1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል
ፖለቲካእስያ

መካከለኛው ምስራቅ አዲሱ የጦር አውድማ ወይስ ?

ሰኞ፣ ነሐሴ 6 2016

በኢራን የስለላ እና የደህንነት ተቋማቶቿ ብቃት ላይ ጥያቄ ያስነሳው ሁነቱ የእስራኤል ሰላዮች ኢራን ውስጥ እንደልባቸው እየተዘዋወሩ «የልባቸውን እያደረሱ ነው » ሲያስብላቸው ፤ በአንጻሩ ኢራን ያላት ብቸኛ መልስ ብቀላ ብቻ መሆኑን በይፋ አስታውቃለች።

https://p.dw.com/p/4jODO
Israel 2023 | Symbolbild Störung GPS | Google Maps-Ansicht von Jerusalem und Westjordanland
ምስል Pond5 Images/IMAGO

የመካከለኛው ምስራቅ ቀውስ ፤ የኃያላን መንግስታት ተሳትፎ ውጥረት እና የኢትዮጵያዉያን ስጋት

ረቡዕ ሐምሌ 24 ቀን 2016 ዓ.ም. እሥራኤል ለዓመታት ምቹ ቦታ እና ጊዜ ስትፈልግላቸው የነበረ እና ቀንደኛ ጠላቴ የምትላቸውን የፍልስጥኤማውያኑን ታጣቂ ቡድን ቁጥር አንድ ሰው ቴህራን ውስጥ ተገደሉ። ኢስማኤል አብደል ሰላም አህመድ ሃኒዬ፤ ከዚያ በፊት ሰዓታት አስቀድሞ  የሊባኖሱ ታጣቂ ቡድን ከመስራቾች አንዱ እንደሆነ የሚታመንበት እና በእስራኤል ላይ ሲፈጸሙ የነበሩ ዋና ዋና ጥቃቶችን እንደመራ የሚታመንበት  ፉአድ ሽኩር ቤይሩት ውስጥ ተገደለ። የሁለቱ ሰዎች መገደል ኢራንን ፣ ፍልስጥኤማውያን እና የሄዝቦላህ ደጋፊዎችን አንገብግቧል፤ ደማቸውን ካልተበቀልን አናርፍም ዛቻም አሰምተዋል። እስራኤል ግን  ለኢስማኤል ሃኒያ ግድያ ማረጋገጫም ሆነ ማስተባበያ ሳትሰጥ ዛሬ ደርሳለች።  የሽብር ፣ ጥቃት ፣ የሞት እና ውድመት ወሬ ብርቅ ያልሆነበት የመካከለኛው ምስራቅ ከዚህ በኋላ ምናልባትም ከእስከ ዛሬው የከፋ የሞት እና የጥፋት ድግስ ተደግሶለት ይሆን ? የጦርነት አውድማ ሃገራት ብሎም በስደት ዓለም በዚያ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ስጋት እና ዕጣ ፈንታቸው ምን ይሆን ?

እሥራኤል ከኢራን ቀጥተኛ ወታደራዊ ጥቃት በኋላ


የእስራኤሉ የስለላ ቡድን ሞሳድ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የተሳካ ተልዕኮ ከፈጸመባቸው ስምሪቶች ውስጥ ለዚያውም በሰዓታት ልዩነት ዋነኛ ጠላቴ ነው የሚላቸውን የሁለት ታጣቂ ቡድኖችን ፖለቲካዊ እና ወታደራዊ አመራር መግደሉ አልያም እንዲገደሉ መረጃ ማደራጀቱ ዋነኛው እንደሆነ ነው የተነገረለት።  
የሐማስ የፖለቲካ ቢሮ ሀላፊ እስማኤል ሀኒዬ በኢራን መዲና ቴህራን ለአዲሱ ፕሬዚዳንት በዓለ ሲመት በሄዱበት ነበር በማረፊያቸው ውስጥ ከነጠባቂያቸው የተገደሉት ። ለሀኒዬ ግድያ እስራኤል ለወራት ሳትዘጋጅ እንዳልቀረች የእስራኤል ፣ ኢራን እና የአሜሪካን ከፍተኛ ባለስልጣናትን ጠቅሶ ኒውዮርክ ታይምስ ዘግቧል። 
በእስማኤል ሃኒያ ግድያ ግድያ እስካለፈው የሳምንቱ መጨረሻ ቀናት እስራኤል ማስተባበያም ሆነ ማረጋገጫ ሳትሰጥ ቆይታለች። 


