የጀርመን የልማት እርዳታ በጀት መቀነስ
ሰኞ፣ ኅዳር 17 2005
ዲርክ ኒብል እጎአ በ2009 ዓ.ም መጨረሻ ላይ በፌደራል ጀርመን የኤኮኖሚ ትብብርና የልማት ሚኒስትርነት ሥራ ሲጀምሩ የመስሪያ ቤታቸው በጀት 5.8 ቢሊዮን ዩሮ ነበር ። ከዚያም በቀጠሉት አመታት የነፃ ዲሞክራቱ የዲርክ መስሪያ ቤት በጀት እየጨመረ ሄዶ በአሁኑ ጊዜ ወደ 6.4 ቢሊዮን ዩሮ ግድም ደርሷል ።የጀርመን መንግሥት በአጠቃላይ ለልማት እርዳታ የሚመድበው ገንዘብ እጎአ እስከ 2012 ድረስ ከአገሪቱ ያልተጣራ ብሔራዊ የአገር ውስጥ ገቢ 0.35 በመቶ ወደ 0.4 በመቶ ከፍ ብሏል ። ይሁንና የልማት ትብብር መስሪያ ቤት የመጪው አመት በጀት እንዲቀንስ ተወስኗል ።
ስለዚሁ የዶቼቬለው ማርሴል ፍዩርስትናው ያዘጋጀውን ዘገባ ሂሩት መለሰ አጠናቅራዋለች
በመጪው የጎርጎሮሳውያኑ 2013 አመተ ምህረት ከጀርመን የልማት ትብብር ሚኒስቴር መስሪያ ቤት አመታዊ በጀት ላይ 87 ሚሊዮን ዩሮ ይቀነስበታል ። በዚህ የተነሳም መስሪያ ቤቱ በበጀት አመቱ ያለውን ገንዘብ አብቃቅቶ ለመጠቀም ይገደዳል ። ከ 2 ሳምንት በፊት ነበር በሥልጣን ላይ ያሉት ፓርቲዎች የህዝብ እንደራሴዎች በሰጡት ድምፅ በጀቱ እንዲቀንስ የተወሰነው ። በምክር ቤቱ ውስጥ አብልጫ ድምፅ ያላቸው ፓርቲዎች የህዝብ እንደራሴዎች የበጀት ኮሚቴ የልማት ትብብር ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ 38 ሚሊዮን ዮሮ ተጨማሪ ገንዘብ ይሰጠው ሲሉ ጠይቀዋል ። ይሁንና የተጣማሪዎቹ የነፃ ዲሞክራቶቹና የእህትማማቾቹ የክርስቲያን ዲሞክራት ህብረት የክርስቲያን ሶሻል ህብረት ፓርቲዎች ተወካዮች ለአውሮፓ የሚሰጠው የልማት መዋጮ ግን አያስፈልግም ሲሉ ነው የወሰኑት ። የበጀት ቅነሳው የሁለትዮሽ የልማት ትብብር ፕሮጀክቶች ላይ ተፅዕኖ አያደርግም ። ሆኖም እጎአ በ2013 የዲርክ መስሪያ ቤት በአጠቃላይ ሥራዎቹን ለማከናወን በአነስተኛ ገንዘብ መወሰን ይኖርበታል ። ከሁሉ በተለይ በአውሮፓ ህብረት ሥር የሚካሄዱት ፕሮጀክቶች የበጀት ቅነሳው ይነካቸዋል ። ይህ ውሳኔ የልማት ትብብር ሚኒስትር ዲርክ ኒብልን በእጅጉ ቅር አስኝቷል ። « እንደ ጀርመን ፌደራል መንግሥት ለልማት እርዳታ የምናውለውን ገንዘብ መጠን ካልተጣራው ብሄራዊ ገቢያችን ወደ 0.7 በመቶ ለማሳደግ ስናቅድ ፓርላማው ደግሞ ለሌሎች ጉዳዮች ቅድሚያ ከሰጠ ለኔ ማን ከትልሙ እንዳፈነገጠ ግልፅ ነው ። ሌላ ሃሳብ ያቀረበው ሥልጣን ላይ ያለው መንግሥት አይደለም ። ሆኖም እንቀበለዋለን ። ዋናው ነገር በጀቱን የመወሰን መብቱ የፓርላማው ነው ።
