1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ሐረማያ ዩኒቨርሲ የኮሮና ምርመራ በሁለት ቦታ ጀመረ

ሰኞ፣ ሚያዝያ 5 2012

ሐረማያ ዩኒቨርሲቲ በዩኒቨርሲቲው ዋና ግቢ እና ሐረር በሚገኘው የሕክምና ትምህርት ክፍል የኮሮና ቫይረስ ምርመራ ማድረግ የሚችሉ ሁለት ላብራቶሪዎችን ለአገልግሎት ዝግጁ ማድረጉን አስታወቀ። 

https://p.dw.com/p/3aqEe
Äthiopien Haramaya Universität
ምስል DW/Mesaye Tekelu

ሐረማያ ዩኒቨርሲ የኮሮና ምርመራ በሁለት ቦታ ጀመረ

ሐረማያ ዩኒቨርሲቲ በዩኒቨርሲቲው ዋና ግቢ እና ሐረር በሚገኘው የሕክምና ትምህርት ክፍል የኮሮና ቫይረስ ምርመራ ማድረግ የሚችሉ ሁለት ላብራቶሪዎችን ለአገልግሎት ዝግጁ ማድረጉን አስታወቀ። 
ዩኒቨርሲቲው የላብራቶሪዎቹን ስራ መጀመር አስመልክቶ ባካሄደው ውይይት እና ጉብኝት ላይ ሀረር የሚገኘው የዩኒቨርሲቲው ህክምና ፋካልቲ ላብራቶሪ ኃላፊ ዶ/ር ነጋ አሰፋ ለዶይቼ ቬለ እንደገለፁት ላብራቶሪዎቹ የኮቪድ 19 ምርመራ ለማድረግ ዝግጁ ናቸው ፡፡
ኃላፊዎቹ እንዳሉት በዩኒቨርሲቲው ዋና ግቢ የሚገኘው ላብራቶሪ በቀን ሁለት መቶ ናሙናዎችን መመርመር የሚያስችል ነው። 
ላብራቶሪውን በሙሉ አቅሙ ለማሰራት የሚያስፈልጉ ግብዓቶች መኖራቸውንና ይህንኑ በሚመለከት  ከኢትዮጵያ ህብረተሰብ ጤና ኢንስቲቲዩት ጋር በመነጋገር ላይ መሆናቸውን ጠቁመዋል፡፡
የሀረማያ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ዶ/ር ጀማል ዩሱፍ በበኩላቸው ለምስራቅ ሀገሪቱ አካባቢዎች አገልግሎት የሚሰጡት የዩኒቨርሲቲው ሁለቱ ላብራቶሪዎች አቅም ቀጣይነት እንዲኖረው የሚመለከታቸው የመንግስት አካላት አስፈላጊውን ድጋፍ እንዲያደርጉ ጠይቀዋል።
ከዚህ በተጨማሪ "አስከፊውን የኮቪድ 19 ወረርሽኝን መከላከል በእውቀት ሊመራ ይገባል" ያሉት የዩኒቨርሲቲው ፕሬዝዳንት ዶ/ር ጀማል በዩኒቨርሲቲው የሚገኘው የምርምር እና ፈጠራ ቡድን የተለያዩ ፈጠራዎችን እየሰራ መሆኑን አስረድተዋል ፡፡
የላብራቶሪዎቹ ስራ መጀመር ቀደም ሲል አዲስ አበባ በመላክ ይደረግ የነበረውን የናሙና ምርመራ በአቅራቢያ እንዲሆን የሚያደርግ እና ችግሩን ለመከላከል የሚደረገውን ጥረት የሚያግዝ መሆኑን በዝግጅቱ ላይ የተገኙት የሀረሪ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ዑርዲን በድሪና የኦሮሚያ ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች ተናግረዋል።
መሳይ ተክሉ
 ኂሩት መለሠ