አገዳደሉም እንደዚያው አወዛጋቢ እንደነበር ነው የታየው ። በአንድ በኩል የእስራኤል የስለላ ድርጅት ሞሳድ በሀኒዬ ማረፊያ ቤት «ከወራት በፊት አስቀድሞ ቦምብ አስገብቶ ነው» የሚል መረጃ ሲወጣ  ፤ በሌላ በኩል ደግሞ ሃኒዬ ከርቀት በመቆጣጠሪያ በሚመራ ተተኳሽ ጥቃት ሳይገደሉ እንዳልቀረ ሲነገር ቆይቷል። የኢራን መንግስት በቅርቡ ባወጣው መግለጫም ይኽንኑ አረጋግጧል።  በጥቃቱ የአሜሪካ እጅ እንዳለበትም በመጥቀስ ። ምንም እንኳ አሜሪካ አስቀድማ  እጄ ከደሙ ንጹህ ነው ብትልም ። 
የኢስማኤል ሃኒዬ በቴህራን መገደል ፤ ለዚያውም ጥብቅ ጥበቃ በሚደረግበት የቴህራን ክፍል መፈጸም ፤ የሀገሪቱን መንፈሳዊ መሪ አያቶላ አሊ ሃሚኒን ጨምሮ ፕሬዚዳንቱን እንዲሁም የወታደራዊ እና የደህንነት ባለስልጣናትን አበሳጭቷል ፤ ብሎም ለበቀል አነሳስቷል። 

ኢስማኤል አብደል ሰላም አህመድ ሃኒዬ ግድያ
በኢራን የስለላ እና የደህንነት ተቋማቶቿ ብቃት ላይ ጥያቄ ያስነሳው ሁነቱ የእስራኤል ሰላዮች ኢራን ውስጥ እንደልባቸው እየተዘዋወሩ «የልባቸውን እያደረሱ ነው » ሲያስብላቸው ፤  በአንጻሩ ኢራን ያላት ብቸኛ መልስ ብቀላ ብቻ መሆኑን በይፋ አስታውቃለች። ምስል Fatemeh Bahrami/picture alliance/Anadolu

አሜሪካ ፤ ኢራን ፤ መካከለኛው ምስራቅ


በኢራን የስለላ እና የደህንነት ተቋማቶቿ ብቃት ላይ ጥያቄ ያስነሳው ሁነቱ የእስራኤል ሰላዮች ኢራን ውስጥ እንደልባቸው እየተዘዋወሩ «የልባቸውን እያደረሱ ነው » ሲያስብላቸው ፤  በአንጻሩ ኢራን ያላት ብቸኛ መልስ ብቀላ ብቻ መሆኑን በይፋ አስታውቃለች። 
እንደዚያም ሆኖ ግን ኢራን በእስራኤል ላይ የምትወስደው ብቀላ መቼ እና እንዴትነት ለጌዜው ገና አልታወቀም። አንድ ነገር ግን ልብ ይሏል፤  ኢራን  አጋሮቼ የምትላቸው እና አሜሪካን ጨምሮ ምዕራባውያን በሽብርተኝነት የፈረጇቸው የሊባኖሱ ታጣቂ ቡድን ሄዝቦላህ እና የየመኑ ሃውቲን ለበቀል እርምጃው ማስተባበሯ እንደማይቀር ነው በስፋት እየተወራ ያለው ። 
እስራኤልም ከኢራን እና አጋሮቿ ሊደርስ ይችላል ያለችውን የብቀላ እርምጃ ለመከላከል ያስችለኛል ያለችውን እርምጃ መውሰድ መጀመሯ ተዘግቧል። የምድር ስር ሆስፒታሎችን ከመክፈት ጀምሮ በጥቃት ምክንያት ተጨማሪ ጉዳት ሊያስከትሉ ይችላሉ   ያለቻቸውን ተቀጣጣይ የፋብሪካ ኬሚካሎችን ከምድር በታች መቅበር መጀመሯም ተገልጿል።  


