1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ምክክር በሽግግር ፍትሕ የፖሊሲ አማራጭ ሰነድ ላይ

ሰኞ፣ የካቲት 27 2015

የሽግግር ፍትሕ የፖሊሲ አማራጭ ሰነዱ ለታለመው ሥራ የማስፈፀሚያ ስልት አድርጎ ከዘረዘራቸው ውስጥ ክስ ቀዳሚ ነው። እውነትን ማፈላለግ እና ይፋ ማድረግ፣ እርቅ ፣ ምህረት፣ ማካካሻ መስጠት፣ ተቋማዊ ለውጥ ማድረግ የሚሉትም ተዘርዝረዋል። የወንጀል ምርመራውን ፣ ክስ የመመስረቱን እና የፍርድ ሂደቱን ማን ያከናውነው የሚለው ጥያቄም ለውይይት ቀርቧል።

https://p.dw.com/p/4OJIF
Äthiopien Addis Ababa | Nationales Konsultationsprogramm
ምስል Solomon Muche/DW

ምክክር በሽግግር ፍትሕ የፖሊሲ አማራጭ ሰነድ ላይ

የኢትዮጵያ  "የሽግግር ፍትሕ የፖሊሲ አማራጭ ሰነድ" ላይ ዛሬ የመጀመርያው ውይይት ተደረገ። ሰነዱ የተዘጋጀው በግጭት፣ በጦርነት ወይም በሌላ ምክንያት ለተፈፀሙ ጥቃቶች ፣ መጠነ ሰፊ የሰብዓዊ መብቶች ጥሰቶች እና በደሎች የተሟላ መፍትሔ በመስጠት ዘላቂ ሰላም ፣ እርቅ፣ መረጋጋት እና የሕግ የበላይነት የሰፈነበት ሥርዓት መፍጠር ለማስቻል መሆኑ ተገልጿል። የፍትሕ ሚኒስቴር ያዘጋጀው እና በቀጣዩ ዓመት መጀመርያ ፀድቆ ሥራ ላይ ይውላል የተባለው የሽግግር ፍትሕ የፖሊሲ አማራጭ በደሎች እንዲሽሩ ፣ ቁርሾዎች እንዲጠገኑ፣ እና ወደ ዴሞክራሲ የሚደረግ የተባለው ሽግግር እንዲሳካ አስፈላጊ መሆኑ ታምኖበት መዘጋጀቱ ተገልጿል። 
ኢትዮጵያ ከፍተኛ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች እየተፈፀመባት ያለች አገር መሆኗ፣ አለመረጋጋት፣ ግጭትና የእርስ በርስ ጦርነት ዜጎችን ለሞት፣ ለመፈናቀል አደጋ እያጋለጡ በመሆኑና ለነዚህ ችግሮች የተሰጡ ምላሾች ሙሉ አለመሆናቸው የአጥፊዎችና የተጎጅዎችን ቁጥር ማብዛቱ ፣ የበደሎች መደራረብ እና የጥፋቶች ማህበረሰባዊ ቅርጽ መያዝ በመደበኛው የፍትሕ ሥርዓት እና አካሄድ ፍትሕ መስጠትንም ሆነ ይቅርታ እና እርቅን ማከናወን አላስችል በማለቱበማለቱ ፤ ተጠያቂነትን ለማረጋገጥ ብሎም የሕግ የበላይነትን ለማስፈን የሽግግር ፍትሕ ፖሊሲ ማስፈለጉ ተገልጿል።
በሂደት በጉዳዩ ላይ በተመረጡ 59 ቦታዎች ላይ ከሕዝብ ጋር ውይይት እንደሚደረግም በዛሬው የመጀመርያው ውይይት ላይ ተገልጿል። ሰፊ ውይይት ከተደረገበት በኋላ በመጪው ዓመት መጀመርያ ፀድቆ ተግባራዊ ይደረጋል የተባለው የሽግግር ፍትሕ ፖሊሲ "እውነት እየተጣራ ይፋ የሚሆንበት ፣ እርቅ የሚሰፍንበት፣ የማካካሻ እርምጃ እና የተቋማት ለውጥ የሚካሄድበት ይሆናል" ተብሏል። የፍትሕ ሚኒስትሩ ጌድዮን ጤሞትዮስ ይህንኑ አብራርተዋል።
የሽግግር ፍትሕ የፖሊሲ አማራጭ ሰነዱ ለታለመው ሥራ የማስፈፀሚያ ስልት አድርጎ ከዘረዘራቸው ውስጥ ክስ ቀዳሚ ነው። እውነትን ማፈላለግ እና ይፋ ማድረግ፣ እርቅ ፣ ምህረት፣ ማካካሻ መስጠት፣ ተቋማዊ ለውጥ ማድረግ የሚሉትም ተዘርዝረዋል። የወንጀል ምርመራውን ፣ ክስ የመመስረቱን እና የፍርድ ሂደቱን ማን ያከናውነው የሚለው ጥያቄም ለውይይት ቀርቧል። በውይይቱ የተሳተፉት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን ጉዳዩ መሠረታዊ መሆኑን ገልፀው በየዘመኑ በዜጎች ላይ የተፈፀሙ የመብት ጥሰቶች ተገቢ ምላሽ እንዳላገኙ ገልፀው ይህ እርምጃ ያንኑ መልስ ለመስጠት የተወጠነ መሆኑን አብራርተዋል።

