ሰኞ፣ መጋቢት 11 2009
የተባበሩት መንግስታት የስድተኞች ከፍተኛ ኮሚስሽን «UNHCR» ቅዳሜ ባወጣዉ ዘገባ በየቀኑ ከ600 በላይ የሚሆኑ የደቡብ ሱዳን ስድተኞች በአገሪቱ ባለዉ ግጭትና የምግብ እጥረት ምክንያት ወደ ኢትዮጵያ እየገቡ መሆኑን ጠቅሰዋል። ከ 356,000 በላይ የደቡብ ሱዳን ስድተኞች ኢትዮጵያ እንደምታስተናግድ የኮሚሽኑ ዘገባም ያመለክታል።
ከተጠቀሰዉ ቁጥር አብዛኞቹ ስድተኞች በደቡብ ሱዳን የእርስ በርስ ግጭት ከተቀሰቀሰ ከታህሳስ 2006 ወዲህ ወደ ኢትዮጵያ እንደመጡ በኢትዮጵያ የኮሚሽኑ የኮሙኒኬሼን አላፊ አቶ ክሱት ገብረእግዚአብሔር ለዶይቼ ቬሌ ተናግረዋል። ከመስከረም 2009 ዓ,ም ጀምሮም 68, 858 ስድተኞች በጋምቤላ በሚገኘዉ ሰባት የስድተኞች መጠልያ እንደገቡም አቶ ክሱት ገልፀዋል።
አዲስ እየሚመጡት ስድተኞች በጋምቤላና ደቡብ ሱዳን መካከል የምትገኘዋን የድንበር ከተማ በፓጋክ አቋርጦ «ንጉኝል» የተባለዉ ስድተኞች ካምፕ እየገቡ እንደሆነ የ«UNHCR» ዘገባ ያመለክታል። የስድተኞች ቁጥር መጨመሩ አሳሰቢ እየሆነ መምጣቱ የሚጠቅሰዉ ይህ ዘገባ ንጉኝል ስድተኞች መጠልያ ከሞላ አማራጭ የስደተኞች ካምፕ ማፈላለግ ግድ እንደሚለዉ ያሳስባል።
የስድተኞች ቁጥር አሁን ባለዉ ሁኔታ ከጨመረ አሁን አንድ የቀረዉ የስድተኞች መጠልያ በግንቦት ወር ዉስጥ ሊሞላ ይችላል ሲሉም አቶ ክሱት አክለዋል።
ከደቡብ ሱዳን ጋር የሚዋሰነዉ የቤኒሻንጉሉ ጉሙዝ ክልል ብዙ ደቡብ ሱዳናዊያን ስድተኞችም እንደሚገኙ ዘገባዎች ይጠቁማሉ።
አዲስ እየተሰደዱ ያሉት የደቡብ ሱዳን ነዋሪዎች የሚፈልሱት ከላይኛዉ የናይል ግዛትና ከጆንግሌ ግዛት መሆኑን የኮሚሽኑ ዘገባ ጠቅሶ አብዛኞቹም ሴትችና ህፃናት መሆናቸዉን አመልክቶአል።
አዜብ ታደሰ
መርጋ ዮናስ