በእስራኤል ኢራን እና አጋፋሪዎቻቸው ደጀንነት እየተጎሰመ ያለው የጦርነት ነጋሪት የመካከለኛው ምስራቅን ወደሌላ አስከፊ ቀውስ እንዳይከተው ብርቱ ስጋት ያሳደረው ሁነቱ እንደተፈራዉ ይደርስ ይሆን? ወይስ ባላንጣዎቹ ሳይፈልጉም ቢሆን ያረጋጉት ይሆን ?  እንጠይቅ ።
በኢየሩሳሌም በሚገኘው የሂብሩ ዩኒቨርሲቲ የእስልምና እና የመካከለኛው ምስራቅ ጉዳይ አጥኚ ፕሮፌሰር ሲሞን ቮልፍጋንግ ፉክስ እንደሚሉት የሃኒያ በቴህራን መገደል አንድምታው ከ ሃኒዬ እና ሃማስ ባሻገር ለኢራን እንደሀገር ውርደት ያስከተለባት ነው።   

ለሟቹ እስማኤል ሀኒዬ ጸሎት ሲደረግ
በእስራኤል ኢራን እና አጋፋሪዎቻቸው ደጀንነት እየተጎሰመ ያለው የጦርነት ነጋሪት የመካከለኛው ምስራቅን ወደሌላ አስከፊ ቀውስ እንዳይከተው ብርቱ ስጋት ያሳደረው ሁነቱ እንደተፈራዉ ይደርስ ይሆን?ምስል irna.ir

የሳውዲ ዐረቢያ እና የዩኤስ አሜሪካ ግንኙነት


«በቴህራን የኢስማኢል ሃኒዬን ዒላማ ያደረገ ግድያ በመጀመሪያ ደረጃ የኢራን ውርደት ተደርጎ መታየት አለበት።  የአክሲስ ኦፍ ሬዚስታንስ ተወካዮችን ጨምሮ በርካታ እንግዶች በተገኙበት አዲሱ የኢራን ፕሬዚዳንት  ማሱት ፔዜሽኪያን በዓለ ሲመት የሚከናወንበት ትልቅ ስብሰባ ሃማስ ፣ እስላማዊ ጂሃድ ፣ እና ኢስማኢል ሃኒህን ለማጥፋት መመረጡ ፤   ኢራን የራሷን እንግዶች እንኳን መጠበቅ እንደማትችል እና እስራኤል ባሻት ቦታ እና ጊዜ የፈለገችውን ማድረግ እንደምትችል  ያሳየ ነበር።»

በአውሮጳ ህብረት ምክር ቤት የመካከለኛው ምስራቅ ጉዳይ አጥኚ እና ተከታታይ ኬሊ ፕቲሎ እንደሚሉት ደግሞ  የሃማሱ መሪ ግድያ ምናልባትም ሊገመት የማይችል ብዙ ነገሮችን ሊቀያይር የሚችል ነው ።

« የሃማስ የፖለቲካ መሪ የነበሩትን የዕውቁ የሃኒዬ ግድያ ጨዋታ ቀያሪ ይመስለኛል። ይህ ምን ውጤት እንደሚያመጣ ለመናገር በእርግጥ አስቸጋሪ ነው።  ነገር ግን ውጤቶቹ ለከፋ ችግር ሊያጋልጡ የሚችሉ ሊሆኑ ይችላሉ»

