ጃሚንግ እና አይ ቲ ዩ
ማክሰኞ፣ መጋቢት 11 2004ጉዳዩን በቅርበት የተከታተለው መንበሩን ዤኔቭ ያደረገው ድርጅት እንዳስረዳው፡ ይህ የመረጃ ፍሰትን ያደናቀፈው ተግባር በተለይ በዐረባውያቱ ሀገሮች ውስጥ የሕዝብ ዓመፅ ከተቀሰቀሰበት ጊዜ ወዲህ ተጠናክሮዋል።
በመሆኑም በዚሁ ሕዝብ መረጃ የሚያገኝበትን መሰረታዊ መብት የሚጥሱት ወገኖች ከዚሁ ተግባራቸው እንዲታቀቡ ድርጅቱ ከጥቂት ጊዜ በፊት ባካሄደው ምክክር ላይ ማሳሰቡን የቴክኒክ ክፍል ኃላፊ ኢቮን ኦንሪ ገልጸዋል።
አንድ መቶ ዘጠና ሦስት አባል ሀገሮች ያሉት ዓለም አቀፉ የቴሌኮምዩኒኬሽን ህብረት የራድዮና የቴሌቪዥን ስርጭቶችን ባዕድ ረባሽ ድምጽ በማስገባት ለማወክ እና ለማፈን ሆን ተብሎ በሚደረግ አሰራር፡ ማለትም በጃሚንግ አንጻር አስፈላጊው ትግል ሊደረግ እንደሚገባ አሳስቦዋል። ድርጅቱ በዚሁ ጊዜ ይህን ማሳሰቢያ ማሰማት አስፈላጊ የሆነበትን ምክንያት የቴክኒክ ክፍል ኃላፊ ኢቮን ኦንሪ ሲያስረዱ፡
« ካለፉት ሁለትና ሦስት ዓመታት ወዲህ የማሠራጫ ሞገዶች በተደጋጋሚ መታወካቸውን ያመላከቱ ክሶች እየተበራከቱ የሄዱበት ሁኔታ አንዱ ምክንያት ነው። ለነገሩ በየጊዜው እየተገናኘ በራድዮና ቴሌቪዥን ስርጭቶች ደንቦች ላይ የሚመክረው የድርጅቱ ስብሰባ እንዲህ ዓይነት ወቀሳ በሚቀርብለት ጊዜ በአሰራሩ ላይ ችግሩን ለማስወገድ የሚቻልበትን ለውጥ ለማድረግ ይሞክራል። እና የተወሰኑ አባል ሀገሮች ለችግሩ መፍትሔ ሊያስገኝ ይችላሉ ባሉዋቸው ሀሳቦች ላይ ድርጅቱ ውይይት እንዲያደርግበት ሀሳብ በማቅረባቸው ነበር። »
እንደሚታወቀው፡ ባለፉት ጊዚያት ከተለያዩ አባል ሀገሮች እና ከአምስት ዓበይት የዓለም አቀፍ አሰራጪ ድርጅቶች በተደጋጋሚ በሳተላይት ስርጭቶች ላይ አፈና ይደረጋል በሚል ወቀሳ ከቀረበለት በኋላ ነው።
በአባል ሀገሮች ሆን ተብሎ የሚደረግ እወካ ወይም አፈናን ለማስቀረት እንዲቻል አይቲ ዩ በአሰራሩ ላይ አንዳንድ ለውጥ የማድረጉን ስምምነት የደረሰው ከአራት ሣምንታት በፊት በዤነቭ ባደረገው ምክክር ላይ ነበር። በተለይ በፋርስ እና በዐረብኛ እንዲሁም በሌሎች ቋንቋዎች የዶይቼ ቬለ እና የአሜሪካ ድምፅ የአማርኛ ሥርጭትም ጭምር ሆን ተብሎ በተደረገ የአፈና ተግባር እየታወኩ መሆናቸው ነበር በወቅቱ የተገለጸው። በአረብ ሳት እና በዩቴልሳት በየሚተላለፉ የሳተላይት ስርጭቶች ላይ የታየው የዚሁ እወካ ምንጭም ከኢራን፡ ከሶርያና ካንዳንድ ሌሎች ሀገሮች መሆኑ ነበር የተነገረው።
ድርጅቱ ከጥቂት ጊዜ በፊት ያደረገጋቸው አንዳንድ የአሰራር ለውጦች እነዚህ በእወካ ተግባር የሚወቀሱትን ሀገሮች አሰራር ያስለውጥ መሆን አለመሆኑና ጠብቆ የሚታይ ቢሆንም፡ ኢቮን ኦንሪ እንዳሉት ግን እስካሁን የሚያበረታታ ውጤት አልታየም።
« በመገናኛ ዘዴ ስርጭት ላይ ባለፉት ጊዚያት ብዙም መሻሻል አላየንም፤ በተለይ በዚህ ሣምንት፡ ትናንት ራሱ አንዳንድ አባል ሀገሮች አረፈብን ባሉት ጃሚንግ አንጻር እንድንረዳቸው ጥያቄ ማቅረባቸው ይህን የሚያረጋግጥ ሆኖዋል። አፈናው በተለይ በወቅቱ ትልቅ ውዝግብ ከሚታይባት ከሶርያ አኳያ መሰንዘሩ ነው የተሰማው። »
አባል ሀገሮች አይ ቲ ዩ የሚያወጣቸውን መመሪያዎች እንዲያከብሩ ለማስቻል ድርጅቱ ተጨማሪ ሥልጣን እንዲኖረው የሚፈልጉ ወገኖች እንዳሉ ነው ኢቮ ኦንሪ ያስረዱት።
« በርካታ አውሮጳውያት ሀገሮች የሚጠቃለሉበት እና በዩኤስ አሜሪካ የሚደገፍ አንድ የአባል ሀገሮች ቡድን አይቲ ዩ ጃሚንግን በመታገሉ ረገድ ሁነኛ ርምጃ መውሰድ እንዲችል ሚናውን ማጠናከር መፈለጉን ግልጽ አድርጎዋል። የተወሰኑ የጃሚንግ ዓይነቶችን ለመታገል ይቻልም ዘንድ በድርጅቱ የስርጭት አሰራር ላይ አንዳንድ ለውጥ ማድረግ አስፈላጊ እንደሚሆን ነበር ቡድኑ ያሳሰበው። »
በተለይ ካለፈው አንድ ዓመት ተኩል ወዲህ የሕዝብ ዓመፅ ከተቀሰቀሳበቻው ዐረባውያቱ ሀገሮች፡ በተለይም ከሶርያ እየተጠናከረ መምጣቱን የሚጠቁሙ በርካትታ ምልክቶች ማግኘቱን ገልጾዋል።
አርያም ተክሌ
ሂሩት መለሰ