ታሪካዊው የሼህ ሆጀለ ቤተ- መንግስት
ቅዳሜ፣ ሰኔ 15 2011ማስታወቂያ
በአሁኑ ጊዜ ስፍራው የከተማዋ ቀዳሚ የቱሪስት መዳረሻ ስፍራ ለማድረግ እየሰራ እንደሆነ የክልሉ ባህልና ቱሪዝም ቢሮ ገልፆአል። ሼህ ሆጀለ አሊ ሀሰን በኢትዩጵያ ውስጥ ለባንክ መመስረት እገዛ ከማድረግ ጀምሮ በጣሊያን ወረራ ወቅት ለሀገራቸው ዳር ድንበር መጠበቅ ከፍተኛ አስተዋጾ ማበርከታቸውን የግል ታሪካቸው ያስረዳል፡፡ከመቶ ዓመታት በፊት የተለያዩ ውሳኔዎችን ይሰጡበት የነበረው በአሶሳ ከተማ የሚገኘው የሼህ ሆጀለ ቤተ መንግስት ወይም የሼህ ሆጀለ አሊ ሀሰን የችሎት አዳራሽ በመባል የሚታወቀው ከዚህ ቀደም በደረሰበት ጉዳት ምክንያት ለክልሉ የቱሪስት መዳረሻ ስፍራ መሆን አልቻለም ነበር ተብሏል። የሼህ ሆጀለ ቤተ-መንግስት በባህልና ቱሪዝም ቢሮ በታሪካዊ ቅርስነት የተመዘገበ ቢሆንም ለቅርስ የሚሠጠውን ያህል ትኩረት አልተሰጠውም የሚለው ሀሳብ የሚጋሩት የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ባህልና ቱሪዝም ቢሮ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ አበበ ጥላሁን ቤተ- መንግስቱ የቀደመውን ይዘቱን ሳይለቅ እንዲቆይና አስፈላጊውን መሰረተ ልማቶችን ለማሟላት እየሰራ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡ ከዚህ ቀደም በክልሉ የቱሪዝም አቅም ጥናት በማድረግ የሼህ ሆጀለ ቤተ- መንግሰትን ጨምሮ በክልሉ ሦስት የሚሆኑ ታሪካዊ ስፍራዎች በቅርስነት መመዝገባቸውን ኃላፊው ገለፀዋል።
ነጋሳ ደሳለኝ
ልደት አበበ