የመካከለኛው ምስራቅ ቀውስ በእስራኤል ፣ ኢራን ፣ ሃማስ ፣ ሄዝቦላ እና የሁቲ አማጽያን ተገድቦ የሚቀር አይደለም። እስራኤል በዳይ ትሁን ተበዳይ ፤ ተንኳሽ ትሁን ተተንኳሽ ሁሌም በምንም ሁኔታ ከጎኗ የማትለየው አሜሪካ ተጨማሪ የጦር አውሮፕላን ተሸካሚ መርከቦችን ወደ መካከለኛው ምስራቅ አስጠግታለች። 

የመካከለኛው ምስራቅ የካቶሊክ ጳጳሳት ሲኖዶስ


ኢራን በይፋ ባቀረበችላት ጥያቄ ሩስያ ለኢራን የአየር መከላከያ የራዳር ስረዓት  እንደምታቀርብላት ተሰምቷል። ይህ ደግሞ የዓለማችን ወታደራዊ ኃያላኑ አሜሪካ እና ሩስያ በዩክሬን የጦር ሜዳ በቀጥታ እና በተዘዋዋሪ የጀመሩትን አውዳሚ ጦርነት በመካከለኛው ምሥስራቅ የመቀጠል ዕድላቸው ሰፊ እንደሆነ ነው በተንታኞች እየተገለጸ ያለው። ምንም እንኳ አሜሪካ ፣ ግብጽ እና ቃጣር እስራኤል እና ሐማስ በአስቸኳይ ወደ ሰላም ንግግር እንዲመለሱ እየወተወቱ ቢሆንም ። 
 አይመጣምን ትቶ ይመጣልን መያዝ እና አስቀድሞ መጠንቀቅን የመረጡ በርካታ የውጭ ዜጎች የጦርነቱ ስጋት ካጠላባቸው እንደ ሊባኖስ ካሉ ሃገራት መውጣት መጀመራቸው ተሰምቷል። የተለያዩ አየር መንገዶችም ወደ እስራኤል ፣ ሊባኖስ ኢራን የነበራቸውን በረራም እስከማቋረጥ ደርሰዋል። 

የእስራኤል ጦር በሊባኖስ መንደሮች ተከታታይ ጥቃት አድርሷል
ኢራን በይፋ ባቀረበችላት ጥያቄ ሩስያ ለኢራን የአየር መከላከያ የራዳር ስረዓት  እንደምታቀርብላት ተሰምቷል።ምስል RABIH DAHER/AFP/Getty Images


በመካከለኛው ምስራቅ በሚገኙ ሃገራት የሚኖሩ በርካታ ኢትዮጵያዉያንም በእርግጥ ጦርነቱ ስጋት ገብቷቸዋል።
ሰላማዊት ተስፋዬ ሊባኖስ ቤሩት ውስጥ ነው የምትኖረው ። እርሷ እና ጓደኞቿ በሊባኖስ ሊፈጠር ይችላል ተብሎ በሚጠበቀው ጦርነት ላይ በእርግጥ ስጋት ገብቷቸዋል። በተለይ የሄዝቦላህ ወታደራዊ አዛዥ ፉአድ ሽኩር ከተገደለ በኋላ በሊባኖስ ያለው ሁኔታ እየተለዋወጠ ነው።
« በእርግጥ ወደ ገጠራማ ሳይዳሱር ወደ ሚባሉ አካባቢዎችጋ ያለው ነገር ትንሽ ያስፈራል። ለእነርሱ እዚያ አካባቢ ለሚኖሩት ዛሬ ሳይሆን ከስድስት ወር ከሰባት ወራት በፊት የነበሩ ድምጾች አሉ ። ዕቃ የመውደቅ የተለያዩ ነገሮችን እንሰማለን። እኛ ግን አሁን ከባለፈው ሳምንት ጀምሮ ነው እንቅስቃሴዎችን እየሰማን ያለነው ።  ባለፈው ሳምንት አንድ ዋናው በሞተበት አጋጣሚ ፤ ከዚያ በኋላ ነው እንግዲህ ፍርሃታችን እየጨመረ የመጣው ።»

