የይግባኝ ዉሳኔ ለዞን ዘጠኝ ጸሐፍት
ዓርብ፣ መጋቢት 29 2009ማስታወቂያ
በዚህም መሠረት ናትናኤል መኮንን እና አጥናፍ ብርሃኔ በሽብር ወንጀል ሳይሆን በመደበኛ የወንጀለኛ መቅጫ ሕግ ጉዳያቸዉ እንዲታይ ወስኗል። ጉዳያቸዉ በፍርድ ቤት ለ54ኛ ጊዜ መሆኑ ነዉ።በአሁኑ ጊዜ በዉጭ ሀገር የምትገኘዉን ሶልያና ሽመልስን ጨምሮ፤ 10 የሚሆኑ የዞን ዘጠኝ የድረገጽ ጸሐፍት በማኅበራዊ መገናኛ ብዙሃን ላይ በመጻፍ፤ የሚያደርጉትንም መንግሥት እንዳይደርስበት የተለያዩ ስልጠናዎች በመዉሰድ፤ በሽብር ወንጀል ተፈርዶባቸዉ የተከሰሱ ሰዎች እንዲፈቱ በመገፋፋትና በመብት ላይ ጫና በማድረግ የሽብር ወንጀል ፈጽመዋል በሚል መከሰሳቸዉ ይታወሳል። ይህ ክስ እየተመረመረ ባለበት ሰዓት የተወሰኑት ላይ የቀረበዉን ክስም አቃቤ ሕግ በማንሳቱ ተቋርጦ በአምስቱ ማለትም ሶልያና ሽመልስ፤ ናትናኤል ፈለቀ፤ አቤል ዋበላ ፣ በፍቃዱ ኃይሉ እና አጥናፍ ብርሃኔ ጉዳይ ክርክር ቀጠለ። ጠበቃ አምኃ መኮንን ለዶቼ ቬለ በዝርዝር እንዳስረዱት ፍርድ ቤት ክርክሩን ሰምቶ አቃቤ ሕግ ያቀረበዉ ማስረጃ ክሱን አያስረዳም በሚል ሁሉንም ተከሳሾች በነፃ አሰናብቶ ነበር። አቃቤ ሕግ በቂ ማስረጃ ቀርቦ ሳለ የሥር ፍርድ ቤት አላግባብ ዉድቅ አድርጎብኛል ሲል ይግባኝ አለ። ይግባኝ ሰሚዉ ፍርድ ቤትም ይህን ተመልክቶ ዛሬ ሰፋ ያለ ዉሳኔ ሰጥቷል። ዝርዝሩን ከድምጽ ዘገባዉ ያድምጡ፤
ሸዋዬ ለገሠ
አዜብ ታደሰ