአፋር፣ በትግራይ እና በኦሮሚያ ክልሎች የባሰ መሆኑን የባለሙያዎቹ በድን አመልክቷል። ኢትዮጵያ ውስጥ በጦርነት ወቅት ከፍተኛ በሰብዓዊነት ላይ የሚፈፀሙ እና የጦር ወንጀሎች መፈፀማቸውን ብሔራዊው እና ዓለምአቀፍ የመብት ድርጅቶች አረጋግጠዋል። መሰል ከፍተኛ ጉዳት በሰዎችና በማህበረሰቦች ላይ የሚያደርሱ ችግሮች ከመከሰታቸው በፊትም ሆነ በኋላ እንዳይደገሙ፣ አጥፊዎች እንዲጠየቁ የሚደረጉ ውትወታዎች እና ግፊቶች ውጤት ያላቸው አይመስልም። የኢትዮጵያ ሲቪክ ማህበረሰብ ድርጅቶች ምክር ቤት እንዲህ ያለው ችግር መቋጫ እንዲኖረው የትምህርት ተቋማት እና ሲቪል ድርጅቶች በትብብር ሊሰሩ ይገባል ሲሉ ይህንን የሚያጠናክር ሥራ መጀመሩን የተቋሙን ኃላፊ ወክለው እየሠሩ ያሉት ወይዘሮ ሀና ወልደገብርኤል ተናግረዋል። በተቋሙ የፕሮግራም ልማት አማካሪ የሆኑት ዶክተር ቃለወንጌል ምናለ ሲቪክ ድርጅቶች የጥብቅና እና የውትውታ ሥራ እንደሚሰሩ ፣ ኢትዮጵያ ውስጥ ያሉ "ሁሉም ችግሮች ፣ ግጭቶች፣ አለመግባባቶች በሰላማዊ መንገድ እንዲፈቱ ፣ መቋጫ እንዲያገኙ ጥረት እናደርጋለን" ብለዋል። ነገር ግን የእርምት ሥራዎች እንዲከናወኑ ወሳኙ እና እርምጃ የሚወስደው መንግሥት ነው ብለዋል።

የሰብአዊ መብት ጥሰት ምልክት
የሰብአዊ መብት ጥሰት ምልክት። ፎቶ ከማኅደርምስል Colourbox

"የኢዲስ ዓመት የሰላም ጥሪ" እና ውጤቱ 

አገር በቀል የሲቪል ማኅበራት ለሰላም ጥሪ ጋዜጣዊ መግለጫ እንዳይሰጡ ተከለከሉከአንድ ወር በፊት "የኢዲስ ዓመት የሰላም ጥሪ" ካደረጉት  35 አገር በቀል የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች መካከል በኢትዮጵያ የሰብዓዊ መብቶች ድርጅቶች ሕብረት የተባለው ድርጅት ዳይሬክተር አቶ መሱድ ገበየሁ ድርጅቶቹ ካቀረቡት ጥሪ ውስጥ አገር አቀፍ የሰላም መድረክ እንዲመቻች የሚለው በጎ ምላሽ አለማግኘቱን ሆኖም አጥፊዎች የሚዳኙበት ገለልተኛ ምርመራ እና ተጠያቂነት እንዲሰፍን የማድረግ ተነሳሽነትን ግን ከመንግሥት በኩል ማየት መጀመራቸውንና ብዙ መመዘኛዎችን አጣርቶ እርምጃ ይወስዳል ያሉት የአውሮጳ ኅብረት ለኢትዮጵያ ከፍተኛ መጠን ያለው የገንዘብ ድጋፍ ለመስጠት ከሰሞኑ እንቅስቃሴ ማድረጉን በአብነት ጠቅሰዋል። በቅርቡ አዲስ አበባ የመጡት የዩናይትድ ስቴትስ የአፍሪካ ቀንድ ልዩ መልዕክተኛ ማይክ ሀመር እነዚህን የሲቪክ ድርጅቶች እንዳነጋገሯቸው እና በአማራ ክልል የተደነገገው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ እንዲነሳ ፍላጎት እንዳላቸው ለመንግሥት እንደገለፁ ነግረውናልም ብለዋል።

የሲቪክ ማህበረሰብ ድርጅቶች በተለይ በሰብዓዊ መብት ላይ ይሰሩ የነበሩት ምንም እንኳን 10 በመቶ ገቢያቸውን ከውጪ ረጂዎች ፣ 90 በመቶውን ከሀገር ውስጥ ምንጭ እንዲያደርጉ የሚያስገድደውና ብዙዎች እንዲከስሙ አድርጎ የነበረው ሕግ ተሻሽሎ አሁን ለሥራቸው ማስኬጂያ ገንዘብ ከውጭ የሚያገኙበት ዕድል ቢሰፋም የመብት ረገጣዎችን በዘላቂነት በማስቀረት ረገድ የሚሠሩት ሥራ እዚህ ግባ የሚባል ሆኖ አልተስተዋልም።
ሶሎሞን ሙጬ 
ኂሩት መለሰ
ሸዋዬ ለገሠ