የእስራኤል፡ ፍልስጤም ኢቀጥተኛ ድርድር


ተስፋነሽ ታከለም እዚያው ሊባኖስ ቤሩት ውስጥ ሳይዳ በምትባል የከተማ ክፍል ውስጥ በቤት ሰራተኝነት እያገለገለች ትገኛለች።  ከአሰሪዎቿ በምትሰማው እና እየሆነ ባለው ነገር ስጋት እንደገባት ትናገራለች።
«ያለው ነገር በጣም ያስፈራል ፤ ሰዎች የሚናገሩት ነገር ብዙም ምቹ አይደለም በቃ ፤ በፍርሃት ውስጥ ነው እኛ ያለነው»
ጦርነቱ መቼ ይጀመራል ከሚለው ጥያቄ ይልቅ መቼ ይባባሳል የሚል ጥያቄ ማንሳትን የሚያስቀድሙም አይጠፉም ። ምክንያታቸው ደግሞ በየዕለቱ ለሰዎች ሞት ፣ የአካል ጉዳት እና የንብረት ውድመት ምክንያት የሆኑ ጥቃቶች አንዱ በአንዱ ላይ መፈጸማቸው በመቀጠሉ ነው። 
በኩዌት ዩኒቨርሲቲ የኤኮኖሜ ጉዳዮች ተመራማሪ ዶክተር አየለ ገላን እንደሚሉት ኢራን ባለፈው በእስራኤል ላይ ያዘነበችው አይነት የሚሳኤል ጋጋታ የመደገም ዕድሉ ጠባብ ነው ። ምንም እንኳ ጦርነቱ አይቀሬ ቢመስልም።

የእስራኤል ጦር በጋዛ ያደረሰው ጥቃት
ጦርነቱ መቼ ይጀመራል ከሚለው ጥያቄ ይልቅ መቼ ይባባሳል የሚል ጥያቄ ማንሳትን የሚያስቀድሙም አይጠፉም ። ምክንያታቸው ደግሞ በየዕለቱ ለሰዎች ሞት ፣ የአካል ጉዳት እና የንብረት ውድመት ምክንያት የሆኑ ጥቃቶች አንዱ በአንዱ ላይ መፈጸማቸው በመቀጠሉ ነው። ምስል AP Photo/picture alliance


« እውነቱን ለመናገር እነደዚህ አይነት ነገሮች በርካታ መላምት ነው ያላቸው እና በእርግጠኝነት ይሄ ይሆናል ለማለት አስቸጋሪ ነው። መላ ከመምታት ተነስቼ ግን ይኼ ይሆናል የሚለውን ለማስቀመጥ ያህል ግን ሲመስለኝ ምናልባት ነው እንግዲህ ምናልባት ኢራን እንደባለፈው አይነት ሚያዝያ ያደረገችውን አይነት የሚሳኤል ጋጋታ ወደ እስራኤል በቀጥታ ትተኩሳለች ብዬ አልገምትም። ምክንያቱም የአጸፋ ጋጋታ ይመጣላ  ከዚህ ይልቅ ሊባኖስ ውስጥ የሚገኘውን የሄዝቦላ ታጣቂ ቡድን ማጠናከር ላይ ሊያተኩሩ ይችላሉ የሚል ግምት አለኝ  »
የመካከለኛው ምሥራቅ ጦርነት በወታደራዊ ኃይል ጥቃት ከማድረስ እና ከመከላከል ባሻገር የኤኮኖሚ ጦርነቱም ቀላል ግምት የሚሰጠው አይደለም ይላሉ ዶ/ር ኢየለ። በዚህ ረገድ ደግሞ ኢራን በምትደግፋቸው የየመን የሁቲ አማጽያን አማካኝነት የቀይ ባህር የመርከብ የንግድ መርከብ መስመርን ያሽመደመደችበት እና በእስራኤል ላይ የጎላ ጉዳት ያስከተለችበትን አንድምታ ያነሳሉ።
«ሀውቲዎች ማድረግ የፈለጉትን እስራኤልን በኤኮኖሚ ወጥሮ መርከቦች ወደ እስራኤል እንዳይሄዱ ፤ በዚያ በኩል እንዳያልፉ ማድረግ ችለዋል። ቀላል ጥቃት አይደለም።»
እርግጥ ነው የመካከለኛው ምስራቅ ቀውስ በጦርነቱ ውስጥ ተሳታፊ በሚሆኑ ሃገራት የሚያስከትለው ውድመት ቀላል ግምት የሚሰጠው አይደለም። 