ዲርክ ኒብል እንደሚሉት ውሳኔው የጀርመን መንግሥት ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ የገባውን ቃል እንዳይጠብቅ አድርጓል ። የጀርመን መንግሥት በአለም አቀፍ ደረጃ እጎአ እስከ 2015 ለልማት ትብብር የሚያውለውን ገንዘብ መጠን ካልተጣራ የሃገር ውስጥ ገቢው ቢያንስ ወደ 0.7 ለማሳደግ ቃል ገብቶ ነበር ። እናም እንደ ኒብል ይህ ትልም ሊተገበር የማይችል እንደነበረ መረዳት ይቻላል ። ቃል ሲገባ የነበረው እጎአ ከ 1970 ዎቹ አንስቶ ነው ። የተሻለ ውጤት የተገኘው በ1980ዎቹ ነው ። ያኔ የልማት እርዳታው ወደ 0.47 በመቶ አድጎ ነበር ። ስምምነት ላይ በተደረሰባቸው የተመድ የአምዓቱ የልማት ግቦች በኩልም ይህ ነው የሚባል ውጤት አልተገኘም ። በዚህ ረገድ ከጀርመን በኩል የፖለቲካ ፈቃደኝነቱ እንደሚጎድል ነው የተገለፀው ። ከጀርመን ፓርቲዎች አብዛኛዎቹ የ 0.7 በመቶው ትልም ተግባራዊነት ይደግፋሉ ። እጎአ በየካቲት 2011 በጀርመን ፓርላማ ቦታ የያዙ የ5ቱ ፓርቲዎች ተወካዮች በተያዘው ግብ ለመቀጠል ድጋፋቸውን ሰጥተዋል ። ከ 622 የህዝብ እንደራሴዎች 372 እጎአ እስከ 2015 የሚያስፈልገው የ 1.2 ቢሊዮን ዩሮ ጭማሪ እንዲደረግ የተደረገውን ጥሬ ተቀብለዋል ። በሃሳብ ደረጃ 60 በመቶው የትልሙ ደጋፊ ናቸው ። ምንም እንኳን በተጣማሪዎቹ በእህትማማቾቹ በክርስቲያን ዲሞክራት ህብረትና በክርስቲያን ሶሻል ህብረት እንዲሁም በነፃ ዲምኮራቶቹ ፓርቲ መካከል በተደረገው ስምምነት ግቡን ለማሳካት ቢታለምም በተግባር እንደሚታየው ግን የአንጌላ ሜርክል መንግሥት ከታለመው የልማት እርዳታ ግብ አፈንግጧል ። ያም ቢሆን ይላሉ ኒብል ውሳኔውን ከመቀበል ውጭ ሌላ ምርጫ አይኖራቸውም ።
« ፓርላማው በውሳኔው ከ 0.7 ከመቶው ግብ በተወሰነ ደረጃ ርቋል ። ከዝህብ እንደራሴዎች ግማሾቹ ትልሙን አስፈላጊ አድርገው እንደሚወስዱ በፊርማቸው አሳውቀዋል ። እንደ መንግሥት አመራር አባል የፓርላማውን ውሳኔ መቀበል አለብኝ ። እናም ሁኔታው ቀላል አይሆንም »
እጎአ በ2013 በሚካሄደው የጀርመን አጠቃላይ ምርጫ የአረንጓዴዎቹ ፓርቲና ሶሻል ዲሞክራቶች ቀንቷቸው ሥልጣን ከያዙ አሁን የተላለፈው ውሳኔ እንደሚቀይሩ ነው የተናገሩት።
ሂሩት መለሰ
ተክሌ የኋላ