የጠቅላይ ሚንስትር ጽ/ቤትና የውጭ ጉዳይ መግለጫ
ሐሙስ፣ ጳጉሜን 4 2013ማስታወቂያ
የጠቅላይ ሚንስትር ጽ/ቤትና የውጭ ጉዳይ ሚንሥትር በየፊናቸው ዛሬ ወቅታዊ ጉዳዮች ላይ መግለጫ ሰጥተዋል። ኢትዮጵያ በተጠናቀቀው ዓመት በዲፕሎማሲያዊ ሥራዎች ብርቱ ችግሮችን መጋፈጧን ስኬቶችንም መቀዳጀቷን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ገልጧል። የታላቁ ሕዳሴ ግድብን የፀጥታ ሥጋት አድርጎ ዓለም አቀፍ ጉዳይ ማድረግን ችግር፤ ጉዳዩ ወደ አፍሪቃ ማዕቀፍ መመለሱን ደግሞ ስኬት ብሎታል። የግድቡን ሁለተኛ ሙሌት ማጠናቀቅ በስኬት ታይቷል። ሱዳን የኢትዮጵያን ሉዓላዊ ግዛት በኃይል ወርራ መያዟ እና ችግሩ እስካሁን ባይፈታም የኢትዮጵያ ትዕግስት እና ነገሩን በስክነት ማየት እንዲሁም የብጥብጥ መነሻ ይሆናል ተብሎ የነበረውን አገር አቀፍ ምርጫ ማጠናቀቅ በስኬት የሚጠቀሱ መሆናቸውን የሚኒስቴሩ ቃል አቀባይ አምባሳደር ዲና ሙፍቲ ተናግረዋል። በሌላ በኩል የጠቅላይ ሚኒስቴር ጽ/ቤት የፕሬስ ሴክሬታሪያት ዛሬ በሰጡት መግለጫ ሕወሓት በአፋር ክልል በመከላከያ ሠራዊት እና የአፋር የፀጥታ አካላት ተሸንፎ መውጣቱ ተገልጿል። ቡድኑ በአማራ ክልል ዳባት ወረዳ 200 ንፁሐን ዜጎችን መግደሉንና ምን ያህል ሰዎች እንደተገደሉ የሚያጣራ ኮሚቴ መቋቋሙም ተነግሯል።
ሰለሞን ሙጬ
ማንተጋፍቶት ስለሺ
ነጋሽ መሐመድ