የአውሮፓ ህብረት፤ የመካከለኛው ምስራቅ፣ ዩክሬይን እና የሳህል አካባቢ አጀንዳዎች


የግጭት ጦርነቱ ማጠንጠኛ የእስራኤል ሐማስ ጦርነት ዓመት ሊሞላው ከሁለት ወራት ያነሰ ጊዜ ብቻ ቀርቶታል ። በጦርነቱ ጋዛ 40 ሺ ገደማ ልጆቿን በሞት  ተነጥቃለች ። መቶ ሺ ገደማ ልጆቿ ከቀላል እስከ ከባድ የአካል ጉዳት አስተናግደዋል። የሞት እና የአካል ጉዳት ከደረሰባቸው ፍልስጥኤማውያን 70 ከመቶ ገደማ ያህሉ ሴቶች  እና ህጻናት መሆናቸውን መረጃዎች ያመለክታሉ ። ጋዛ በእርግጥ ወደ ፍርስራሽነት ተቀይራለች።  በእስራኤል በኩል በመስከረም 27ቱ የሃማስ ጥቃት ከ1100 በላይ እስራኤላዉያን ሲገደሉ ሌሎች በርካቶች ቆስለዋል። ከ250 በላይ  በሃማስ ታግተው ከተወሰዱት ሰዎች መካከል 115ቱ አሁንም ድረስ በሃማስ እጅ እንዳሉ ይታመናል።  

 

እስራኤል ሃማስን ሳላጠፋ አላርፍም አይነት ንጹሃንን ያልለየ ወታደራዊ ዘመቻዋን አጠናክራ ቀጥላለች ። ባለፈው ቅዳሜ እንኳ ተፈናቃይ ፍልስጥኤማዉያንን ባስጠለለ ትምህርት ቤት ላይ ባደረሰችው ጥቃት 100 ያህል ፍልስጥኤማዉያን ተገድለዋል። 

ትኩረት የሳበው የአውሮጳ ህብረት የመሪዎች ጉባኤ


በማግስቱ ትናንት እሁድ ከወደ ሊባኖስ የተሰማው ዜና ደግሞ ሄዝቦላ ለተገደለበት ወታደራዊ አዛዡ ብቀላ በሰሜናዊ እስራኤል በሚገኝ አንድ ወታደራዊ ማሰልጠኛ ሰፈር ላይ የድሮን ጥቃት ፈጽሞ ጉዳት ማድረሱን ገልጿል። ምንም እንኳ እስራኤል ሄዝቦላ ካሰማራቸው ድሮኖች አንዱን መትቶ መጣሉን እና ሌሎች መከስከሳቸውን ቢያሳውቅም። 

