የዓለምን ቀዉስ ለመፍታት ሩስያ ዋንኛ አጋር ናት
ቅዳሜ፣ ግንቦት 29 2007ቡድን ሰባት በመባል የሚጠራው የበለፀጉት አገራት ስብስብ ቡድን ጉባኤ ሊጀምር አንድ ቀን ሲቀረው የመሪዎቹን ጉባኤ በመቃወም ዛሬም ደቡባዊ ጀርመን ውስጥ የተቃውሞ ሰልፍ ተካሄደ። ፖሊስ እንዳስታወቀው ቁጥራቸው 3600 የሚጠጉ ሰልፈኞች ጋርሚሽ-ፓርተንኪርሸን በተባለው ከተማ ባቡር ጣቢያ ተቃውሟቸውን ለማሰማት ተሰብስበዋል። የሰልፈኞቹ ቁጥር እስከ 10 000 ከፍ ሊል እንደሚችል ይገመታል። ስለሆነው ፖሊስ የፀጥታ ጥበቃውን አጠናክሯል። በስፍራውም ከመላ ጀርመን 17 ሺህ የሚደርሱ ፖሊሶች ለጥበቃ ተሰማርተዋል። የቡድን ሰባት ተቃዋሚዎች ፤ ለከባቢ አየር ለውጥ እና ድህነትን ለመዋጋት አማራጭ የመፍትሄ ሀሳብ ከጉባኤው ይጠብቃሉ። ይህ በእንዲህ እንዳለ የጀርመኗ መራህይተ መንግሥት አንጌላ ሜርክል ጉባኤው ከመጀመሩ አስቀድመው ከዚህ ጉባኤ የሚጠብቁትን እንደሚከተለው ለዶይቸ ቬለ ገልፀዋል።
«ለእኔ ቀዳሚነት ያለው ነገር በመጀመሪያ የሰባቱ የሀገር እና የመንግሥት መሪዎች ተገናኝተው ወሳኝ በሆኑ ርዕሶች ላይ መወያየታቸው ነው። ይህ በመጭዉ ዓመት የተወሰኑ መሰረታዊ ነጥቦች ላይ ምን እንደታሰበ፤ ልዩነቱች እና የጋራ አስተሳሰብ የቱጋ እንዳለ ለማወቅ፤ የሀሳብ ልውውጥ ማድረጉ በጣም በጣም አስፈላጊ ነው»
አንጌላ ሜሪክ ከ ዶይቼ ቬሌ ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ በዓለም ዓቀፍ የሚታየዉን ቀዉስ ለመፍታት ሩስያ ዋንኛ ሚናን እንደምትጫወት ሳይገልፁ አላለፉም። በሶርያ የሚታየዉን የርስ በርስ ጦርነት ለመግታት ከሩስያ ጋር ብቻ መፍትሄ እንደሚገኝ ሜርክል ተናግረዋል። በሶርያ የነበረዉን ኬሚካላዊ የጦር መሳርያ ለማስወገድ የተቻለዉ ከሩስያ ርዳታ ጋር ብቻ እንደነበር፤ በዚህም ምክንያት የሞስኮዉ መንግሥት ዋንኛ አጋር መሆኑን ሜርክል አስምረዉበታል። እንድያም ሆኖ ባለፉት ዓመታት ሩስያ ከሰባቱ በኢንዱስትሪ ከለፀጉት ሃገራት አስተሳሰብ እና አሠራር ጋር ቀርባ አለመታየቷን ሜርክል ተናግረዋል።
ልደት አበበ
አዜብ ታደሰ