የገንዘብ ዝውውር አገልግሎት በሞባይል
ረቡዕ፣ የካቲት 2 2008
የኢትዮጵያ ባንኮች እና የገንዘብ ተቋማት ደንበኞቻቸው ባሉበት ሆነው ገንዘባቸውን የሚያንቀሳቅሱባቸው አገልግሎቶች በተንቀቃሳሽ/ሞባይል/ ስልኮች አማካኝነት ጀምረዋል። በዋናነት የባንክ ቅርንጫፎች በአቅራቢያቸው ለማያገኙ የባንክ አገልግሎት ተጠቃሚ ላልሆኑ ግለሰቦች ላይ ትኩረት ያደረጉ ሲሆን ለአገሪቱ አዲስ ናቸው። ባንኮችን፤ የገንዘብ ተቋማት፤ ኢትዮ-ቴሌኮም እና የቴክኖሎጂ ኩባንያዎችን ካጣመሩት ግልጋሎቶች «ሔሎ ካሽ» እና «ኤም ብር» የተባሉት ይጠቀሳሉ።
ደንበኞች ወደ ባንኮች መሄድ ሳያስፈልጋቸው ባሉበት ክፍያ መፈጸም፤ ገንዘብ መላክ እና መቀበል እንዲሁም ጥሬ ገንዘብ ማውጣት የሚያስችሉት የእነዚህ አገልግሎቶች በሌሎች የአፍሪቃ አገራት ተሞክረው ስኬታማ የሆኑ ናቸው።
መቀመጫውን በኔዘርላንድስ ያደረገው ቤል-ካሽ ኩባንያ በሚያቀርበው የ«ሔሎ ካሽ» ቴክኖሎጂ የሚሰጠዉ አገልግሎት በዚህ አመት ብቻ ከ2 እስከ 3 ሚሊዮን ደንበኞችን ለማፍራት አቅዷል። አገልግሎቱ ከአንድ አመት በኋላ ማለትም በጎርጎሮሳዊው 2017 ዓ.ም. የደንበኞቹን ቁጥር ወደ አስር ሚሊዮን ሊያሳዳግ አቅዷል።
የፋይናንስ ፍሰቱንና አገልግሎቱን የሚቆጣጠረው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ «ኤ.ም. ብር» የተሰኘው አገልግሎት ለአምስት የብድር እና ቁጠባ ተቋማት የፈቀደው ባለፈው ታሕሳስ ወር ነበር። የኤም ብር አገልግሎት የቴክኖሎጂ አቅራቢ ሞስ አይሲቲ የተሰኘ ኩባንያ መቀመጫው በደብሊን፣ አይርላንድ ሲሆን ተመሳሳይ አገልግሎቶችን በኬንያ እና ሞዛምቢክም ያቀርባል። የአዲስ ብድር እና ቁጠባ ተቋም ከአገልግሎቱ ጀማሪዎች መካከል አንዱ ነው።
እንደ «ኤም ብር» ሁሉ የ«ሔሎ ካሽ» አገልግሎትም በተለያዩ የገንዘብ ተቋማት በጥምረት የሚሰጥ ነው። ከአስራ ስድስቱ የኢትዮጵያ የግል ባንኮች መካከል ሁለቱ ለደንበኞቻቸው አገልግሎቶቻቸውን ለማቅረብ በ«ሔሎ ካሽ» ይገለገላሉ።
እሸቴ በቀለ
ሸዋዬ ለገሠ