በሊባኖስ የደረሰ ጥቃት
በማግስቱ ትናንት እሁድ ከወደ ሊባኖስ የተሰማው ዜና ደግሞ ሄዝቦላ ለተገደለበት ወታደራዊ አዛዡ ብቀላ በሰሜናዊ እስራኤል በሚገኝ አንድ ወታደራዊ ማሰልጠኛ ሰፈር ላይ የድሮን ጥቃት ፈጽሞ ጉዳት ማድረሱን ገልጿል። ምስል Stringer/REUTERS


እስራኤል እና አሜሪካ በሳምንቱ መጨረሻ ቀናት በመከላከያ ሚንስትሮቻቸው አማካኝነት ተነጋግረዋል። የእስራኤሉ የመከላከያ ሚንስትር ዮአቭ ጋላንት ባለፈው ዓርብ በሰጡት መግለጫ ሄዝቦላ ትንኮሳዉን አጠናክሮ የሚቀጥል ከሆነ እስራኤል በእጇ ባሉ አማራጮች ሁሉ ተጠቅማ ሄዝቦላን ትዋጋለች ብለዋል።  «በእሳት የመጫወት ውጤቱም መጨረሻው ጥፋት ነው ብለዋል።» 
እስራኤል እና ሃማስ ጦርነት ከጀመሩበት የባለፈው መስከረም 26 ቀን 2016 ዓም ጀምሮ ለሃማስ አጋርነቱን የገለጸው ሄዝቦላ ከእስራኤል በተሰነዘረበት የአየር ጥቃት ወታደራዊ አዛዦችን ጨምሮ ከ350 በላይ ታጣቂዎች እና አባላት እንደተገደሉበት መረጃዎች ያመለክታሉ። 

 

የመካከለኛው ምስራቅ የሠላም ሂደቱና ውድቀቱ
ታጣቂ ቡድኑ በሰሜናዊ እስራኤል ባደረሰው ተከታታይ ጥቃትም ወታደሮችን ጨምሮ በርካታ እሥራኤላዉያን ተገድለዋል።
በመላው ዓለም የማህበረ ፖለቲካ ኤኮኖሚ ተጽዖኖ ፈጣሪ በሆነው መካከለኛው ምስራቅ በእርግጥ መቼ ምን ሊፈጠር እንደሚችል ማንም አፉን ሞልቶ መናገር አይችልም ። 
እንደ የመገናኛ ብዙኃን ዘገባ እስራኤል በጋዛ ዘመቻ ከጀመርችበት ጊዜ አንስቶ ከአንድ ሶስተኛ በላይ የሃማስ ታጣቂዎችን መግደል እንዳልቻለች ነው። ይህ ደግሞ አሁንም ሃማስ ከሁለት ሶስተኛው ኃይሉ ጋር ያለበት አለ ማለት ነው። የሃዉቲ አማጽያን ከነአስቸጋሪ የአማጺ ባህሪያቸው በማንኛውም ሰዓት ጥቃት የማድረስ አቅም እንዳላቸው አሳይተዋል። 


በእስራኤል አፍንጫ ስር ሆኖ እስከአፍንጫዊ የታጠቀው ሄዝቦላ ብርቱ የእስራኤል ተገዳዳሪ ነው። ከእነርሱ ጀርባ ደግሞ በጊዜ ሂደት ጡንቻዋን ያፈረጠመችው ኢራን አለች ። አሜሪካም ወደ ጫወታው ሜዳ ተጠግታለች። ሩስያም በቅርብ ርቀት አለች ። በእርግጥ የመካከለኛው ምሥራቅ ከሰፈር ጥል ባሻገር ዓለም አቀፍ የጦር አውድማ ይሆን ይሆንን? የእኛን ልጆች ጨምሮ የሰላማዊ ሰዎች ዕጣ ፈንታስ ምን ይሆን? ወይስ በጎውን እንመኝና ተቀናቃኞችን ወደ ሰላም ንግግር የሚመልስ የሆነ ተዓምር ይፈጠር ይሆን
ታምራት ዲንሳ 
ኂሩት መለሰ