Äthiopien Addis Ababa | Nationales Konsultationsprogramm
ምስል Solomon Muche/DW

የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን እና የተባበሩት መንግስታት ከፍተኛ የሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን ጽ/ቤት በጉዳዩ ዙሪያ የማህበረሰብ ምክክሮችን አድርገዋል።በምክክሮችም ዜጎች ሰላምና ደህንነትን እንደሚሹ፣ የማካካሻ እርምጃ እንዲፈልጉ ፣ እውነቱ እንዲጣራ፣ የደረሱ በደሎች እውቅና እንዲሰጣቸው፣ ይቅርታ መጠየቅ ያለበት ይቅርታ እንዲጠይቅ ፣ የወንጀል ምርመራ እንዲደረግና ተጠያቂነት እንዲሰፍን፣ ጥሰቶች እንዳይደገሙ ዋስትና ሊሰጥ እንደሚገባ ፍላጎታቸው መሆኑን ገልፀዋል። 

በዛሬው ውይይት ክስ የመመስረት ተፈፃሚነቱ ቁርጠኝነት ላይ ጥያቄ ተነስቷል። ጉዳዩ ከፖለቲካ ጫና ነፃ ሆኖ ካልተፈፀመ ስኬታማ እንደማይሆንም አስተያየት ቀርቧል።
የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ዐፈ ጉባኤ ታገሰ ጫፎ በውይይቱ ላይ የፍሬ ነገሩን አስፈላጊነት ተናግረዋል።
ኢትዮጵያ ውስጥ ከፍተኛ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች ፣ አለመረጋጋት፣ ግጭትና የእርስ በርስ ጦርነት ሞትና፣ መፈናቀልን ከማስከተሉ ባለፈ ለዚህ የተሰጡ ምላሾች ሙሉ አለመሆናቸው የአጥፊዎችና የተጎጅዎችን ቁጥር ከፍተኛ ማድረጉ፣ የጥፋቶች ማህበረሰባዊ ቅርጽ መያዝ በመደበኛው የፍትሕ ሥርዓት እና አካሄድ ፍትሕ መስጠትንም ሆነ ይቅርታ እና እርቅን ማከናወን አላስችል በማለቱ ፣ ባለፉ በደሎች ይቅር ለመባባልና እርቅ ለማውረድ የሽግግር ፍትሕ የግድ ማስፈለጉን የባለሙያዎች ቡድን ለውይይት ያቀረበው የጥናት ሰነድ ያሳያል።
ሰሎሞን ሙጬ 
ኂሩት መለሰ
ሸዋዬ ለገሠ