የጌንሸር ህልፈት
ዓርብ፣ መጋቢት 23 2008የቀድሞዉ የጀርመን የረጅም ዘመን ዉጪ ጉዳይ ሚንስትር እና የለዘብተኛዉ የነፃ ዴሞክራቶች ፓርቲ (FDP) መሪ ሐንስ-ዲትሪች ጌንሸር ሞቱ።89 ዓመታቸዉ ነበር።እዚሕ ቦን የሚገኘዉ ፅሕፈት ቤታቸዉ እንዳስታወቀዉ አንጋፋዉ ፖለቲከኛና ዲፕሎማት የሞቱት ዛሬ ሲነጋጋ ነዉ።ጌንሼር በጤና እጦት ለብዙ ጊዜ የሐኪም ክትትል አልተለያቸዉም ነበር።እንደ ጎርጎሪያኑ አቆጣጠር ከ1974 እስከ 1992 ድረስ መጀመሪያ የቀድሞዋ ምዕራብ ጀርመን ኋላ ደግሞ የተዋሐደችዉ ጀርመንን በዉጪ ጉዳይ ሚንስትርነት ለእስራ-ስምንት ዓመታት አገልግለዋል።ጌንሸር ቀዝቃዛዉ ጦርነት በሠላም እንዲያበቃ፤የአዉሮጳ አንድነት እንዲጠናከር እና ከሁሉም በላይ ጀርመን ዳግም እንድትዋሐድ አብይ አስተዋፅኦ ያደረጉ ዲፕሎማት ነበሩ።
የጀርመኑ ፕሬዝደንት ዮአኺም ጋዉክ የጌንሸር ተዓማኒነትና ዲፕሎማሲያዊ ክሒል ለጀርመን ገፅታ ዓለማቀፋዊነትን የቸረ ብለዉታል።ለዉጪ ጉዳይ ሚንስትር ፍራንክ ቫልተር ሽታይንማየር ደግሞ ጌንሸር «ደማቅ ታሪክ የፃፉ፤ የጀርመንና የአዉሮጳ ታላቅ ልጅ» ነበሩ።«ሐንስ ዲትሪች ጌንሼር በረጅም ጊዜ እንቅስቃሴያቸዉና ሕይወታቸዉ ደማቅ ታሪክ የፃፉ (ሰዉ) ናቸዉ።የሐገራችንን-የጀርመን እና የአዉሮጳን ታሪክ።በታሪክ መፅሐፍት የሚኖራቸዉ ሥፍራ ልዩና የሳቸዉ ብቻ ነዉ።የሐንስ ዲትሪች ጌንሸርን ያክል ለረጅም ጊዜ የጀርመን ዉጪ ጉዳይ ሚንስትር የሆነ የለም።የጀርመንን መለያየት እና የአዉሮጳን ክፍፍል ማጥፋት ለሳቸዉ የዕድሜ ልክ ምግባራቸዉ ነበር።ይሕ ታላቅ ፖለቲካዊ አላማዉ ሲሳካ ለማየት እና በገቢራዊነቱ ሒደት መሳተፍም የቻሉ ሰዉ ነበሩ። አንድ ታላቅ ጀርመናዊ እና ታላቅ አዉሮጳዊ ዛሬ ሔዱብን።የእመበለታቸዉን እና የቤተሰባቸዉን ሐዘን እንጋራለን።»
ጌንሸር እንደ ጎርጎሪያኑ አቆጣጠር በ1974 የዉጪ ጉዳይ ሚንስትር ከመሆናቸዉ በፊት ለአምስት ዓመት ያክል የሐገር ግዛት ሚንስትር ነበሩ።
ነጋሽ መሐመድ
ይልማ ኃይለ ሚካኤል
ኂሩት መለሰ
አርያም ተክሌ